15/06/2026
በሀዲያ ዞን ሌሞ ወረዳ ከ60 ሚሊዮን ብር በላይ ገንዘብ ተመድቦ የለምቡዳ ንፁህ የመጠጥ ውሃ ጉድጓድ ቁፋሮ ተጀመረ ።
ሰኔ 08/2018ዓ.ም(ወልቂጤ)
ወርልድ ቪዥን ኢትዮጵያ የሌሞ አካባቢ ፕሮግራም በሌሞ ወረዳ የሶስት ቀበሌያት ህብረተሰብን ተጠቃሚ የሚያደርግ የከርሰ ምድር ንፁህ የመጠጥ ውሃ ጉድጓድ ቁፋሮ አስጀመረ ።
ወርልድ ቪዥን ኢትዮጵያ የሌሞ አካባቢ ፕሮግራም አስተባባሪ አቶ አበባአየሁ ጩማ እንደገለጹት የተጀመረው ዘላቂ የከርሰ ምድር ውሃ ፕሮጀክት ግንባታው ሙሉ በሙሉ ሲጠናቀቅ ከ20 ሺህ በላይ የአከባቢውን ህብረተሰብ ተጠቃሚ እንደሚያደርግና ግንባታው ተጀምሮ እስከ ሚጠናቀቅም ከ60 ሚሊየን በላይ ገንዘብ ተመድቦ ወደ ስራ መገባቱንና ፕሮጀክቱም በሶስት ዓመት ውስጥ ተጠናቆ ለሕዝብና ለመንግስት ርክብክብ እንደሚደረግ ገልፀው ለስራው መሳካትም ከማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ጀምሮ እስከ አካባቢው ነዋሪዎች ከጎናቸው እንዲሆኑ ጠይቀዋል።
የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ውሃ መስኖና ማዕድን ልማት ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ሙላቱ ጡሞሮ ወርልድ ቪዥን ኢትዮጵያ ስራውን በተያዘለት የጊዜ ገደብ በጥራት እንዲያጠናቅቅ ቢሮው የቅርብ ክትትልና ድጋፍ እንደሚያደርግ አስታውቀው ወርልድ ቪዥን ኢትዮጵያ ሶስቱን ቀበሌያት ተጠቃሚ ለማድረግ የከርሰ ምድር ንፁህ የመጠጥ ውሃ ጉድጓድ ቁፋሮ በማስጀመሩ አመስግነዋል ።
የሌሞ ወረዳ ዋና አስተዳደሪ አቶ ታደለ ደምሴ እንደተናገሩት ለምቡዳ ላይ የተጀመረው የከርሰ ምድር ውሃ ቁፋሮ ሲጠናቀቅ የለምቡዳ፣የማስቢራንና የጎራ ጡሜን ህብረተሰብ ተጠቃሚ እንደሚያደርግና የወረዳውን አማካይ የመጠጥ ውሃ ሽፋንም ከ7 እስከ 10 በመቶ እንደሚያሳድግ ገለጸው ፕሮጀክቱ ከሶስት ዓመት ቀድሞ እንዲጠናቀቅም የአከባቢው ማህበረሰብን ጨምሮ የወረዳው መንግስት አስፈላጊውን ድጋፍና ትብብር ያደርጋል ብለዋል።
በማስጀመሪያ ስነ ሥርዓቱ ላይ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ውሃና ማዕድን ቢሮ ምክትል ኃላፊ አቶ ሙላቱ ጡሞሮ፣ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ኢንቨስትመንትና ኢንደስትሪ ልማት ቢሮ ምክትል ኃላፊና የኢንቨስትመንት ዘርፍ ኃላፊ አቶ አሼቦ ኡሊሶ፣የሌሞ ወረዳ ከፍተኛ አመራሮችን ጨምሮ ሌሎች የቀበሌ አመራሮችና የአካባቢው ነዋሪዎች ተገኝተዋል።
የወረዳው መንግስት ኮምኒኬሽን ዘግቧል ።