14/04/2026
በሁምቦ ወረዳ የ7ኛው ሀገራዊ ምርጫ የመራጮች ምዝገባ በወጣቶች ንቁ ተሳትፎ በላቀ መነሳሳት እየተከናወነ ይገኛል
ሁምቦ፤ ሚያዝያ 6/2018 ዓ.ም በወላይታ ዞን በሁምቦ ወረዳ 7ኛው ሀገራዊ ጠቅላላ ምርጫ ፍጹም ሰላማዊ፣ ዴሞክራሲያዊ እና ተአማኒ ሆኖ እንዲጠናቀቅ ታስቦ እየተከናወነ ያለው የመራጮች ምዝገባ ሂደት በወጣቶች አደረጃጀት መሪነት ተጠናክሮ መቀጠሉ ታወቀ።
በወረዳው ስር በሚገኙ ሁሉም የምርጫ ጣቢያዎች የሚካሄደው ይህ የምዝገባ ሂደት፣ ወጣቱ የሀገር ግንባታ ባለቤትነቱን በተግባር እያረጋገጠበት የሚገኝ መድረክ ሆኗል። የወረዳው ወጣቶች በ"1 ለ 10" እና በ"1 ለ 3" አደረጃጀቶቻቸው አማካኝነት መራጩ ሕዝብ ወደ ምርጫ ጣቢያዎች በመሄድ የመራጭነት ካርዱን እንዲወስድ የቀስቃሽነትና የአስተባባሪነት ሚናቸውን በከፍተኛ ኃላፊነት እየተወጡ ይገኛሉ።
የወረዳው የወጣቶች ክንፍ አመራሮች እንደገለጹት፣ ወጣቱ በምርጫ ጣቢያዎች አካባቢ ያለውን የፀጥታ ሁኔታ ከመጠበቅ ጀምሮ፣ አረጋውያንና አካል ጉዳተኞች ወደ ምዝገባ ጣቢያዎች መጥተው ካርዳቸውን እንዲወስዱ አስፈላጊውን ድጋፍ እያደረገ ነው። በተለይም በገጠር ቀበሌዎች የሚገኘው መራጭ ሕዝብ ስለ ምርጫው አስፈላጊነትና ድምፅ የመስጠት መብቱ ያለውን ግንዛቤ ለማሳደግ በየቤቱ የሚደረገው ቅስቀሳ ውጤታማ መሆኑ ተጠቁሟል።
ይህ የምዝገባ ሂደት ስኬታማ መሆን የኢትዮጵያን የዴሞክራሲ ሥርዓት ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር የሚደረገውን ጥረት የሚያግዝ ሲሆን፣ የወረዳው ነዋሪዎችም የወጣቱን ጥሪ ተቀብለው በነቂስ በመውጣት ካርዳቸውን እየወሰዱ ይገኛሉ። የምዝገባ ሂደቱ በሁሉም ጣቢያዎች ያለምንም የፀጥታ ስጋትና በታላቅ የሕዝብ ተሳትፎ እየተከናወነ መሆኑ የወረዳውን ሰላማዊነትና የሕዝቡን የፖለቲካ ንቃት የሚያሳይ መሆኑ ተገልጿል።
በቀሪዎቹ የምዝገባ ቀናትም ማንኛውም ዕድሜው ለምርጫ የደረሰ ዜጋ ካርዱን በመውሰድ ዜጋዊ ግዴታውን እንዲወጣና ለሀገሪቱ ብልጽግና የበኩሉን አሻራ እንዲያኖር ጥሪ ቀርቧል።
!!