Central Ethiopia Region Urban Development and Construction Bureau

Central Ethiopia Region Urban Development and Construction Bureau This is the Official page of Centra Ethiopia Region Urban Development and Construction Bureau.

በከተሞች የሚታየውን የሥራ አጥነት ቁጥር ለመቀነስና ሰፊ የሥራ ዕድል ለመፍጠር፣ የኢንቨስትመንት አቅምን ለማጎለበት፣ በከተሞች ልማትን ለማፋጠንና መልካም አስተዳደርን ለመገንባት፣ የንግድ ሥርዓቱን ዘመናዊ ለማድረግ ከመስከረም 2003 ዓ.ም ጀምሮ የንግድ ኢንዱስትሪ ከተማ ልማት ሴክተር ተብሎ በመጠራትና መዋቅራዊ አደረጃጀቱን እስከታችኛው መዋቅር ድረስ በማድረስ ለ5 ዓመታት ያህል በከተሞች የልማትና የመልካም አስተዳደር ስራዎችን አከናውኗል፡፡
በመሆኑም ሴክተሩ በመጀመሪያው ዙር የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዕቅድ ዘመን የተጣሉ ግቦችን ለማሳካት ሰፊ ርብርብ በማድረግ ከፍተኛ ውጤት ማስመዝገብ ችሏል፡፡
ይሁንና በሴክተሩና በስሩ በሚገኙ

ተቋማት ላይ የሚታዩ የአደረጃጀት ክፍተቶችን በመፈተሽ በሁለተኛው የዕድገትና ትራንስፎርሜሽን ዘመን ከመጀመሪያው ምዕራፍ ጀምሮ አዲስ አደረጃጀት በአዋጅ እንዲፈጠር ተደርጓል፡፡
በዚህም መሠረት በቀድሞ ስሙ ን/ኢ/ከ/ል/ቢሮ ተብሎ የሚጠራው አደረጃጀት የከተማ ልማትና ቤቶች ቢሮ ፣የንግድና የኢንዱስትሪ ልማት ቢሮ፣ እና የኢንቨስትመንት ኮሚሽን በሚል የአደረጃጀትና የመዋቅር ለውጥ ተደርጓል፡፡
ስለሆነም ይህ ጽሁፍ በዋናነት የሚዳስሰው ከጥቅምት 16/2008 ዓ.ም ጀምሮ በአዋጅ ቁጥር 161/2008 ፀድቆ ወደ ተግባር በገባው በከተማ ልማትና ቤቶች ቢሮ ላይ ትኩረት በማድረግ መረጃውን ለአንባቢው እንዲደርስ ያደርጋል፡፡

በወልቂጤ ከተማ እየተከናወኑ ያሉ ሁሉአቀፍ ፕሮጀክቶች ህብረተሰቡን በማህበራዊና በኢኮኖሚያዊ ዘርፎች ተጠቃሚ እያደረጉ ነው  ሲል የወልቂጤ ከተማ አስተዳደር ገለፀ።‎ቡታጅራ፣ ‎ግንቦት 28/20...
05/06/2026

በወልቂጤ ከተማ እየተከናወኑ ያሉ ሁሉአቀፍ ፕሮጀክቶች ህብረተሰቡን በማህበራዊና በኢኮኖሚያዊ ዘርፎች ተጠቃሚ እያደረጉ ነው ሲል የወልቂጤ ከተማ አስተዳደር ገለፀ።

ቡታጅራ፣ ‎ግንቦት 28/2018ዓ.ም

‎የለውጡ መንግስት ለከተሞች እድገትና ለውጥ በሰጠዉ ልዩ ትኩረት በወልቂጤ ከተማ የኢኒሼቲቭ ፕሮግራሙ ኮሪደር ልማት፣ የከተማ ጽዳትና ውበት፣ የሥራ እድል ፈጠራ፣ የአረንጓዴ አሻራ ሥራዎች ፣የኑሮ ውድነት ከማረጋጋት አንፃር ሊጠቀሱ የሚችሉ ውጤቶች ተመዝግቧል ።

‎የወልቂጤ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ሙራድ ከድር እንደገለፁት የለውጡ ትሩፋቶች በተገቢው በመጠቀም ከዚህ በፊት በነበረው የልማት ቁጭት በፍጥነት ህዝባችንን አሳትፈን ወደ ተግባር ገብተናል።

‎የኮሪደር ልማት ስራዎች ስናስጀም በፍጥነት ወሰን የማስከበር ስራ በመስራት እና የገፅታ ግንባታ ስራ ልዩ ትኩረት ሰጥተን ሰርተናል።

‎በዋናው አስፓልት አካባቢ ያሉ የህብረተሰብ ክፍሎችን በመልሶ ማልማትና የገፅታ ግንባታ ተግባራት አቅም ያላቸው በፍጥነት በተቀመጠው ስታንዳርድ ግንባታ እንዲፈፅሙ በማድረግ አቅም የሌላቸው በመንግሥት ቁጠባ ቤት የሚኖሩትን ደግሞ በአክሲዮን በማደራጀት ሙያዊ ድጋፍ በማድረግ ልማቱን በማፋጠን ወደ ስራ ገብተዋል።

‎የከተማው ማህበረሰብ ለልማት ያለውን ድጋፍ በከፍተኛ ሁኔታ ያሳየበት እንደነበረም ከንቲባው ጠቁመዋል።

‎በመጀመሪያው ዙር የኮሪደር ስራ 7.6 ኪሎ ሜትር በሁለቱ ክፍለከተማ መጠናቀቁን ገልፀው በህዝብና በመንግሥት ቅንጅት ተግባራዊ ሆኗል።

‎የስራ ባህላችንን ከፍ በማድረግ በከተማችን ለሚገኙ ከ700 በላይ የሚሆኑ የህብረተሰብ ክፍሎችን በኮሪደሩ ልማት ስራ ምክንያት የስራ እድል እንደተፈጠረላቸው አንስተዋል።

‎የሁለተኛው ዙር 6.8 ኪሎሜትር የኮሪደር ልማት ስራ ከ218 ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ ስራው መጀመሩንም ተናግረዋል።

‎እንዲሁም በከተማችን ከተሰሩ የኢኒሼቲቭ ፕሮግራም ስራዎች ፅዱ ከተማ የኢትዮጵያ ኢኒሼቲቭ ደረጃውን የጠበቀ መፀዳጃ ቤት ግንባታ ተጠናቆ አገልግሎት እየሰጠ ይገኛል ።

‎የአንድ ከተማ አንድ ፕሮጀክት የማህበረሰብ ፋርማሲ ቤት ግንባታ ተጠናቆ ከ4.2 ሚሊዮን ብር በላይ ወጪ የመድኃኒት ግዢ በማድረግ አገልግሎት እየሰጠ ነው ሲሉ ከንቲባው ተናግረዋል።

‎የኑሮ ውድነት ለማረጋጋት ደረጃውን የጠበቀ የገበያ ማዕከል ግንባታ ከ20ሚሊዮን ብር ወጪ እየተገነባ ነው ያሉት ከንቲባው ከሰንበት እስከ ሰንበት ገበያዎች ምርቶች በስፋት በማስገባህ ማህበረሰቡ ተጠቃሚ ለማድረግ ስራዎች በትኩረት የተሰሩ ይገኛል ብለዋል።

‎ትምህርት የሁሉም ነገር መሰረት በመሆኑ ትውልድ ላይ የሚሰሩ ስራዎች ተጠናክረው የሚቀጥሉ ሲሆን አራት የመማሪያ ክፍል ግንባታ በጉብሬ ክፍለከተማ በአንድ ትምህርት ቤት እያስገነባን ነው ብለዋል።

‎ሌላው የኢኒሼቲቭ ፕሮግራም አንዱ የሆነውን የአንድ ማዕከል የመሶብ አገልግሎት ግንባታ በከተማችን እየተገነባ ሲሆን በአጭር ጊዜ ተመርቆ አገልግሎት የሚሰጥ መሆኑንም ገልፀዋል።

‎ማዕከሉ ሲጠናቀቅ በቴክኖሎጂ በማስተሳሰር ግልፅ ጥራት ያለው አገልግሎት ለማህበረሰቡ በመስጠት ያለው አስተዋጽኦ ከፍተኛ ነው ብለዋል፦ የከተማው መንግስት ኮሙኒኬሽን



ወቅታዊ ጉዳዮችን አስመልክቶ የተሰጠ መግለጫግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም. ማለዳ ላይ፤ የመጀመሪያው የወገግታ ጭላንጭል በከፍታማዎቹ የኢትዮጵያ ተራሮች ላይ ፈንጥቆ ጨለማውን ሳይቀድ በፊት ኢ...
05/06/2026

ወቅታዊ ጉዳዮችን አስመልክቶ የተሰጠ መግለጫ

ግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም. ማለዳ ላይ፤ የመጀመሪያው የወገግታ ጭላንጭል በከፍታማዎቹ የኢትዮጵያ ተራሮች ላይ ፈንጥቆ ጨለማውን ሳይቀድ በፊት ኢትዮጵያውያን ረጃጅም ሰልፍ ተሰልፈዋል። በጅማ፣ በድሬዳዋ፣ በሐዋሳ፣ በባሕር ዳር እንዲሁም ስማቸው በዓለም አቀፍ የዜና ጋዜጣዎች ላይ ፈጽሞ ሊወጣ በማይችሉ ከተሞችና መንደሮች ውስጥ ያሉ ወንዶችና ሴቶች፤ ወሳኝ ተግባር ለመፈጸም በሰልፍ ቆሙ። ድምፅ ሰጡ! ይህንን ታሪካዊ ኃላፊነት ለመወጣት ከሃምሳ አራት ሚልዮን በላይ የሚሆኑ ዜጎች ተመዝግበው ነበር። ይህ ቁጥር ከአንዳንድ ሀገሮች አጠቃላይ ሕዝብ ቁጥር በላይ ነው። ይህ ምርጫ እውነተኛ ስለመሆኑ ጥያቄ ለሚያነሣ ለማንኛውም አካል ግልጽ እና የማያሻማ ምላሽ ሰጥቷል!

‎የኢትዮጵያ ሕዝብ ፍላጎት
‎የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ከ52,000 ምርጫ ጣቢያዎች መካከል ከ50,188 በላይ የሚሆኑት በሰዓቱ ተከፍተው ቀኑን ሙሉ መራጮችን ሲያስተናግዱ እንደነበር አረጋግጧል። ከ42 የፖለቲካ ፓርቲዎች የተወጣጡ ከ10,438 በላይ ዕጩዎች እና 80 የግል እጩዎች በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት እና የክልል ምክር ቤት ወንበሮችን ለማሸነፍ ተወዳድረዋል። ይህ በማንኛውም ሊለካ በሚችል መሥፈርት በኢትዮጵያ ታሪክ ትልቁ እና በውሳኔ አሰጣጥም ሆነ በአስተዳደራዊ ረገድ እጅግ በረቀቀ ሁኔታ ተግባራዊ የተደረገ ዴሞክራሲያዊ ተሳትፎ የታየበት ኩነት ነበር።

የቀድሞው የኬንያ ፕሬዚዳንት ክቡር ኡሁሩ ኬንያታ የሚመሩትና ከ37 የአፍሪካ ሀገሮች የተወጣጡ 83 ታዛቢዎችን ያቀፈው የአፍሪካ ኅብረት የምርጫ ታዛቢ ቡድን ምርጫውን “ዴሞክራሲያዊ አስተዳደርን በሰፊው በሚደግፍ ሕጋዊና ተቋማዊ ማዕቀፍ ውስጥ የተካሄደ” ሲል ገምግሞታል። በቀድሞዋ የኡጋንዳ ምክትል ፕሬዚዳንት ክብርት ዶክተር ስፔሲዮዛ ዋንዲራ ካዚብዌ የሚመራው የኢጋድ የምርጫ ታዛቢ ቡድን ባወጣው የመጀመሪያ ደረጃ ሪፖርት፥ በታዘቡባቸው ጣቢያዎች ሁሉ የምርጫ ሳጥኖች በትክክል የታሸጉ መሆናቸውን፣ የፓርቲ ወኪሎች በሂደቱ በሙሉ መገኘታቸውን እንዲሁም ምርጫው አስደናቂ ተቋማዊ፣ አስተዳደራዊና የቴክኖሎጂ ዕድገትን ያሳየ መሆኑን አረጋግጧል። የኢጋድ የምርጫ ታዛቢ ልዑክ ይሄንን ምርጫ «የበርካታ አዳዲስ ምዕራፎች ምርጫ» ሲል ሰይሞታል። የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ኮሚሽን በድምፅ መስጠት ሂደት ውስጥ ምንም ዓይነት የሰብዓዊ መብት ጥሰት እንዳልተመለከተ አረጋግጧል። የሲቪክ ማኅበረሰብ ታዛቢዎች ጥምረት በምርጫ ቦርድ እውቅና ከተሰጣቸው 55 ድርጅቶች 65,299 የታዛቢዎችን በመላ ሀገሪቱ ያሠማራ ሲሆን፥ 99 በመቶ የምርጫ ጣቢያዎች ላይ ያለምንም ዕንቅፋት የመታዘብ ዕድል ማግኘቱን አረጋግጧል። እነዚህ ተዓማኒነት ያላቸው ሀገራዊ እና አኅጉራዊ ተቋማት ያደረጓቸው ግምገማዎችና የሰጧቸው እውነተኛ ፍርዶች ናቸው። እነዚህ ለአፍሪካ ጥላቻ ካላቸው ወይም የአፍሪካን ዴሞክራሲ በውጫዊ መሥፈርቶች ከሚለኩ ተቋማት የተደመጡ ድምፆች አይደሉም።

‎አንዳንድ ዓለም አቀፍ ተንታኞች ይሄንን ምርጫ እንደ ንግሥና በዓል አድርገው ያቆሸሹት ሲሆን ውጤቱም አስቀድሞ የተወሰነ ድራማ እንደነበር አድርገው ሊያቀርቡት ሞክረዋል። እነዚህን መግለጫዎች ከእውነታው ፈጽሞ የራቁ፣ በጥናትና ትንተና ላይ ያልተመሰረቱ እንዲሁም ነፃና የታሰበበት ዴሞክራሲያዊ ምርጫቸውን በኩራት ላደረጉ በሚልዮን የሚቆጠሩ ኢትዮጵያውያን ክብር የማይሰጡ በመሆናቸው የጠቅላይ ሚኒስትር ጽሕፈት ቤት ሙሉ በሙሉ የማይቀበላቸው መሆኑን ያረጋግጣል። አስቀድሞ የተወሰነ ውጤት ቢኖር ኖሮ፤ ከ37 የአፍሪካ ሀገሮች የተወጣጡ 83 ገለልተኛ ታዛቢዎችን፣ 65,299 የሀገር ውስጥ የሲቪል ማኅበረሰብ ታዛቢዎችን ወይም 1,100 ዕውቅና የተሰጣቸውን ዓለም አቀፍ ጋዜጠኞች መጋበዝ ባላስፈለገ ነበር።

‎ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ በዚህ ሀገራዊ ምርጫ ለተሳተፉ የኢትዮጵያ ዜጎች፣ ለብሔራዊ ምርጫ ቦርድ እና ላሠማራቸው ከ350,000 በላይ ኃላፊዎች፣ ሂደቱን ለጠበቁት የጸጥታ ኃይሎች እንዲሁም ኢትዮጵያ ለዴሞክራሲ ግንባታ መጎልበት እና ለሂደቱ መሳካት ያላትን ቁርጠኝነት ላረጋገጡት የአፍሪካ እና ቀጣናዊ የታዛቢ ቡድኖች ምስጋናቸውን ያቀርባሉ!

‎ስለ ኢትዮጵያ ልማት
‎ኢትዮጵያውያን ግንቦት 24 2018 ዓ.ም ውሳኔያቸውን ሲያስቀምጡ፣ ሀገራቸውን በፍጹም የዴሞክራሲ ባህል ውስጥ ለማንበር ነው። በሌላ በኩል ኢትዮጵያ ባላት ጸጋ ልክ የሚያስፈልጋትን ሁለንተናዊ ልማት በፍጥነት እውን የማድረግ ባህል እንዲቀጥል ሕዝባችን ተናግሯል።

‎ባለፉት ዓመታት የታየው እውነት እንደሚያሳየን የኢፌዴሪ መንግሥት የተስፋ ቃል መንግሥት አልነበረም። ይልቁንም በተጨባጭ የሚታዩ ውጤቶች የተመዘገቡበት ውጤት ተኮር መንግሥት ሲሆን፤ እነዚህም ውጤቶች በግልጽ የሚታዩ ናቸው። የኢትዮጵያ ኢኮኖሚ በ2017 በጀት ዓመት የ9.2 በመቶ ዕድገት ያስመዘገበ ሲሆን፥ ይሄም በዓለም ላይ ፈጣን ዕድገት ካስመዘገቡ ኢኮኖሚዎች አንዱ ያደርገዋል። ይሄንን መነቃቃት መሠረት በማድረግ በ2018 በጀት ዓመት የኢኮኖሚ ዕድገቱ 10.2 በመቶ ይደርሳል ተብሎ ይጠበቃል። ዕድገቱ ግብርናን፣ ኢንዱስትሪንና የአገልግሎት ዘርፎችን በከፍተኛ ደረጃ ያካተተ ሰፊ መሠረት ያለው ቢሆንም፥ ከጊዜ ወደ ጊዜ ግን ኢንዱስትሪው ለዕድገቱ ዋነኛ አንቀሳቃሽ ኃይል ሆኖ እየመጣ ይገኛል። ይሄም መንግሥት ለማኑፋክቸሪንግ፣ ለኢንዱስትሪ ልማት፣ ለዕሴት ጭማሪና ለውጭ ገበያ ተኮር ምርቶች የሰጠውን ቀጣይነት ያለው ትኩረት ያሳያል።

‎እነዚህ ውጤቶች እንዲሁ ግምቶች ብቻ ሳይሆኑ፥ በጠቅላይ ሚኒስትሩ የ100 ቀናት የሥራ አፈጻጸም ግምገማ ሥርዓት አማካኝነት ክትትል የሚደረግባቸው የተጠያቂነትና የታቀደ አመራር ፍሬዎች ናቸው። አጠቃላይ የወጪ ንግድ ገቢ 20 ቢልዮን የአሜሪካ ዶላር ይደርሳል ተብሎ የሚጠበቅ ሲሆን፥ ይህም ከ2016 ዓ.ም. ወዲህ የ100 በመቶ ገደማ ጭማሪ አሳይቷል። የዋጋ ግሽበትም ወደ ታች ማሽቆልቆሉን በመቀጠል አሁን ላይ ወደ አንድ አሐዝ ደረጃ እየተቃረበ ይገኛል፤ ይሄም በቅርብ ዓመታት ውስጥ በቤተሰቦችና በንግዶች ላይ ከባድ ጫና ፈጥሮ ከነበረው ባለ ሁለት አሐዝ የዋጋ ግሽበት አንጻር ትልቅ መሻሻል ነው። ይህ ስኬት የተመዘገበው ዓለም አቀፍ የኃይል አቅርቦትና ሌሎች ስትራቴጂካዊ ቁሳቁሶችን ገበያ ያናጋው የመካከለኛው ምስራቅ ወቅታዊ ጂኦፖለቲካዊ ውጥረት ጨምሮ፣ ውጫዊ ጫናዎች በነበሩበት ወቅት ነው።

‎የሀገር በቀል ኢኮኖሚ ማሻሻያ አጀንዳ ከተጀመረ ወዲህ መንግሥት ከውጭ ምንጮች ምንም ዓይነት አዲስ የንግድ ብድር ስምምነት ያላደረገ ሲሆን፥ ይሄም የሀገሪቱን የብድር ዕዳ ጫና በከፍተኛ ሁኔታ አቅልሎታል። ከእነዚህ ቁጥሮች በስተጀርባ ኢትዮጵያውያን በዓይናቸው የሚያዩትና በእጃቸው የሚዳስሱት ተጨባጭ ለውጥ አለ። ታላቁ የኢትዮጵያ ሕዳሴ ግድብ ለመኖሪያ ቤቶች፣ ለንግድ ተቋማትና ለጎረቤት ሀገራት የኤሌክትሪክ ኃይል እያመነጨ ይገኛል። ይህ ግድብ በራሳቸው በኢትዮጵያውያን የተደገፈ፣ በኢትዮጵያውያን መሐንዲሶች የተገነባና ቀጣይነት የነበረውን ውጫዊ ጫናዎችን ተቋቁሞ የተጠናቀቀ ነው። ከሃይድሮ ፓወር ጎን ለጎን፥ በኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል የሚገኘውን የአይሻ ሁለት የንፋስ ኃይል ማመንጫ እና በአርሲ ዞን የሚገኘውን የአሰላ የንፋስ ኃይል ማመንጫ ፕሮጀክቶች፤ በመሳሰሉ ሥራዎች የታዳሽ ኃይል አቅርቦቷን እያሰፋች ሲሆን፥ ይህም የቀጣናዊ ኢነርጂ ትብብርን እያሳደገ የብሔራዊ ኃይል አቅርቦት መረቡን የመቋቋም ዐቅም ያጠናክራል። በአፍሪካ አህጉር ታሪክ ውስጥ ትልቁ የመሠረተ ልማት ኢንቨስትመንት አንዱ የሆነው የቢሾፍቱ ዓለም አቀፍ አውሮፕላን ማረፊያ ፕሮጀክት የመሠረት ድንጋይ ተጥሎ ግንባታው ተጀምሯል። እነዚህ ምኞቶች አይደሉም፤ ተጨባጭ ሐቆች ናቸው።

‎ግብርና፣ አምራች ኢንደስትሪና ቴክኖሎጂ
‎በግብርናው ዘርፍ፣ የመንግሥት የምግብ ሉዓላዊነት አጀንዳ ወቅታዊ ለውጦችን ሳይሆን መዋቅራዊ ውጤቶችን እያስገኘ ቀጥሏል። በሶማሌ ክልል የጎዴ ዩሪያ ማዳበሪያ ፋብሪካን ለመገንባት ከአሊኮ ዳንጎቴ ግሩፕ ጋር የተፈረመው አጋርነት የዘመኑ ጉልህ የኢንዱስትሪ ኢንቨስትመንቶች አንዱ ማረጋገጫ ነው። ፋብሪካው በዓመት 3 ሚልዮን ሜትሪክ ቶን ዩሪያ የማምረት አቅም እንዲኖረው ታቅዶ እየተገነባ ሲሆን፥ ይሄም ኢትዮጵያን በዓለም ትላልቅ ማዳበሪያ አምራች ሀገራት ተርታ ያሰልፋታል። ጠቅላይ ሚኒስትሩ ግንቦት 9 ቀን 2018 ዓ.ም. የፕሮጀክቱን የግንባታ ሂደት በጎበኙበት ወቅት እንደገለጹት፤ “ይህ ፕሮጀክት በግብርና ትራንስፎርሜሽን፣ በምግብ ዋስትና፣ በኢንዱስትሪ ዕድገትና በኢኮኖሚ ራስን መቻል ላይ የተደረገ ስትራቴጂካዊ ኢንቨስትመንት ነው” ብለዋል። አስተማማኝ ባልሆነና ውድ በሆነ የማዳበሪያ አቅርቦት ለረጅም ጊዜ ለተገደቡት ኢትዮጵያውያን አምራቾች የዚህ ፕሮጀክት ፋይዳ ፈጣንና ተጨባጭ ነው።

ከዚህ ምርጫ ጥቂት ቀናት ቀደም ብሎ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ግንቦት 19 ቀን 2018 ዓ.ም. በነገሌ ቦረና ገዳ አውሮፕላን ማረፊያ ምርቃት ላይ ሲገኙ የታየው ተምሳሌትነት ለቦረና ሕዝብ ትልቅ ትርጉም ነበረው። ይህ ዞን በዓለም አቀፍ ደረጃ የሚታወቅበት ስም የሀገርን አንገት ያስደፋ እንደነበር የቅርብ ጊዜ ትውስታ ሲሆን፤ እርሱም ድርቅ ነው። ለሦስት ተከታታይ ዓመታት የዝናብ መጥፋት በሚሊዮን የሚቆጠሩ ከብቶችን የገደለ፣ ቤተሰቦች ለውኃ ፍለጋ በመቶዎች የሚቆጠሩ ኪሎ ሜትሮችን እንዲጓዙ ያስገደደ፣ እንዲሁም በእነዚህ የግጦሽ መሬቶች ላይ ለዘመናት ራሳቸውን ችለው የኖሩ ማኅበረሰቦችን ለአስቸኳይ የምግብ እርዳታ እጅ እንዲዘረጉ አድርጎ ነበር። ዓለም የሚያውቃት ቦረና እርሷ ነበረች። የጠቅላይ ሚኒስትሩ የግንቦት ወር ጉብኝት ግን የተለየ ታሪክ አሳይቷል። አሁን ላይ ለአርብቶ አደር ማኅበረሰቦችና ለከብቶቻቸው ንጹሕ ውኃ እያቀረቡ ያሉትን የውኃና የመስኖ መሠረተ ልማቶችን የገመገሙ ሲሆን፥ ከጥቂት ዓመታት በፊት አቧራ ብቻ በነበረው መሬት ላይ የክላስተር እርሻዎችን ጎብኝተዋል፤ በያቤሎ የባህል ማዕከል መርቀዋል፤ እንዲሁም በአየር ንብረት ሁኔታዎች ምክንያት ቀድሞ ተገልሎ ለነበረው ቀጣና ዓመቱን ሙሉ ትስስር የሚፈጥር አውሮፕላን ማረፊያ መርቀው ከፍተዋል።

‎የአምራች ዘርፉም ተመሳሳይ የለውጥ ታሪክ አለው። በግንቦት 2018 ዓ.ም. በተካሄደው 4ኛው ኢትዮጵያ ታምርት ኤክስፖ ላይ፤ መንግሥት ለአራት ዓመታት የተመዘገበውን ቀጣይነት ያለው የኢንዱስትሪ መስፋፋት ውጤቶች አቅርቧል። የአምራች ዘርፉ የግብአት አቅርቦት በዓመት 9 ሚልዮን ቶን ወደ 15 ሚልዮን ቶን አድጓል። የምርት አቅም አጠቃቀም ከ47 በመቶ ወደ 67 በመቶ ከፍ ማለቱን፣ የማኑፋክቸሪንግ ዕድገት ከ4.8 በመቶ ወደ 10.7 በመቶ ማደጉን፣ እንዲሁም ለአነስተኛና መካከለኛ ኢንተርፕራይዞች የሚቀርበው ፋይናንስ ከ8.1 ቢልዮን ብር ወደ 50 ቢሊዮን ብር ማደጉን ያሳያል። እነዚህ ስኬቶች በሀገር ውስጥ ምርት ላይ በከፍተኛ ሁኔታ እየተንጸባረቁ ይገኛሉ። ኤክስፖው በተጠናቀቀ በሃያ ቀናት ውስጥ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በዘጠኝ ወራት ውስጥ ብቻ ተጠናቆ ከ80 በመቶ በላይ ጥሬ ዕቃውን ከሀገር ውስጥ የሚያገኘውን ግዙፍ የኢንዱስትሪ ኢንቨስትመንት «ግራንዲዩር የሴራሚክ ማኑፋክቸሪንግ» ፋብሪካን በሞጆ ከተማ መርቀዋል። ቀደም ሲል በገቢ የሴራሚክ ምርቶች ላይ ጥገኛ የነበረችው ኢትዮጵያ አሁን ላይ የሴራሚክ ምርቶችን ከውጭ ማስገባት ሙሉ በሙሉ ለማቆምና ለውጭ ገበያ የሚሆን ምርት ለማስፋፋት እየተዘጋጀች ትገኛለች።

‎በቴክኖሎጂው ዘርፍም፥ ዘመናዊ ልማት ከጊዜ ወደ ጊዜ በዳታ፣ በፈጠራና በዲጂታል ሥርዓቶች የሚወሰን መሆኑን በመገንዘብ፥ መንግሥት ኢትዮጵያን ሰው ሠራሽ አስተውሎት እና የኢንዱስትሪ 5.0 ማሕቀፎችን ቀድመው ከተገበሩ ሀገራት ተርታ እያሰለፋት ይገኛል።

‎የጽንፈኝነትን ፖለቲካ ውድቅ ማድረግ
‎በኦነግ ሸኔ ዐማጽያን በንጹሐን ዜጎች ላይ በተለይም በሃይማኖት ተቋማት ውስጥ ዒላማ ተደርገው የተፈጸሙ ጥቃቶችን ተከትሎ፤ የቤተሰብ እና የወዳጆቻቸውን ሕይወት ላጡ፣ የአካል ጉዳት ለደረሰባቸው እና የቤት ንብረታቸው ለወደመባቸው በአርሲ ዞን ለሚገኙ ወገኖቻችን ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ በኢትዮጵያ መንግሥት ስም የተሰማቸውን ጥልቅ ኀዘን ይገልጻሉ።

እነዚህ ጥቃቶች የሀገሪቱን ብሔራዊ ዕድገት ለማደናቀፍ ከሚሹ አካላት፣ በአማራ ክልል ከሚንቀሳቀሱ የሀገር ውስጥ አማፂ ቡድኖች እና ለሀገሪቱ ሁለንተናዊ ዕድገት ጥላቻ ካላቸው የውጭ ኃይሎች ጋር በጥምረት የተከናወኑ ሲሆኑ፤ ዓላማቸውም በኢትዮጵያ አለመረጋጋትንና የምርጫ መስተጓጎልን ለመፍጠር ሲደረግ የነበረ የጥፋት ውጥን ተከታይ ነው። መንግሥት 7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ያለ አንዳች የፀጥታ ችግር ፍትሐዊና አሳታፊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ ከአንድ ዓመት በላይ የዘለቀ ልዩ ትኩረትና ዝግጅት በማድረግ በቁርጠኝነት ሲሠራ ቆይቷል። በሌላ በኩል የጥፋት ኃይሎች ከባዕዳን ጋር 'ፅምዶ' የሚል ቁርኝት በመፍጠር ዕኩይ ዓላማቸውን ለማሳካት ሰፊ የጥፋት ዝግጅት ሲያድርጉ ቆይተዋል፣ ሀገራዊ ምርጫው እንዳይከናወን ሰፊ ርብርብ አድርገዋል። በተጨባጭም በቅድመ ምርጫ እና በምርጫ ወቅት የዜጎችን የመምረጥ መብትና ነጻነት ለመጋፋትና ለማደናቀፍ አለን የሚሉትን የጥፋት እጅ ዘርግተዋል።

‎እነዚህ የጠላት ኃይሎች በመደጋገፍና በመናበብ ዐመፅና ሁከት ለማነሳሳት፣ ከተሞችን በሽብር ጥቃት ለማወክ፣ በመንገዶች የደፈጣ ጥቃት በመፈጸም እንቅስቃሴ ለመገደብ እና በተወሰኑ አካባቢዎች ዒላማ አድርገው ነጥሎ ለማጥቃት ተንቀሳቅሰዋል። እንደ ማሳያ የጦር መሣሪያ፣ ተተኳሾችንና ሌሎች ሎጀስቲክሶችን በድጋፍ በማቅረብ በደቡባዊ ትግራይ በሚገኙ አዋሳኝ የአማራ ክልል አንዳንድ ቦታዎች ላይ ትንኮሳ ፈጽመዋል፣ በአማራ ክልል ባሕር ዳር፣ ጎንደር፣ ደብረ ብርሃን እና ወልድያ ከተሞችን ጨምሮ በክልሉ ዋና ዋና ከተሞች እና ሲቪሎች ላይ ዒላማ በማድረግ ያካሄደው የሽብር እንቅስቃሴና ዝግጅት፣ በአዲስ አበባ ከተማ ባደራጃቸው የኅቡዕ ሴሎች አማካኝነት በተመረጡ አከባቢዎች ላይ ጥቃት እንዲፈጸም ተንቀሳቅሰው የነበረ ቢሆንም ይሄን የጥፋት ሴራ እና ድርጊት እንዲከሽፍ ማድረግ ተችሏል።

‎በተመሳሳይ በኦሮሚያ ክልል የሸኔ ሽብር ቡድን ከጽንፈኛው ፋኖ ታጣቂ ቡድን ጋር በመናበብ በአንዳንድ አካባቢዎች መንገዶችን በመዝጋት እንቅስቃሴ ለማስቆምና ለማስተጓጎል ፍላጎት የተንቀሳቀሰ ቢሆንም በጸጥታ ኃይሉ በተወሰደበት የተጠናከረ እርምጃ ፍላጎቱን ማሳካት አልቻለም። ቡድኑ በፀጥታ ኃይሉ የተወሰደበትን ርምጃ መቋቋም ባለመቻሉ እና ፍላጎቱን ማሳካት ባለመቻሉ ስስ ዒላማዎች ላይ ያተኮረ ርምጃ በመውሰድ የሃይማኖት እና የብሔር ግጭት ለመቀስቀስ በማለም በአርሲ ዞን አሰኮ እና አካባቢው ጥቃት በመፈጸም ሁሉን አይነት የጥፋት ርብርብ ያደረገ ቢሆንም ሁኔታውን በመቆጣጠር ፀጥታ ኃይላችን በእነዚህ ኃይሎች ላይ የተቀናጀ ርምጃ እየወሰደ ይገኛል።

መንግሥት መሰል ሥጋቶችን በንቃት በመከታተል ላይ ሲሆን፣ በምርጫው ወቅትም በብዙ የሀገሪቱ አካባቢዎች የተቀነባበሩ ተመሳሳይ ዕቅዶችን በስኬት ማክሸፍ ችሏል። በንጹሐን ዜጎች ላይ የሚፈጸሙ ጥቃቶችን፤ ፍርሃትና ክፍፍልን ከሚያጎሉ የሚዲያ ዘመቻዎች ጋር በማስተሣሠር የተቀነባበረው ይህ እኩይ ተግባር፤ በመንግሥት የደኅንነት መዋቅርና ኦፕሬሽኖች አማካኝነት በከፍተኛ ሁኔታ እንዲስተጓጎል ተደርጓል። ብሔራዊ እና ሃይማኖታዊ ክፍፍልን ለመዝራት የኃይል ጥቃትን እና ውድመትን እንደ መሣሪያ የሚጠቀሙ አካላት በሁሉም ኢትዮጵያውያን ዘንድ በግልጽ ሊወገዙ ይገባል። መሰል ተግባሮች በኢትዮጵያ ውስጥ ምንም ዓይነት የወደፊት ዕድል እንደሌላቸው ለማሳየት የተቀናጀ ብሔራዊ ምላሽ በመስጠት ወሳኝ ርምጃዎችን ይቀጥላል።

‎በንጹሐን ዜጎች ላይ ጥቃት የሚፈጽሙ አካላት፣ ድርጊታቸውን ምክንያታዊ ለማስመሰል ምንም ዓይነት የፖለቲካ ንግግር ቢጠቀሙ፤ ወሳኝ ዓላማን እያሳኩ ሳይሆን ወንጀል እየፈጸሙ ነው። የፖለቲካ ቅሬታዎች በኢትዮጵያ ሕገ መንግሥታዊ ሥርዓት፣ በብሔራዊ ምክክር ሂደት እና በዴሞክራሲያዊ ተቋማት አማካኝነት መፍትሔ ሊያገኙ የሚችሉ እና ሊያገኙ የሚገባቸው ናቸው።


ጽንፈኝነት ግን በኢትዮጵያ ምድር ፈጽሞ ቦታ የለውም!

//

05/06/2026
በበጀት ዓመቱ ቀሪ ጊዜያት ፣ በልዩ ትኩረት እየተመሩ የሚገኙ ተግባራትን በጠንካራ የህዝብ ንቅናቄ በማስፈጸም ማሳካት ይጠበቃል _ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር)፤  ግንቦት 27 ፣...
04/06/2026

በበጀት ዓመቱ ቀሪ ጊዜያት ፣ በልዩ ትኩረት እየተመሩ የሚገኙ ተግባራትን በጠንካራ የህዝብ ንቅናቄ በማስፈጸም ማሳካት ይጠበቃል _ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር)፤

ግንቦት 27 ፣ 2018

የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር)፣ በልዩ ትኩረት እየተመሩ የሚገኙ ተግባራትን ወቅታዊ የአፈጻጸም ሁኔታ ዛሬ በበይነ መረብ ገምግመዋል፤ ቀጣይ የትኩረት አቅጣጫዎችም ተመላክተዋል።

በመድረኩ የክልሉ አስተባባሪ ኮሚቴ አባላት፣ የክልሉ ካብኔ አባላት፣ የዞኖች እና ልዩ ወረዳዎች አስተባባሪ ኮሚቴ አባላት፣ እና ሌሎችም የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች ተሳትፈዋል ።

የአፈጻጸም ግምገማው በፋይዳ መታወቂያ ምዝገባ፣ በመሶብ _የአንድ ማዕከል አገልግሎት ማዕከላት ዝግጅት ፣በኢትዮ _ኮደርስ ስልጠና፣ በገቢ አሰባሰብ ፣በከተማና በገጠር ኮሪደር ልማት ፣ በሥራ ዕድል ፈጠራ ስራዎች አፈጻጸም፣የኑሮ ውድነትትን ከማረጋጋትና የነዳጅ አቅርቦትንና ስርጭትን በተመለከቱ ጉዳዮች ዙሪያ ያተኮረ መሆኑ ተጠቅሷል ።

ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር)፣ በመድረኩ ማጠቃለያ እንደገለፁት ፣ በልዩ ትኩረት እየተመሩ የሚገኙ ተግባራትን በጠንካራ የህዝብ ንቅናቄ በማጀብ በበጀት ዓመቱ ውስን ቀሪ ጊዜያት ርብርብ በማድረግ ማጠናቀቅ ይገባል ።

የየደረጃው አመራር፣ በሰባተኛው ጠቅላላ ምርጫ ሂደት የታየውን ሕዝባዊ ንቅናቄ እንደመልካም አጋጣሚ በመጠቀምና በማስቀጠል ለህብረተሰባዊ ተሳትፎና ተጠቃሚነት እመርታ እንዲተጋ አሳስበዋል ።
በበጀት ዓመቱ ቀሪ የአንደ ወር ጊዜ በሁሉም መስኮች በበጀት ዓመቱ መጀመሪያ የታቀዱ ዕቅዶችን በተሟላ ሁኔታ በመፈፀም የህዝብ ተጠቃሚነትን ለማሻሻል በልዩ ትኩረት እንዲሠራ ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) ጥሪ አቅርበዋል ፤የትኩረት መስኮችም ተመላክተዋል።

በሀድያ ዞን ፎንቃ ከተማ አስተዳደር ለቅየሳና ካርታ ዝግጅት ባለሙያዎች በህግ ማዕቀፍ ላይ የግንዛቤና ተግባር ተኮር ስልጠና እየተሰጠ መሆኑ ተገለጸ።በቀን 26/09/2018  ዓ.ምየክልሉ ከተማ...
03/06/2026

በሀድያ ዞን ፎንቃ ከተማ አስተዳደር ለቅየሳና ካርታ ዝግጅት ባለሙያዎች በህግ ማዕቀፍ ላይ የግንዛቤና ተግባር ተኮር ስልጠና እየተሰጠ መሆኑ ተገለጸ።

በቀን 26/09/2018 ዓ.ም

የክልሉ ከተማ መሬት ይዞታ ምዝገባና መረጃ ኤጀንሲ በፎንቆ ከተማ አስተዳደር በዘርፉ ለተሰማሩ ባለሙያዎች በህግ ማዕቀፉ ላይ የግንዛቤና የተግባር ተኮር ስልጠና እየሰጠ መሆኑ ተገለጸ።

ስልጠናውም በክልሉ የካዳስተር ካርታ ዝግጅት ዳይሬክቶሬት አማካኝነት እየተሰጠ ነው ተብሏል።

በየሽዋስ ዘለቀ

በጉራጌ ዞን ወልቂጤ ከተማ አስተዳደር መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ለህዝቡ አገልግሎት አሰጣጥ ለማስጀመር የደረሰበት ደረጃ የጉራጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ላጫ ጋሩማ በተገኙበት ተጎብኝቷ...
03/06/2026

በጉራጌ ዞን ወልቂጤ ከተማ አስተዳደር መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ለህዝቡ አገልግሎት አሰጣጥ ለማስጀመር የደረሰበት ደረጃ የጉራጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ላጫ ጋሩማ በተገኙበት ተጎብኝቷል።

ቡታጅራ፣ ግንቦት 26/2018 ዓ.ም

መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት ህዝቡ በአገልግሎት አሰጣጥ ላይ ያለውን ቅሬታ በዘላቂነት እንደሚፈታ በጉብኝቱ ወቅት የተገለፀ ሲሆን፦

የወልቂጤ ከተማ መሶብ የአንድ ማዕከል ዲጂታል አገልግሎት በከተማዋ የተጀመረውን የልማት ጉዞ ለማሳለጥ የጎላ አበርክቶ እንደሚኖረው በጉብኝት ወቅት ተመላክቷል፡፡

የጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አሕመድ (ዶ/ር) ኢኒሼቲቭ ፕሮግራም አንዱ የሆነው መሶብ የአንድ ማዕከል ዲጂታል አገልግሎት በተለያዩ አካባቢዎች በማንዋል ሲሰጥ የቆየውን የመንግሥት አገልግሎት በአንድ ማዕከል ፈጣን ምላሽ መስጠት የሚያስችል መሆኑንም ተመላክቷል።

መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት በ2030 ዲጅታል ኢትዮጵያን እውን ለማድረግ የተያዘውን ሀገራዊ ተልዕኮ ለማሳካት ቁልፍ ሚና እንዳለው ተገልጿል።

የመንግሥት አገልግሎትን ዘመናዊ፣ ቀልጣፋ፣ ውጤታማና ከብልሹ አሰራር የተላቀቀ እንዲሆን በአንድ ጣራ ሥር በማምጣት የከተማዋን ነዋሪዎች እንግልት ለመቀነስ የተወጠነው "ወልቂጤ መሶብ" የአንድ ማዕከል ዲጂታል አገልግሎት ከፍተኛ ውጤት ሊያመጣ እንደሚችል ተገልጿል።

ማዕከሉ አብዛኛው የሲቪል ስራዎች የተጠናቀቀለት መሆኑን እና በቅርቡም ተጠናቆ አገልግሎት መስጠት እንደሚጀምር ተገልጿል።

የጉራጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ ክቡር አቶ ላጫ ጋሩማ በጉብኝቱ ወቅት ግንባታው በጥሩ ሂደት እየሄደ መሆኑን በመግለፅ ቀሪ ስራዎች በፍጥነት ጥራታቸውን ጠብቀው እንዲጠናቀቁና በጥቂት ቀናት ውስጥ ለአገልግሎት ክፍት እንዲሆን አሳስበዋል።

በጉብኝቱ የጉራጌ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ላጫ ጋሩማ፣ የወልቂጤ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ሙራድ ከድር፣ የወልቂጤ ከተማ ብልጽግና ፓርቲ ቅ/ጽ/ቤት ሀላፊ አቶ ታደለ በቀለ፣ የከተማው አስተባባረ አካላትን ጨምሮ፣የዞኑና የከተማ ከፍተኛ የስራ ሀላፊዎች ተገኝተዋል ሲል የወልቂጤ ከተማ አስተዳደር የመንግስት ኮሚዩኒኬሽን ጉዳዮች ጽፈት ቤት መረጃ ያሳያል።

በርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) የተመራ የክልሉ የስራ ሀላፊዎች ቡድን በወራቤ ከተማ የወንዝ ዳርቻ ልማትና ሜላያን ፓርክ ላይ ምልከታ አደረገ። ቡታጅራ፣ ግንቦት 26/2018 የማዕ...
03/06/2026

በርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) የተመራ የክልሉ የስራ ሀላፊዎች ቡድን በወራቤ ከተማ የወንዝ ዳርቻ ልማትና ሜላያን ፓርክ ላይ ምልከታ አደረገ።

ቡታጅራ፣ ግንቦት 26/2018

የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር) የተመራ የክልሉ ከፍተኛ አመራሮች ቡድን በወራቤ ከተማ የወንዝ ዳርቻ ልማትና ሜላያን ፓርክ ላይ ምልከታ አድርጓል።

ሜላያን የወንዝ ዳርቻ ልማት 9 ሄክታር መሬት የሚሸፍን ሲሆን ለአካባቢው ህብረተሰብ ተጨማሪ የመዝናኛ ስፍራ በመሆን እያገለገለ ነው።

የወንዝ ዳርቻ ልማቱ የከተማዋን ገጽታ በመቀየር ረገድ ጉልህ አስተዋጽኦ እያበረከተ ስለመሆኑም ተመላክቷል።

በልማት ስራ ምልከታው የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ ወ/ሮ ፋጤ ስርሞሎ፣ የክልሉ ብሔረሰቦች ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ አቶ አቡቶ አኒቶ፣ ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አንተነህ ፈቃዱ፣ በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክላስተር አስተባባሪዎች፣ የስልጤ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዘይኔ ቢልካ እና ሌሎች የክልል፣ የስልጤ ዞን እና የከተማ አስተዳደሩ ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል።

ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር)በወራቤ ከተማ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት መርቀው ስራ አስጀመሩ (ቡታጅራ፣ግንቦት 26/2018) የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እን...
03/06/2026

ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር)በወራቤ ከተማ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት መርቀው ስራ አስጀመሩ

(ቡታጅራ፣ግንቦት 26/2018) የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ርዕሰ መስተዳድር እንዳሻው ጣሰው (ዶ/ር)በስልጤ ዞን በወራቤ ከተማ መሶብ የአንድ ማዕከል አገልግሎት መርቀው ስራ አስጀመሩ

በማዕከሉ በ6ተቋማት 20 አገልግሎት እየተሰጠ መሆኑም ተመላክቷል።

በምረቃ መርሐ ግብሩ የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል የህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ ወ/ሮ ፋጤ ስርሞሎ፣የክልሉ ብሔረሰቦች ምክር ቤት ዋና አፈ ጉባኤ አቶ አቡቶ አኒቶ፣ምክትል ርዕሰ መስተዳድር አቶ አንተነህ ፈቃዱ፣በምክትል ርዕሰ መስተዳድር ማዕረግ የክላስተር አስተባባሪዎች፣የስልጤ ዞን ዋና አስተዳዳሪ አቶ ዘይኔ ቢልካ፣
የክልል እና የስልጤ ዞን ከፍተኛ የስራ ኃላፊዎች ተገኝተዋል።

ኢትዮጵያውያን መርጠዋል፤ ኢትዮጵያ አሸንፋለች!ግንቦት 25 2018 ዓ.ምየመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት ኢትዮጵያ ከዜጎቿ የፈለገችዉን ኹሉ በፈለገችው ጊዜና ኹኔታ የምታገኝ ሀገር ናት፡፡ ለሀ...
02/06/2026

ኢትዮጵያውያን መርጠዋል፤ ኢትዮጵያ አሸንፋለች!

ግንቦት 25 2018 ዓ.ም

የመንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት

ኢትዮጵያ ከዜጎቿ የፈለገችዉን ኹሉ በፈለገችው ጊዜና ኹኔታ የምታገኝ ሀገር ናት፡፡ ለሀገራቸዉ የተጠየቁትን ሁሉ ለመስጠት ወደኋላ የማይሉ ዜጎች ስላሏት በእጅጉ ኮርታለች፡፡ ከዓድዋ እስከ ሕዳሴ ግድብ፣ ከወገን ለወገን መረዳዳት እስከ አረንጓዴ ዐሻራ የዜጎቿን ተሳትፎ ጠይቃ፣ ከመሻቷ በላይ ተሳትክቶላታል፡፡ ዛሬ የተደገመዉም ይኸው ነው፡፡

ኢትዮጵያ ኢትዮጵያዊ ዴሞክራሲን ማንበር፣ በግልጽና ዴሞክራሲያዊ ምርጫ መንግሥትን መምረጥ፣ ሕገ መንግሥታዊነትን ፅኑ መሠረት ማስያዝ ትሻለች፡፡ ለዚህ ደግሞ 7ኛዉን ሀገራዊ ምርጫ እንደ ትልቅ አጋጣሚ መጠቀም አስፈልጓት ነበር፡፡

በምላሹም ከ54 ሚሊዮን በላይ ዜጎች ለመራጭነት ተመዝግበው የዛሬዋን ቀን ሲጠባበቁ ቆይተዋል፡፡ እነሆ የእናት ሀገር ጥሪን በመቀበል ዜጎች በነቂስ ወጥተው ሲመርጡ ውለዋል፤ ሌሊቱንም አጋምሰዋል፡፡ በኢትዮጵያ የምርጫ ታሪክ ዜጎች ለረዥም ሰዓታት ተሰልፈዉ ድምፅ የሰጡበት ልዩ ምርጫም ነው፡፡

ምርጫዉ እንዳይካሄድ ባዳ እና ባንዳ ተቀናጅተዉ ያልቆፈሩት ጉድጓድ፣ ያልደረደሩት እንቅፋት አልነበረም፡፡ ነገር ግን ኢትዮጵያ ለጠራችው ሀገር ወዳድ ኢትዮጵያዊ የማይቻል ነገር አልነበረምና በስኬት ተጠናቅቋል፡፡ ኢትዮጵያውን በሰላማዊ መንገድ መርጠው ኢትዮጵያ አሸንፋለች፡፡

የኢትዮጵያን የዴሞክራሲያዊ ምርጫ ጥሪ ተቀብሎ ከንጋት እስከ ምሽት በመምረጥ ምላሽ ለሰጠው ሕዝብ፣ ሕገ መንግሥታዊ ሥርዐቱ እንዲጸና እና ዜጎች በሰላም እንዲመርጡ ምቹ ዓውድ ለፈጠሩ የፀጥታ አካላት፣ ወቅታዊና ትክክለኛ መረጃ በየደቂቃዉ ሲያደርሱ ለነበሩ የመገናኛ ብዙኃን ተቋማት እንዲሁም የምርጫዉን ሂደት ለመሩ፣ ላስተባበሩ እና ለታዘቡ ሁሉ ኢትዮጵያ ታመሰግናለች፡፡

የኢፌዴሪ መንግሥት ኮሙኒኬሽን አገልግሎት

ግንቦት 25 2018፣አዲስአበባ፣ኢትዮጵያ

Address

Butajira

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when Central Ethiopia Region Urban Development and Construction Bureau posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Share