30/05/2026
ከታሪፍ በላይ ያስከፈለ አሽከርካሪ ላይ እርምጃ መወሰዱ ተገለፀ
መነሻውን ከቦንጋ ወደ ጠሎ ያደረገው ኮድ ሶስት ደ/ም 00661 የህዝብ ማመላለሻ ተሽከርካሪ በህግ ከተቀመጠዉ ታሪፍ በላይ በማስከፈሉ እርምጃ መወሰዱን የጠሎ ወረዳ ፖሊስ ጽ/ቤት የትራፊክ ስራ ሂደት አስተባባሪ ረዳት ኢንስፔክተር ሙሉጌታ በዛብህ ተናግረዋል።
ተሽከርካሪው ግንቦት 21 ቀን 2018 ዓም ከቦንጋ-ጠሎ ህጋዊ ታሪፍ 170 ብር ሲሆን ያለአግባብ 400 ብር ማስከፈሉን ነው ረዳት ኢንስፔክተር ሙሉጌታ ያብራሩት።
በዚህም በተደረገው ክትትል 29 ሰዎችን ከጫነው ተሽከርካሪ ለእያንዳንዳቸው 2 መቶ 30 ብር ተመላሽ የተደረገ ሲሆን በተመሳሳይ በሰራዉ ህገወጥ ተግባር 1 ሺህ 500 ብር መቀጣቱን ጠቁመዋል።
ህብረተሰቡ መሰል ህገወጥ ድርጊቶችን በመጠቆም የተለመደውን ትብብር ማድረግ እንዳለበት የጠቆሙት ረዳት ኢንስፔክተር ሙሉጌታ የተሽከርካሪ አሽከርካሪዎችና ባለንብረቶች ከህገወጥ ድርጊታቸው እንዲቆጠቡ አሳስበዋል።