05/07/2023
ያልተቋጨው ጉዞ!.....
=========================
ዕለቱ የካቲት 17 ቀን 2014 ዓ.ም. አንዳቤት ወረዳ ሽሜ ሞሻ ቀበሌ፣ የአካባቢው ማህበረሰብ በስራ ላይ ተጠምዷል ግማሹ በተፈጥሮ ሃብት ልማት ፣ ግማሹ በእርሻ ስራ ላይ ተስማርቶ ሁሉም እንደየ ስራው ባህሪ የየግል ስራውን ያከናውናል። በአካባቢው ያሉ ህጻናትም በበኩላቸው ከብቶችን ሲጠብቁ፣ በጫካው እና በየሸንተረሩ ሲጫወቱ ይስተዋላል። እንዲህ እየሆነ የእኩለ ቀኑ ሰዓት ደረሰ። ሰዓቱ ከቀኑ 6፡00 ሰዓት ነው። ከዚሁ ቀበሌ እግዚአብሔር አብ ተብሎ ከሚጠራው ስፍራ። ስራ ላይ የቆየው ማህበረሰብ ለምሳ ሰዓት ወደየቤቱ እየሄደ ነው። በአካባቢው የነበሩ ህጻናት በጫካው እንደ ነገሩ ያገኙትን እንጨት እየለቀሙ ነበር። ከጫካው እንጨት ሲለቅሙ እስካሁን ያልተለመደ አዲስ ነገር አገኙ በፎጣ የተሸፈነ ጫካ ውስጥ ተኝቶ የተገኘ ሰው። ይህ ሰው ምን ሆነ? ቀርበው ለማየት ፍርሃት ቢያድርባቸውም እንደምንም ብለው ቀርበው ሲመለከቱት ፊቱ እና አፍንጫው አካባቢ ጉዳት የደረሰበት ሞቶ የተገኘ ሰው። በሁኔታው ተደናግጠው ሰው እንዲደርስላቸው ጩኸት ሲያሰሙ የአካባቢው ማህበረሰብ ደርሶ ማንነቱን ማወቅ ያልቻሉት ሰው ሞቶ የተገኘ መሆኑን ለቀበሌያቸው የኮ/ፖሊሲንግ ኦፊሰር በስልክ እንዲደርስላቸው አሳውቀው። የቀበሌው ፖሊስ ኦፊሰርም ወዲያውኑ ፈጥኖ ደርሶ ሰው መሞቱን ካረጋገጠ በኋላ ለወረዳ ፖሊስ ጽ/ቤት መርማሪ ፖሊስ እንዲደርስለት በሪፖርት አሳወቀ። ጉዳዩን የደረሰው የምርመራ ክፍል ፖሊስ ወደ ቦታው በመሄድ ከወንጀል ስፍራው ሲያጣራ የሟችን ማንነት ማወቅና መለየት አልቻለም። መታወቂያም ሆነ ማንነቱን የሚገልጽ መረጃ ማግኘት አልቻለም ነገሩ ግራ የሚያጋባ ነውለአካባቢው ማህበረሰብም ትልቅ ጥያቄ ሆኖበታል። ትንሽ እንደቆየ ከስፍራው ብጫቂ ወረቀት አገኘ። ነጠላ ስም የያዘች፣ የሟችን ይሁን የተጠርጣሪ ማንነትን ግን ማግኘት አልተቻልም ነገሩ አወዛጋቢ ነው።
የካቲት 22 ቀን 2014 ዓ.ም. ለፖሊስ አዲስ ጥቆማ ደረሰው የሟችን ማንነት የሚገልጽ ። ሟች ባምላኩ አለባቸው ገላዬ ከተወለደበት አንዳቤት ወረዳ ደረባ ቀበሌ ከ6 ዓመት በላይ ይኖር የነበረው በኦሮምያ ክልል ውስጥ ነው። የሚተዳደረውም በጉልበት ስራ ሆኖ በቀን የሚያገኛትን ገቢ በባንክ እየቆጠበ እንደሚያስቀምጥ ትንሽ ወንድሙ ያስረዳል።
ሟች እንዴት ከኦሮሚያ ክልል መጥቶ ሞተ?
ለሟች የአክስቱ ልጅ የሆነው የሚኖረው አንዳቤት ወረዳ አንዳቤት ከተማ ውስጥ ነበር ምንም ዓይነት የመተዳደሪያ መስክ የለውም። ለቀን ስራ በሚል ሟቹ ካለበት ወደ ኦሮሚያ ክልል ይሄድና ሟች ባምላኩ አለባቸውን ያገኘዋል። ሟችም ወንድሜ እንኳን መጣህልኝ ብሎ በደስታ ከተቀበለው በኋላ ለሳምንታት ቆይተው ሟችን ቤተሰቦቹ ደካማ ስለሆኑ መጠየቅ እንዳለባቸው ተነጋግረው ፣ ሟችም ቤተሰቦቹን መጠየቅ እንደሚፈልግና ከአክስቱ ልጅ ጋር አብረው ወደ አንዳቤት እንደሚሄዱ ጋምቤላ ላለው ትንሽ ወንድሙ በስልክ ነግሮት ጉዞ ይጀምራሉ። ከሟቹ ገንዘብ እንዳለው የተረዳው የአክስት ልጅ የሆነው አዲስ አበባ ሲደርሱ "ወንድሜ ያጠራቀምከውን ገንዘብ በባንክ አስገባልኝ እና ቦታ ልግዛልህ" ብሎ ያታልለዋል። ወንድሜ ስጋየ ነው ብሎ ያመነው ሟች ለተጠርጣሪው በአካውንቱ 430000 ብር (አራት መቶ ሰላሳ ሽህ ብር) ያስገባለታል። ለሶስት ቀናት አብረው ሲጓዙ ከሰነበቱ በኋላ አንዳቤት ከተማ ሽሜ ሞሻ ቀበሌ ሲደርስ የካቲት 16 ቀን 2014 ዓ.ም. ገዳይ የሆነው የአክስት ልጅ ገና ከቤተሰቦቹ ሳይደርስ ሟች ባምላኩ አለባቸው የተባለውን ከመንገድ ጫካ ውስጥ እንደገደለው ለፖሊስ ጥቆማ ይደርሰዋል።
ይህንን ጥቆማ የደረሰው ምርመራ ቡድን የተለያዩ የቴክኒክ፣ የሰው፣ የሰነድና የኤግዚቪት ማስረጃዎችን በስፋት አስደግፎ በተጠርጣሪ ማማሩ/ክንዳለም ሃይሌ በተባለው ምርመራውን አጣርቶ ለሚመለከተው የፍትህ አካል ይልካል። ጉዳዩን የተመለከተው የደቡብ ጎንደር ዞን ፍትህ መምሪያ በተጠርጣሪው ክስ መስርቶ ሲያከራክር ከቆየ በኋላ የደ/ጎንደር ዞን ከፍተኛ ፍ/ቤት ዛሬ ሰኔ 28 ቀን 2015 ዓ.ም. በዋለው ችሎት በተከሳሽ ማማሩ/ክንዳለም ሃይሌ ላይ ራሱንም ያስተምራል ሌላውንም ማህበረሰብ ያያስጠነቅቃል በሚል የ20 ዓመት ጽኑ እስራት የወሰነበት መሆኑን መረጃው ያስረዳል።