27/10/2025
የአለም ቱሪዝም ቀን
የዓለም ቱሪዝም ድርጅት (UNWT) በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት በ1963ዓ. ም ተቋቁሟል፡፡ በየዓመቱ መስከረም 17 በዓለም አቀፍ ደረጃ የዓለም የቱሪዝም ድርጅት (UNWT) በተባበሩት መንግሥታት ድርጅት የተቋቋመበት ቀን “የቱሪዝም ቀን” ተብሎ ስያሜውን በመያዝ እንዲከበር መወሰኑ ይታወቃል።
በዓሉ ሀገራት ለቱሪዝም ዘርፍ ተገቢውን ትኩረት በመስጠት ቱሪዝም በሚያስገኘው ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ማኅበራዊ አስተዋፅኦ ተጠቃሚ እንዲሆኑ የማነሳሳት እና ግንዛቤ የመፍጠር ከፍተኛ ጠቀሜታ እንዳለው ተነስቷል።
ሀገራችን ኢትዮጵያ የራሷ የሆነ አኩሪ ባህል፣ የተፈጥሮ እና ሰው ሰራሽ ቅርሶች መገኛ ናት ያሉንን ቅርሶች መጠበቅ ፣ በማስተዋወቅ ከዘርፉ የሚገኛውን ሀብት ተጠቃሚ ለመሆን መስራትን ይጠይቃል፡፡
ከትኩረት ማነስ የተነሳ የቱሪዝም ፀጋዎቻችን በአግባቡ አልተጠቀምንም በቀጣይ አልሚዎችን በማፈላለግ እና እኛም አስፈላጊውን ድጋፍ በማድረግ ከቱሪዝም ዘርፎች የኢኮኖሚ ተጠቃሚ ለመሆን መስራትን ይጠይቃል፡፡
የዓለም የቱሪዝም ቀን በየዓመቱ የሚከበር በዓል ሲሆን በዓሉን ለማክበር የዓለም የቱሪዝም ድርጅት በየዓመቱ ለበዓሉ የሚሆን መሪ ቃል ያዘጋጃል፡፡ የቱሪዝም ቀን በዓል በየዓመቱ በእኛ አቆጣጠር መስከረም 17/በፈረንጆች አቆጣጠር መስከረም 27 የሚከበር ሲሆን ቀኑ የተመረጠበት ምክንያትም የአለም የቱሪዝም ድርጅት ህገ ደንብ የፀደቀበት እና ወደስራ የገባበት ቀን በመሆኑ ነው ።
የ2018ዓ.ም የዓለም የቱሪዝም ቀን በዓል "ቱሪዝም ለዘላቂ ለውጥ" (Tourism and Sustainable Transformation) በሚል መሪ ቃል በዓለም አቀፍ ደረጃ ለ46ኛ፣በሀገራችን ለ38ኛ፣በክልል ደረጃ ለ33 ጊዜ በተለያዩ ዝግጅቶች ይከበራል፡፡
የቱሪዝም ቀንን ማክበር ስለቱሪዝም ግንዛቤ ለመፍጠር ፣የጉብኝት ልምድን ለማስፋፋት እንዲሁም የቱሪዝም መዳረሻዎችን ለማስተዋወቅ ትልቅ እድል ይፈጥራል ።
የመስህብ ሀብቶቻችንን መጠበቅ እና መንከባከብ የሁላችንም ሃላፊነት ነዉ
የቱሪዝም ሀብቶችን በማስተዋወቅ በኩል ማህበራዊ ሚዲያው ሠፊ ዕድል ስለሚሠጠን የመስህብ ሀብቶቻችንን በማስተዋወቅ እና ጎብኝዎችን በመሳብ ሁላችንም የቱሪዝም አምባሳደር መሆን ይገባናል።
ቱሪዝም ለሀገር እድገት አለኝታ ነዉ፡፡ የመስህብ ሀብቶች የገቢ ምንጮች በመሆናቸው ይዘታዊና ቁሳዊ ባህሪያቸውን ሳይለቁ ለትውልድ ማስተላለፍ ይገባል፡፡ ያልተመዘገቡና ያልተጠኑ ቅርሶችን እዉቅና ቢሰጣቸው እና ያሉትን እድሳትና ጥገና ቢደረግላቸው መልካም ነዉ፡፡
ኢትዮጵያ ካላት እምቅ የቱሪዝም አቅምና መዳረሻዎች አንፃር እያገኘቸው ያለው ጥቅም እጅግ አነስተኛ ነው።
መንግስት ነባራዊ ሁኔታውን ለመቀየርና ዘርፉ በኢኮኖሚው ውስጥ ተገቢውን ድርሻ እንዲይዝ አስቻይ የሪፎርም ሥራዎችን እያከናወነ ነው፡፡
ከአምስት የኢኮኖሚ አውታሮች አንዱ የሆነውን የቱሪዝምን ዘርፍ በከፍተኛ ትኩረት በመምራት የሀገር በቀል ኢኮኖሚ ስትራቴጂ ቁልፍ አካል እንዲሆን እየተሰራም ነው፡፡
ቱሪዝም የአድናቆት ገበያ መሆኑን በመገንዘብ የኢትዮጵያን ቱሪዝም ዓለም ዓቀፍ ተወዳዳሪነትን የሚያሳድጉ ሥራዎች እንዲከናወኑ ይፈለጋል፡፡
የቱሪዝም ምንነት፡-
ቱሪዝም
ሁሉም ባለሙያዎች የተስማሙበት በአለም አቀፍ ደረጃ አንድ ወጥ የሆነ ፍች የለውም፡ምክንያቱም የቱሪዝም ትምህርት /discipline/ገና በማደግ ላይ ያለ በመሆኑ ነው፡፡
ይሁን እንጅ አብዛኛዎቹ ባለሙያዎች የተስማሙበትና በስፋት የሚገለገል ከአለም ቱሪዝም ድርጅት የተሰጠ ፅንስ ሃሳብ አለው፡፡
ይኸውም፡- ቱሪዝም ማለት ሰዎች በተናጠል ወይም በቡድን በመሆን ከመኖሪያ ቀያቸው (አካባቢያቸው) ተነስተው ለተለያዩ ጉዳዮች ከአንድ አመት ላልበለጠና ከአንድ ምሽት (24 ስዓት) ላላነሰ ጊዜ ወደ ሌላ ከማንኛውም ገቢ ማስገኛ ስራ ውጭ የእረፍት ጊዜን ለማሳለፍ፣ ለመዝናናት፣ራስን ለማደስ ፣ ለንግድ ስራ ወይንም ለሌላ ተግባር የሚያደርጉት ጉዞ ነው፡፡
ነገርግን ሁሉም ተጓዦች ጎብኝዎች ሊባሉ አይችሉም ጎብኝዎች ለመባል የተለያዩ መስፈርቶች መሟላት አለባቸው ከእነዚህም መስፈርቶች
1.የጉብኝት አላማ ሲኖር /purposive criterion/
2.ጉብኝቱን የሚያደርገው ተጓዠ ከመኖሪያ አካባቢው ርቆ መሄድ እንዳለበትና ከቱሪስት ተቀባይ ወገን የተለያዩ አገልግሎቶች ሲያገኝ/spatial criterion/
3.የጉብኝት የጊዜ ገደብም/Temporal criterion/ መኖር ያለበት ሲሆን ከአንድ ምሽት ማነስ እንደለሌለበትና ከአንድ አመት መብለጥ እንደሌለበት የዓለም የቱሪዝም ድርጅት ያስቀምጣል፡፡ ከአንድ ምሽት ካነሰ ወይም ከአንድ አመት ከበለጠ ግን ቱሪስት ሳይሆኑ ሌላ ስያሜ ሊሰጣቸው ይችላል፡፡
የቱሪዝም አብይ ክፍሎች ወይንም አካላት
የቱሪዝም አብይ ክፍሎችና (አካላት) የሚባሉት፡- መስህብ፣ መጓጓዣና መስተንግዶ ናቸው፡፡
ሀ. መስህብ
መስህብ ማለት በአንድ አካባቢ የሚገኘ ተፈጥሮ ወይም ሰው ሰራሽ ቦታ (ስፍራ) አልያም ደግሞ ድርጊት (ክስተት) ሲሆን ጎብኝዎችን ከመኖሪያ ቦታቸው ቀስቅሶ ወደ ሌላ አካባቢ እንዲጓዙ የሚያደርግ ነገር ነው፡፡ለቱሪዝም ልማት ወሳኝና ያለመስህብ ሃብትም ቱሪዝም አይታሰብም፡፡የመስህብ ሃብት የቱሪስቶችን የመዳረሻ ምርጫ ለመወሰን የሚቻል የቱሪዝም ምርት አካል ነው፡
በአጠቃላይ፡- መስህብ ማለት የጎብኝዎችን ስሜት የሚስብ ተፈጥሮአዊና ባህላዊ ውጤት የሆነ ማንኛውም ነገር ነው፡፡
ለ. መጓጓዣ
መጓጓዣ ከመዳረሻ ቦታው መዳረሻና ከመዳረሻዎች ውስጥ ለውስጥም ከቦታ ቦታ የመንቀሳቀሻ ዘዴ ነው፡፡ሁኔታውም የአንድ ተጓዥ ቱሪስት ከአንድ ነጥብ ሀ ወደ ሌላ ነጥብ ነጥብ ለ እንቅስቃሴ ላይ ያተኩራል፡፡በአሁኑ ስዓትም መጓጓዝ የመስህብ አካል ሆኖ በመታየት እየጨመረ መጥቷል፡፡
ሐ. መስተንግዶ
በመሰረታዊነት የምግብ፣ የመጠጥና ማረፊያ አገልግሎቶችን የሚሰጡ ተቋማት ናቸው፡፡
በተጨማሪነት ደግሞ የጉብኝትና ጉዞ፣ የቱሪዝም መረጃ፣ የሱቅና ግላዊ አገልግሎቶች፣ የገንዘብ መለዋወጫና የህክምና አገልግሎቶች፣ የስብሰባ አዳራሽና ወዘተ አገልግሎቶች ይሰጣል፡፡
የቱሪዝም ጥቅሞች፡-
የቱሪዝም ምጣኔ ሃብት በጣም ብዙና በቁጥር ሊተመን የማይቻል ቢሆንም በጥቅሉ ግን እንደሚከተለው ማስቀመጥ ይቻላል፡፡
1. ለምጣኔ ሃብት (ኢኮኖሚ) እድገትና የምጣኔ ሃብትን በማብዛትና በማረጋገት ያግዛል፡፡
2. የስራ ዕድል ፈጠራ፣
3. ፍልሰትን በመቀነስ ሰፈርን መልሶ ይተካል፣
4. የህዝባዊ ተቋማት እንዲጠገኑና እንዲሻሻሉ ያደርጋል፣
5. የመሰረተ ልማት ተቋማትን ያሻሽላል፣
6. ዕደ ጥበባት፣ ልማዶችን፣ ወጎችንና ባህልን ይመልሳል፣
7. ማህበራዊ ግንኙነቶችና ልውውጦች እንዲጨምሩ ዕድል ይፈጥራል፣
8. የተፈጥሮና የህንፃ ግንባታዎች አካባቢ እንዲጠበቁና እንዲሻሻሉ ያደርጋል፣
------------------------------------//--------------------------------
"ቱሪዝም ለዘላቂ ለውጥ" (Tourism and Sustainable Transformation)