30/11/2024
የፍትህ ዘርፍና የዳኝነት ተቋማትን አገልግሎት አሰጣጥ ለማሻሻል የተዘጋጀ የውይይት መድረክ ተካሄደ!
ወራቤ፣ ህዳር 21/2017
የተለያዩ ባለድርሻ አካላት የተሳተፉበትና የስልጤ ዞን ምክር ቤት ከዞኑ የፍትህና የዳኝነት አካላት ጋር በመተባበር ያዘጋጁት የስልጤ ዞን የፍትህ ዘርፍና የዳኝነት ተቋማትን አገልግሎት አሰጣጥ ማሻሻልን ዓላማው ያደረገ የምክክር መድረክ በወራቤ ከተማ ተካሄዷል፡፡
በምክክር መድረኩ ላይ የዞኑን ፍትህ ዘርፍ ተቋማት የአገልግሎት አሰጣጥ ለማሻሻል የተዘጋጀ የመወያያ ሰነድ በስልጤ ዞን ፍትህ መምሪያ ኃላፊ አቶ በረከት ከድር ሲቀርብ በሌላም በኩል በዞን ደረጃ የዳኝነት አገልግሎት አሰጣጥን ለማሻሻል የተዘጋጀ የውይይት ሰነድ በስልጤ ዞን ከፍተኛ ፍርድ ቤት ፕሬዚደንት በአቶ ነስሮ አለሙ ቀርቦ ምክክር ተደርጓል፡፡
በቀረቡ ሰነዶች በዞን ደረጃ ከፍትህና ከዳኝነት ተግባራት ጋር ተያይዞ የሚስተዋሉ ችግሮች እንዲሁም ሊሻሻሉና ሊፈቱ የሚገቡ ጉዳዮች በስፋት ተነስተው በየደረጃው ከተውጣጡ ባለድርሻ አካላት ጋር በመወያየት የጋራ መግባባት ተፈጥሯል፡፡
የስልጤ ዞን ፍትህ መምሪያ ኃላፊ አቶ በረከት ከድር በፍትህና በዳኝነት አገልግሎት አሰጣጥ ላይ ያሉ ጉድለቶችን ማረምና አገልግሎት አሰጣጡን ማሻሻል የሁሉንም እገዛ የሚጠይቅ ሂደታዊ ተግባር መሆኑን አንስተዋል፡፡
በመምሪያው በኩል ነባር ችግሮችን ለመፍታትና አገልግሎት አሰጣጥን ለማሻሻል የፍትህ ተቋማትን በማስተባበርና ባለድርሻ አካላትን በማሳተፍ ተከታታይ ስራዎች እንደሚሰሩ አቶ በረከት ገልጸዋል፡፡
የከፍተኛ ፍርድ ቤቱ ፕሬዚደንት አቶ ነስሮ ዓለሙ በበኩላቸው በፍትህና የዳኝነት ዘርፍ የሚስተዋሉ ችግሮችን ለመፍታትና የአገልግሎት አሰጣጡን ለማሻሻል በየደረጃው ያሉ የፍትህ፣ የፍርድ ቤትና የፖሊስ ተቋማት ቅንጅታቸውን በማጠናከር ተጨባጩን እየገመገሙ ሊሰሩ እንደሚገባ ተናግረዋል፡፡
ቅንጅታዊ አሰራርን ከማጎልበት ባለፈ የማህበረሰብ ተሳትፎን ማጠናከርና የሸሪዓ ፍርድ ቤቶችንም በተገቢው መጠቀም እንደሚያስፈልግ አቶ ነስሮ መክረዋል፡፡
በህላዊ ዳኝነት ላይ የሚስተዋሉ ጉድለቶችን በመፍታትና ተቀራርቦ በመስራት በየ ጊዜው መልካቸውን የሚቀያይሩ አፍራሽ እንቅስቃሴዎችን መከላከልና የአገልግሎት አሰጣጥን ማሻሻል እንሚቻልም አቶ ነስሮ አንስተዋል፡፡
በውይይት መድረኩ የማጠቃለያ መልዕክት ያስተላለፉት የስልጤ ዞን ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ ክብርት ወ/ሮ መህዲያ ቡሴር የፍትህና የዳኝነት ተቋማት እርስ በርሳቸውና ከሌሎች ባለድርሻ አካላት ጋር ያላቸው ቅንጅት እውነተኛና ችግር ፈቺ መሆን እንደሚገባው ጠቁመዋል፡፡
በተግባር ሂደት ልዩ እገዛ ለሚፈልጉ አከባቢዎች በልዩነት መታገዝ እንዳለባቸው ያነሱት ወ/ሮ መህዲያ በዚህ ሂደት ከፍትህ ተቋማት ባሻገር በዞኑ መንግስትና በምክር ቤቶች በኩል ተገቢው ድጋፍ እንደሚደረግ አረጋግጠዋል፡፡
በፍትህና የዳኝነት ዘርፍ የሚስተዋሉ ችግሮችን መፍታት ከተፈለገ መፍታት እንደሚቻል ያስታወሱት ወ/ሮ መህዲያ ለዚህም ሁሉም ባለድርሻ አካላት በቁርጠኝነት እንዲሰሩ አሳስበዋል።