16/09/2026
በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል በተለያዩ ከተሞች የመሰረተ ልማት አውታሮች ተደራሽነት አፈጻጸም ላይ ያተኮረ የምክክር መድረክ ተካሄደ
መስከረም 6/2019)በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የኢትዮጵያ ኤሌክትሪክ ኃይል አገልግሎት እና በኢትዮ ቴሌኮም ተቋማት አፈጻጸም ላይ ያተኮረ መድረክ በዱራሜ፣በወራቤ፣በሀላባ፣እና በሳጃ ከተሞች ተካሂዷል።
የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳደር ልዩ አማካሪ ንጉሴ አስረስ (ዶ/ር) እንደተናገሩት፣ የኃይል እጥረትና መቆራረጥ በከተሞች ዲጂታል ትራንስፎርሜሽንና ልማት ትልቅ ማነቆ መሆኑን ገልጸው፣ ችግሩን በዘላቂነት ለመፍታት የተቀመጡ አቅጣጫዎችን አስተላልፈዋል።
የመሰረተ ልማት አውታሮችን ከስርቆትና ውድመት የመጠበቅ፣ በየደረጃው ከህብረተሰቡና ከአመራሩ ጋር የውይይት መድረኮችን የማመቻቸት እንዲሁም በኤሌክትሪክ መስመሮች ላይ ተግዳሮት የሆኑ ዛፎችን በኮማንድ ፖስት አስተባባሪነት እልባት መስጠት እንደሚገባም ጠቅሰዋል።
የተቃጠሉ ትራንስፎርመሮችን የመተካት፣ አገልግሎቱን አስተማማኝ ለማድረግ የሚያስችሉ የቅድመ ጥገና ሥራዎችን የማከናወን እና የኃይል መቆራረጥ ችግሮችን መፍታት የሚያስችል መድረክ መሆኑንም አብራርተዋል።
ከኢትዮ ቴሌኮም የአገልግሎት ጥራትንና ተደራሽነትን ከማረጋገጥ አንጻር ተቋሙ የኔትዎርክ መሠረተ ልማቶችን ደረጃ የማስፋፋትና የማሻሻል ተግባራት ላይ በትኩረት እየሰራ እንደሚገኝ ተጠቁሟል።
በተለይም በከፍተኛ ሁኔታ እየጨመረ የመጣውን የደንበኞች ቁጥርና የዳታ ፍላጎት ለማስተናገድ የሚከናወኑ የኔትዎርክ አቅም ማሳደጊያ ሥራዎች፣ የትራፊክ መጨናነቅ በሚበዛባቸው አካባቢዎች የሚፈጠሩ የአገልግሎት መቋረጦችንና የጥራት መውደቅን በዘላቂነት መፍታት የሚያስችል መድረክ መሆኑም ተመላክቷል።
የክልሉ መንግስት ኮምኒኬሽን