12/06/2026
ኢትዮጵያ መርጣለች ! ኢትዮጵያ አሸንፋለች!
"ከምርጫ ድል ማግስት ፣ ጠንካራ መንግሥት" በሚል መሪ ቃል የሲዳማ ክልል አመራሮች የ7ተኛውን ጠቅላላ የምርጫ ሥራዎች አፈጻጸም እና የድህረ ምርጫ ሥራዎች ዕቅድ ላይ ውይይት እያካሄዱ ይገኛሉ።
በሲዳማ ክልል በየደረጃው የሚገኙ አመራሮች በ7ኛው ሀገራዊ ምርጫ የተያዙ መንትያ ግቦችን ስኬታማ ለማድረግ የተከናወኑ ዋና ዋና ተግባራት እና ቀጣይ በድህረ ምርጫ መከናወን በሚገባቸው አንኳር የልማትና የፖለቲካ ስራዎች ላይ የጋራ ተግባቦትን የሚፈጥር መድረክ እየተካሄደ ይገኛል።
የሲዳማ ክልል ርዕሰ መስተዳድር አቶ ደስታ ሌዳሞ በውይይቱ ላይ እንደተናገሩት 7ኛው ሀገራዊ ምርጫ የኢትዮጵያ አሸናፊነት የተበሰበረበት እና የሕዝባችን የነቃና ዴሞክራሲያዊ ተሳትፎ በግልጽ የተንጸባረቀበት በመሆኑ ልዩ ያደርገዋል በማለት የምርጫውን መንትያ ግቦች ባሳካ መልኩ እንደ ክልል የተከናወኑ ተግባራት እጅግ አስደሳችና አበረታች ናቸው ብለዋል።
ምርጫውን የመራንበት ስኬታማ መንገድ፣ ከምርጫው ማግስት የሕዝባችንን ሁለንተናዊ እርካታና ተጠቃሚነት በላቀ ደረጃ በሚያረጋግጥ መልኩ በቁርጠኝነት የምንቀጥልበት ይሆናል በማለት ተናግረዋል።
የሲዳማ ክልል ብልፅግና ፓርቲ ቅ/ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ አብርሃም ማርሻሎ በበኩላቸው እንደገለጹት ሀገራዊ ምርጫው የኢትዮጵያን ዲሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ ወደ ላቀ ደረጃ ያሸጋገረ ታሪካዊ ምዕራፍ መሆኑን በመግለጽ አመራሩ በምርጫው ወቅት የታየውን ሕዝባዊ መነሳሳትና ቁርጠኝነት በመጠቀም፣ የተጀመሩ የልማትና የመልካም አስተዳደር ስራዎችን ይበልጥ በማጠናከር የሕዝቡን ተጠቃሚነት ማረጋገጥ እንደሚገባው አሳስበዋል።
የመድረኩ ዓላማም በ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ወቅት የተከናወኑ ስኬታማ ተግባራትን መገምገምና ተሞክሮዎችን በማስቀጠል በድህረ-ምርጫ ወቅት በሚከናወኑ አንኳር የፖለቲካና የልማት ስትራቴጂዎች ላይ በአመራሩ መካከል ወጥ የሆነ ግንዛቤ በመያዝ የሕዝብን አመኔታ ያተረፈ፣ ቀልጣፋና ተደራሽ የአገልግሎት አሰጣጥ ሥርዓትን በመዘርጋት የብልፅግና ጉዞን ማፋጠን መሆኑን አቶ አብርሃም ማርሻሎ ገልጸዋል።
የክልሉ አመራሮች በቀረቡት አጀንዳዎችና የቀጣይ የትኩረት አቅጣጫዎች ላይ በስፋትና በጥልቀት በመወያየት ላይ ይገኛሉ።