01/06/2026
በሙስና ወንጀል የተከሰሱ ግለሰቦች በእስራት ተቀጡ
********************
(የአብክመ.ሥ.ፀ.ሙ.ኮ.ደ.ቅ ግንቦት 24/2018 ዓ.ም) በአማራ ክልል በደብረማርቆስ ከተማ አስተዳደር የአብማ ክፍለ ከተማ የሥራ ኃላፊዎች እና ባለሙያዎች ከመሬት ጋር በተያያዘ ሙያቸውንና ስልጣናቸውን ተጠቅመው በፈጸሙት የሙስና ወንጀል 10 ተከሳሾች በእስራት ተቀጥተዋል፡፡
ተከሳሾች፣ የሰነድ አልባ መረጃን በማጽናት እና በማጽደቅ ሂደት የመንግስትን መሬት ለሌላ ግለሰብ አሳልፈው በመስጠት በፈፀሙት የሙስና ወንጀል በቁጥጥር ስር ውለው አስፈላጊውን ምርመራ በማጣራት መዝገቡን ለምስራቅ ጎጃም ዞን አቃቢ ህግ መምሪያ መላክ መቻሉን የከተማ አስተዳደሩ ፖሊስ መምሪያ የሙስና ወንጅሎች ምርመራ ዋና ክፍል ሃላፊ ኮማንደር ጌታነህ አሰፋ ገልጸዋል።
የምስራቅ ጎጃም ዞን አቃቢ ህግ መምሪያ ከፖሊስ የደረሰውን የምርመራ መዝገብ በማደራጀትና ክስ በመመስረት በህግ አግባብ ሲታይ ከቆየ በኋላ የምስራቅ ጎጃም ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት በቀን በ19/9/2018 ዓ,ም በዋለው ችሎት ተከሳሾች ጥፋተኛ መሆናቸው በሰውና በሰነድ ማስረጃ ተረጋግጧል፡፡
በዚህም 1ኛ አቶ አላምር ተስፋዬ፣ 2ኛ ወ/ሮ ሀይማኖት ታሪኩ፣ 3ኛ አቶ መኳንንት ጠለለ፣ 4ኛ አቶ እንዳልካቸው፣ 5ኛ አቶ ተሻለ መብራቴ፣ 6ኛ አቶ ዮሴፍ ጌትነት እና 7ኛ አቶ ስላንተ ጥበቡ እያንዳንዳቸው በሁለት መዝገብ በ10 አመት እስራት ተቀጥተዋል፡፡
8ኛ ወ/ሮ ታሪክ ሞትባይኖር በተለዬ መንገድ ከግለሰቦች ጋር በመመሳጠር የቴክኒክ ኮሚቴውንና የአብይ ኮሚቴውን በማሳመን ለግለሰቦች መብት ከመፍጠር ባሻገር በራሷ ልጆች ስም የመንግስትን መሬት በማዘወር መብት የፈጠረች መሆኑን በማስረጃ በመረጋገጡ በሁለት መዝገብ በ12 አመት እንዲሁም ወ/ሮ ሶሊያና መሀሪና ወ/ሮ አብዮት እጅጉ እያንዳንዳቸው በ3 አመት እስራት መቀጣታቸውን ገልጸዋል።
የሙስና ወንጀል የመልካም አስተዳደር ችግር ከመፍጠሩም በላይ በሀገር ኢኮኖሚ፣ ማህበራዊ እና ፖለቲካዊ ችግሮችን በማስከተል በህዝብ እና በመንግስት መካከል መተማመን እና ተቀራርበው እንዳይሰሩ የሚያደርግ መጥፎ በሽታ በመሆኑ ማንኛውም ህብረተሰብ የሙስና ወንጀል ሊፈፀም መሆኑን ሲያውቅ ወይም ሲመለከት ጥቆማ በመስጠት እና ለህግ ተባባሪ በመሆን የዜግነት ድርሻቸውን መወጣት እንደሚገባ ማሳሰባቸውን ከከተማ አስተዳደሩ ፖሊስ መምሪያ የፌስቡክ ገጽ የተገኘው መረጃ ያመላክታል።
ትውልድን በሥነምግባር፤ ተቋምን በአሰራር!