13/03/2026
የደብረብረሃን አጠ/ስፔ/ሆስፒታል የእውቅናና ሽልማት ፕሮግራም አካሔደ።
የደብረብረሃን አጠ/ስፔ/ሆስፒታል በአገር አቀፍ ደረጃ በተካሄደው በ4ኛው ዙር የሆስፒታሎች ጥምረት ለጥራት/መረጃን መሰረት ያደረገ የህክምና አገ/ሎት ተወዳድሮ የ5ሚሊየን ብር, የወርቅ ዋንጫ እና የሰርተፍኬት ተሸላሚ በመሆኑ የተነሳ የክልል አመራሮች, የዞን አመራሮች ,የተለያዩ ባለድርሻ አካላት በተገኙበት በዛሬው ዕለት ማለትም በ04/07/2018ዓ.ም ለሆስፒታሉ ጠቅላላ ሰራተኞች,ለባለድርሻ አካላት እና ለተገልጋዩ ማህበረሰብ የእንኳን ደስ ያላችሁ እና የሽልማት ፕሮግራም አካሒዷል ።
በመግቢያው ላይ የሆስፒታሉ ሜ/ዳሬክተር ዶ/ር ንጉሴ ተፈራ የዕለቱን ፕሮግራም በማስተዋወቅ የሆስፒታሉን ስራ-አስኪያጅ የፕሮግራሙን ተሳታ እንኳን ደህና መጣችሁ እንዲሉ ጋብዘዋል።
የሆስፒታሉም ሥራ አስኪያጅ አቶ ጥላሁን ሙሉጌታ የፕሮግራሙን ተሳታፊዎች እንኳን ደህና መጣችሁ በማለት በ4ኛው ዙር ሀገር አቀፍ "የሆስፒታሎች ጥምረት ለጥራት" ውድድር በአገር ደረጃ በአንደኝነት ከተቀመጡት አሥር ሆስፒታሎች መካከል የደብረብረሃን አጠ/ስፔ/ሆስፒታል አንዱ ሆኖ የወርቅ ዋንጫ፣ሰርተፍኬት እና የ5 ሚሊዮን ብር እንዲሸለም የሆስፒታሉ ማኔጅመንት እና አጠቃላይ ሠራተኞች ላደረጉት ያላሰለሰ ጥረት አመስግነዋል።
አያይዘውም ለዚህ ውጤት መምጣት ከፍተኛ አስተዋፅኦ ያላቸውን ክልል ጤና ቢሮ፣ደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር፣የሰሜን ሸዋ ዞን አመራሮች እና ሌሎች ባለድርሻ እና አጋር አካላት ላደረጉት ድጋፍ አመስግነዋል።
በመቀጠልም የደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር ምክትል ከንቲባ የተከበሩ አቶ ወርቃለማሁ ኮስትሬ የዕለቱን ፕሮግራም በመክፈት ሆስፒታሉ በሀገር አቀፍ ደረጃ በተደጋጋሚ ተወዳድሮ ተሸላሚ የሆነ አንጋፋ ሆስፒታል መሆኑን አስታውሰዋል።
በዚህ ዓመትም ከአሥር ምርጥ ሆስፒታሎች አንዱ ሆኖ በማጠናቀቁ እንኳን ደስ አላችሁ በማለት ለውጤቱ መገኘት ማኔጅመንቱ እና መላው ሠራተኛ ላደረጉት ከፍተኛ ትጋት በከተማ አስተዳደሩ ስም አመስግነዋል።
ከአሥር ምርጥ ሆስፒታሎች ውስጥ ደረጃ ይዞ ማጠናቀቅ መቻል ትልቅ ስኬት ነው ያሉት፣የደብረ ብርሃን ከተማ አስተዳደር ብልጽግና ፓርቲ ጽህፈት ቤት ሀላፊ አቶ ሰለሞን ጌታቸው ውጤቱ የማናጅመንት አባላትና የጠቅላላ የሆስፒታሉ ሠራተኞች ልፋት ውጤት ነውና እንኳን ደስ አላችሁ ብለዋል።
በጥረታችሁ አኩሪ ድል በማስመዝገባች እንኳን ደስ አላችሁ ያሉት የደብረ ብርሃን ከተማ ጤና መምሪያ ኃላፊ አቶ በቀለ ገብሬ፣ይህ ስኬት የሁሉም ሠራተኛ የልፋትና የድካም ፍሬ ነው ብለዋል።
ከአሥር የወርቅ ዋንጫ ተሸላሚ ሆስፒታሎች ውስጥ 7ቱ ከአማራ ክልል መሆናቸው የክልሉ መንግሥት ለዘርፉ የሰጠው ትኩረት ከፍተኛ መሆኑን የሚያስረዳ እንደሆነ በማንሳት ጤና ቢሮው ላደረገው ድጋፍ አመስግነው፣በቀጣይም የሆስፒታሉ ማኅበረሰብ እንደ አንድ ሰው ተባብሮ በመሥራት ውጤቱን ማስቀጠል ይገባል በማለት መልዕክት አስተላልፈዋል።
በውጤቱ ተደስተናል፣ኮርተናልም ያሉት የሰሜን ሸዋ ዞን ጤና መምሪያ ኃላፊ ወይዘሮ ፀዳለ ሰሙንጉስ፣ደብረ ብርሃን ሆስፒታል ለከተማው፣ለሰሜን ሸዋ ሕዝብ እና ለአጎራባች ክልሎች እየሰጠ ላለው አገልግሎት አመስግነዋል ይህም ውጤት በሰራተኛው ዘንድ የበለጠ መነሳሳት ይፈጥራል ብለዋል።
በመርሃ ግብሩ ላይ የተገኙት የአብክመ ጤና ቢሮ ም/ሃላፊ አቶ መልካሙ ጌትነት የደብረብረሃን አጠ/ስፔ/ሆስፒታል ላስመዘገበው አመርቂ ውጤት አመስግነው ለዚህ ውጤት መምጣት አስተዋፅኦ ያደረጉ አካላትን ሁሉ አመሥግነው በቀጣይም የሆስፒታሉ ሠራተኞች ህዝባቸውን በቅንነት ማገልገል እንዳለባቸው ጥብቅ መልዕክት አስተላልፈዋል።
በመጨረሻም ተግባሩን ላስተባበሩ, ለፈፀሙ, ድጋፍ ላደረጉ ባለሙያዎች, ሠራተኞች, ግለሠቦች እና ተቋማት የዕውቅና እና የምስጋና የምስክር ወረቀት ተበርክቶላቸው መርሐ ግብሩ ተጠናቋል።
መጋቢት/2018 ዓ.ም
ደብረብሃን