15/09/2026
አምባሳደር ዶ/ር ሙክታር ከሳዑዲ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የአፍሪካ ጉዳዮች ዳይሬክተር ጄኔራል ጋር የስንብት ውይይት አካሄዱ
==========================
(ሪያድ: መስከረም 5 ቀን 2018) በሳዑዲ አረቢያ የኢፌዴሪ ልዩ መልዕክተኛና ባለ ሙሉ ሥልጣን አምባሳደር ዶ/ር ሙክታር ከድር በሳውዲ የሥራ ዘመናቸውን በማጠናቀቅ ላይ በሚገኙበት ወቅት ከሳዑዲ አረቢያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር የአፍሪካ ጉዳዮች ዳይሬክተር ጄኔራል አምባሳደር ሳቅር ቢን ሱለይማን አል ቁረሺ ጋር የስንብት ውይይት አካሂደዋል።
ክቡር አምባሳደር ዶ/ር ሙክታር በሳዑዲ አረቢያ በነበራቸው የሥራ ቆይታ ወቅት ከሳዑዲ አረቢያ ውጭ ጉዳይ ሚኒስቴርና በተለይም ከአፍሪካ ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት ጄኔራል የተደረገላቸውን ትብብርና ድጋፍ በማድነቅ ልባዊ ምስጋናቸውን አቅርበዋል።
ክቡር አምባሳደር ዶ/ር ሙክታር በተለይም አምባሳደር ሳቅር ለኢትዮጵያና ለሳዑዲ አረቢያ የጋራ ግንኙነት ማደግና መጠናከር ላሳዩት ትብብርና ልዩ ትኩረት አድናቆታቸውን ገልጸዋል።
ክቡር አምባሳደር ዶ/ር ሙክታር ይህ የስንብት ውይይት የሁለቱ አገራት የረጅም ጊዜ ወዳጅነትና ትብብር የሚያሳይ መሆኑን ጠቁመው፣ በሥራ ዘመናቸው የተገነቡት ጠንካራ የሥራና የመተማመን ግንኙነቶች ወደፊትም ለቀጣይ ትብብር ጠንካራ መሠረት እንደሚሆኑ ጠቁመዋል።
በተጨማሪም በሁለቱ አገራት መካከል ያለው ታሪካዊ፣ ጂኦግራፊያዊና ባህላዊ ቅርበት በመነሳት የሁለትዮሽ፣ የኢኮኖሚ፣ የፖለቲካ እና የሕዝብ ለሕዝብ ግንኙነቶች በቀጣይም ይበልጥ እንዲጠናከሩ በጋራ መሥራት እንደሚገባ ገልፀዋል።
አምባሳደር ሳቅር ቢን ሱለይማን አል ቁረሺ በበኩላቸው አምባሳደር ዶ/ር ሙክታር በሳዑዲ አረቢያ በነበራቸው የሥራ ዘመን የሁለቱን አገራት ግንኙነት በማጠናከር ላደረጉት ጥረትና አስተዋጽኦ ምስጋና አቅርበዋል።
አምባሳደር ሳቅር በተለይም የኢትዮጵያን የልማት እንቅስቃሴና በቀጠናው ሰላምና መረጋጋት ለማስፈን እያሳየች ያለችውን ቁርጠኝነት አድንቀው፣ በሁለቱ አገራት መካከል ያለው የተለየ ወዳጅነትና ትብብር ወደፊትም እንደሚጠናከር ገልጸዋል።
በመቀጠልም በጋራ የልማት፣ የሰላምና የደህንነት ጉዳዮች ላይ ቅርበት በመፍጠር ለመሥራትና የተጀመሩ የትብብር ሥራዎችን በቀጣይ ለማጠናከር መግባባት ላይ ደርሰዋል።
በመጨረሻም ክቡር አምባሳደር ሳቅር ቢን ሱለይማን አል ቁረሺ አምባሳደር ዶ/ር ሙክታር በቀጣይ በሚኖራቸው የሥራ ስምሪት ስኬታማ እንዲሆኑ ያላቸውን መልካም ምኞት ገልጸዋል።MFAEthiopia Amharic የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴርFBC (Fana Broadcasting Corporate S.C.)Ethiopian Press Agency /የኢትዮጵያ ፕሬስ ድርጅት/Ethiopian Broadcasting CorporationEthiopian News AgencyThe Ministry of Foreign Affairs of EthiopiaEthiopian Diaspora Service