16/10/2021
መንግስት ግን ቂጥ አለው?
በጥላሁን ስንታየሁ
ዛሬ ትንሽ የአእምሮን ማጀት የሚፈትሽ ጥያቄ ይዤ የተነሳሁ ይመስለኛል፡፡ ስለ መንግስት
ቂጥ…. አዎ ጥያቄው ለእኔ አልያም ለአንተ እርባና ባይኖረውም ለአንድ ለተበሳጨ፣ ግራ
ለተጋባ፣ የአእምሮው ጓዳ በጥያቄ ለተሞላ፣ በተስፋ መቁረጥ ውስጥ ላለ ግለሰብ ግን
የህልውና ጥያቄ ነው፡፡…. ጠያቂው ይጠይቃል መንግስት ግን ቂጥ አለው?.... ይሄ ጥያቄ
ፈገግ አስብሎም ግራም አጋቶኝ አድሯል፡፡…. በተደጋጋሚ ወደ ህሊናዬ እየመጣ እንቅልፍም
ነስቶኛል፡፡ መንግስት ልብ አለዎይ? አቅም አለውዎይ? ጉልበት እና ብርታ አለውዎይ?
ወታደራዊ ሀይል አለዎይ? ዜጎቹን መጠበቅ ይችላዎይ? ተብሎ ይጠየቃል እንጅ እንዴት
ቂጥ አለው ወይስ የለውም ተብሎ ይጠየቃል?
ለመንግስትስ የቂጥ መኖር አለመኖር የህልውናው ጉዳይ ይሆን? ብቻ አላውቅም ዘንድሮ
ህልውና የምትለዋ ቃል ምግብ እና መጠጣችን ሆናስ አይደል!...... መንግስትስ ቂጥ
ቢኖረው ሚዲያዎቻችን ምን ብለው የሚዘግቡ ይመስላችኋል? እኔ ግን እንዲህ እና
እንዲያ እያሉ የሚያወጉ ይመስለኛ፡-
# ኢቢሲ ፡- የጆ ባይደን መንግስት በሀገራችን ላይ እያደረሰ ያለው ጫና ለአሸባሪው ቡድን
ከለላ ለመስጠት እና የመንግስትን ቂጥ ሆን ብሎ ለማኮሰስ እንደሆነ የአዲስ አበባ
ዩኒቨርሲቲ ሙሁራን ገለጹ፡፡
# ፋና ፡- ዜጎች የመንግስት ቂጥ እንዳይነካ እና እንዳይደፈር ለማድረግ በግንባር ቀደምነት
ከፊት ተሰልፈው መስራት እንዳለባቸው እና የመንግስትን ቂጥ ላላስፈላጊ እንግልት እና
መጎሳቆል ሊዳርጉ የሚችሉ ነገሮች ሲያጋጥሟቸው ለሚመለከተው አካል በማሳወቅ
የዜግነት ግዴታቸውን ሊወጡ እንደሚገባ ተገለጸ፡፡
# ትግራይ_ቲቪ ፡- የፋሽሽቱ የዓብይ አህመድ መንግስት በትግራይ ህዝብ ላይ እየፈጸመ
ያለው እልቂት ለአንዴ እና ለመጨረሻ ጊዜ እንዲያበቃ በማለት የትግራይ ሰራዊት በወሰደው
መጠነ ሰፊ የማጥቃት ዘመቻ የፋሽሽቱ መንግስትን የግራ እና የቀኝ ቂጥ ለአንዴ እና
ለመጨረሻ ጊዜ መደምሰስ ተቻለ፡፡
ብቻ ሚዲያዎቻን እንዲህ እያሉ የሚዘግቡ የመስለኛል፡፡ ግን መንግስት ቅጥ አለው? ብቻ
አላውቅም ሊኖረውም ላይኖረውም ይችላል፡፡ ካለውስ በየትኛው አቅጣጫ? በስተ ሰሜን
ወይስ በስተ ደቡብ? በስተ ምስራቅ አልያስ በስተ ምዕራብ? የመንግስት ቂጥ መገኛው
በየትኛው አቅጣጫ ነው? ትልቅ ነው ወይስ ትንሽ? እኔ ግን ትልቅ ብቻ ግዙፍ የሚባለው
አይነት ይመስለኛ፡፡ አለ አይደል ከመቀመጫው የሚበልጥ መቀመጫ ይመስለኛ፡፡ ብቻ
እንጃ ጠያቂው ግን ይጠይቃል፡፡
አብዮት ነው፡፡ ጢንቢራቀው እስኪወጣ ድረስ ስክር ብሎ ሰክሯል፡፡ ከግራ ወደ ቀኝ፣ ከቀኝ
ወደ ግራ፣ ከላይ ወደ ታች፣ ከታች ወደ ላይ ብቻ እግሩ መርገጥ እስከቻለበት ድረስ እረገጠ
ሄድ መለስ ይላል፡፡ እኛ ገና ልጅ ሳለን እማዬ እና አባዬ የአብዮትን ወንድም እና እህቶች ፣
እናት እና አባቱን የደርግ አብዮት እንደገደላቸው ያጫውቱን የነበረው ትዝ ይለኛል፡፡ የደርግ
አብዮት ጨካኝ ነው፡፡ የሰፈራችንን አብዮት ሰካራም እና ዘር የለሽ አድርጎታል፡፡
ይወናጨፋል፣ ይውረገረጋል፣ በደመና አልቦታል እሱም ድምጹን ከፍ አድርጎ ``ደም……
መና`` ይላል፡፡ አየሩ ደመና ነው፡፡ ደሙም ደም-መና ነው፡፡…. ``ደም-መና`` ሲል ወደቀ፡፡
መሬቱ ላይ ያለው ድንጋይ አናቱን አገኘው፡፡ ደሙ ፈሰሰ እሱ ግን ደሙን እየጠረገ ተነስቶ
ቆመና….``መሬ…ቱ ባይኖር….ኖሮ….. ወድቄ ነበር፡፡`` አለ፡፡ በግራ እጁ አንዲት አነስተኛ
ሰንጢ ቢጤ ጨብጧል፡፡ ወደ ፊት ሰንዘር ያደርጋታል፡፡
የቀኝ እጁን አውራ ጣት ጥፍር ለማያየው ሰው ለማሳየት እየሞከረ ``ይታይሃል ይሄ ቀለም
የሰኔ አስራ አራቱ ማህተም ነው፡፡…. በቅጡ እንኳን አልደረቀም፡፡…. አይገርምህም ቀለሙ
ሳይለቅ…. ስንት ዜጋ…. ላይመለስ ለቀቀ….ዜ……..ጋ………ዜ…….ጋ……ዜ….``
አብዮት ላይ እልህ፣ ቁጭት፣ አልሸነፍ ባይነት….. ብቻ የተዘበራረቀ ስሜት ይስተዋላል፡፡
እንባው ከቃላቶቹ ቀድሞ ይወርዳል፡፡ እልሁን እና ቁጭቱን አስተውሎ ለተመለከተው ሰው
አንድ ብርጌድ ጦር የመመለስ አቅም ያለው ይመስላ፡፡ አብዮት ንግግሩን ቀጠለ፡፡
``እኔ…. ተስፋ ቆርጫለሁ…. ተስፋዬስ ማን ሊሆን ይችላል?....... እግዜሩ? አይመስለኝም
እሱስ ተስፋ ላለመቁረጡ ምን ዋስትና አለን?..... ምንም፡፡…… መንግስትስ ማን
ነው?..... የአብዮትን ዘር ማዘር አብዮቱ በላቸው፡፡…… የተረፉት ዘሮቼን በሰሜን እና
በወለጋ እንደ ቆሎ ቆሏቸው!!...... እህ…..እህ….``
እንባው ቁልቁል እየወረደ ንግግሩን ቀጠለ፡፡
``እናቱን መንግስት……. ድንጋይ ተንተርሶ ድንጋይ በልቶ ይደር…… እናቱን……..ድሆ
ይሂድ…. አጥንቱ ይመንምን….. ወንበሩ እሾህ አሜኬላ ያብቅል…. የንግስናው በትር ከዘር
ማዘሩ እጅ ይውጣ!..... እናቱን….. ይሄን መንግስት በዚህ ሰንጢ ቂጡን መውጋት
ነበር….. አዎ የመንግስትን ቂጡን መውጋት ቢቻል እንዴት ያስደስታል፡፡ …… ዙፋን ላይ
የተቀመጠበትን ቂጡን መውጋት!!...... ዙፋን እዳያሰኘው አድርጎ ቂጡን
መጨቅጨቅ…….``
አብዮት ይህንን ሲል መሳቅም አሰኝቶኝ ነበር፡፡ ግና ሰሜቱን፣ ህመሙን፣ ቁጭቱን ስመለከት
ለማያገኘው የመንግስት ቂጥ የማይመለስ ግለሰብ የእኔን ቂጥ ቢወጋኝስ ብዬ ፈራሁ፡፡ ዳሩ
ቂጥ እንጅ ዙፋን የለኝ፡፡ አብዮት ንግግሩን ወደ ጥያቄ ቀየር አደረገው፡፡
``መንግስት ግን ቂጥ አለው?.... ካለውስ የግራውን ወይስ የቀኙን ቂጥ ልውጋው?......
የመንግስትን ቂጥ ለሚጠቁመኝ ዎረታውን እከፍላለሁ፡፡….. አናንተ ጠቁሙኝ እንጅ
መውጋቱን ለእኔ ተዉት….. ዙፋን ላይ መቀመጥ ቀርቶ በአካባቢው መቆም እንዳያሰኘው
አድርጌ እወጋዋሉ፡፡…. ቂጥ አልባ እስኪሆን ድረስ እጨቀጭቀዋለሁ፡፡…… የዛኔ መቀመጥ
ሲያቅተው ዜጋውን ቆሞ ይጠብቃል፡፡…… ከቂጡ ደም ሲንፎለፎል ለሌሎቹም ደም ጥብቅና
የቆማል፡፡``
አብዮት ወደ ፊት መራመድ ጀመረ፡፡ እኔም የመንግስትን የቂጥ ህልውና ለጭንቅላቴ
እየጠየኩ ባለሁበት ቆሜ ቀረሁ፡፡ እውነት መንግስት ግን ቂጥ አለው?
፡
ጥቅምት 4/2014 ዓ.ም
ሆሳዕና