25/06/2026
በጅዳ የኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ ት/ቤት የቅድመ-መደበኛ ትምህርት እና የ12ኛ ክፍል ማጠናቀቂያ የተማሪዎች ምረቃ በዓል ተካሄደ፣
(ሰኔ 18 ቀን 2018 ዓ.ም፣ ጅዳ) በጅዳ የኢትዮጵያ ዓለም አቀፍ ት/ቤት የቅድመ መደበኛ ትምህርት ማጠናቀቂያ ፕሮግራም ሰኔ 15 ቀን 2018 ዓ.ም እንዲሁም የ12ኛ ክፍል ተማሪዎች ምረቃ በዓል ሰኔ 17 ቀን 2018 ዓ.ም በጅዳ በድምቀት ተካሄደ። በፕሮግራሙ ላይ የት/ቤቱ የትምህርት አመራር ቦርድ አመራር እና አባላት፣ የት/ቤቱ ርዕሰ መምህር እና ማኔጅመንት አባላት፣ መምህራን እና ሰራተኞች፣ የተመራቂ ወላጆች እንዲሁም ተመራቂ ተማሪዎች በተገኙበት በድምቀት ተካሂዷል።
በፕሮግራሞቹ ላይ በጅዳ ቆንስላ ጀኔራል ጽ/ቤት ምክትል ቆንስል ጀኔራል እና የቆንስል ጀኔራሉ ተወካይ የሆኑት አቶ ለዓለም ጥላሁን ባስተላለፉት መልዕክት የትምህርት ዓላማ እውቀትን እና ክህሎትን ማስጨበጥ ብቻ ሳይሆን የተሟላ ስነምግባርና ጠንካራ ስብዕና ያለው ዜጋ መቅረጽ መሆኑን ጠቅሰው፣ ምሩቃን ለውጤት እንዲበቁ አስተዋጽኦ ላበረከቱ የትምህርት ቤቱ ማህበረሰብ አባላት እና ወላጆች ምስጋና አቅርበዋል። በቀጣይም የመማር መስተማሩ ተግባር ስኬታማ እንዲሆን የሚመለከታቸው ባለድርሻ አካላት በሙሉ ከት/ቤቱ የትምህርት አመራር ቦርድ እና የማኔጅመንት አባላት ጋር በመቀናጀት የበኩላቸው አስተዋጽኦ እንዲያበረክቱ ጠይቀዋል። በማስከተልም ቆንስላ ጄነራል ጽ/ቤቱ ት/ቤቱ የተጣለበትን ኃላፊነት በስኬት እንዲወጣ በመጪው 2026/27 የትምህርት ዘመን ከት/ቤቱ ቦርድ፣ የማኔጅመንት አባላት እንዲሁም የተማሪ ወላጆች ጋር ያለውን ጠንካራ ግንኙነት አጠናክሮ እንደሚቀጥል አረጋግጠዋል። በመልዕክታቸው ማጠናቀቂያ ላይ ለኢትዮጵያውያን የ12ኛ ክፍል ተመራቂ ተማሪዎች ባስተላለፉት መልዕክት በቀጣይ የትምህርት እና የስራ ህይወታቸው የዲጅታሉ ዓለም የፈጠረላቸውን ዕድል በመጠቀም የሀገራቸው ኢትዮጵያን ባህል እና መልካም ዕሴቶች እንዲሁም የኢትዮጵያን መልካም ገጽታ እንዲያስተዋውቁ ጠይቀዋል። በመጨረሻ ላይም ለተመራቂ ተማሪዎች የምስክር ወረቀት ተሰጥቶ ፕሮግራሙ ተጠናቋል።