01/04/2023
ተቋማዊ አቅምን ለማጎልበት የሚረዳ የ9 ወራት የሥራ እንቅስቃሴ የምክክር መድረክ በዞን ማዕከል ተደረገ፡፡
ንግድና ገበያ ልማት ተቋም የተጣለበትን የህዝብ አደራ በብቃት ለመወጣት በተቋም ደረጃ የሚስተዋሉ ችግሮችን ተመካክሮ ለመፍታት ያለመና ጽ/ቤቶች ላይ አዳዲስ አመራሮች ተልዕኮ ተቀብሎ ከመሚጣታቸዉ ጋር ተያይዞ ወጥ የሆነ አቋም ለመያዝና በመዋቅሮች አለመቀናጀት ምክንያት የሚከሰት ህገ-ወጥ ንግድን ለመከላከል ያለመ ምክክር ተደርጓል፡፡
በምክክር መድረኩ የዞኑ ማኔጅሜንት አካላት፣ የወረዳና ከተማ ጽ/ቤት ኃላፊዎችና የአ/ምንጭ ከተማ ቀበሌያት ን/ገ/ልማት ጽ/ቤት ኃላፊዎች ተሳትፈዋል፡፡
በመድረኩ በንግድ ኢንስፔክሽንና ሬጉሌሽን ዳይሬክቶሬት ዳይሬክቴር በአቶ ተስፋዬ ዩካ በኩል ሁሉንም መዋቅሮች የዳሰሰ የ9 ወራት የሥራ አፈፃፀም የቀረበ ሲሆን፡፡ በቀረበዉ ሪፖርት ላይ በጥልቀት ምክክር ተደርጎ የጋራ ማግባባት ላይ ተደርሷል፡፡
ምክክሩን የመሩት የንግድና ገበያ ልማት መምሪያ ኃላፊ ወ/ሪት መስከረም ዛፉ እንደገለፁት የኑሮ ዉድነቱን ለመቀነስ እንደ ተቋም ለብቻችን የምንወጣዉ ነገር ስላልሆነ ባለድርሻ አካላትን ያቀፈ ቅንጂታዊ ሥራዎችን መስራት ይጠበቃል፡፡ አምራች ግለሰቦችን/ማህበራትን እንዲሁም ጅምላ ነጋዴዎችን በቀጥታ ከሸማቹ ማህበራት ጋር ለማገናኘት መንግስት ባስቀመጠዉ አቅጣጫ መሰረት ቅዳሜና እሁድ ገበያ ማመቻቸት ይጠበቃል ያሉት የመምሪያዉ ኃላፊ ለዚህም ስኬት ከመዋቅሩ ፊት አመራሮች ጋር መቀናጀት ያስፈልጋል ብለዋል፡፡ ወቅቱ በዓላትን የምንቀበልበት ወቅት ከመሆኑ ጋር ተያይዞ የገበያ መረጃዎችን በአግባቡ በማሰባሰብና በመተንተን መዋቅር ከመዋቅር ጋር በመናበብ በተመጣጣኝ ዋጋ ለሸማቹ ህብረተሰብ ምርት እንዲደርስ የትስስር ስራዎችን መስራት ያስፈልጋል ብለዋል፡፡
እንደ ተቋም ህገ-ወጥነትን ለመከላከል በዉስጥም ሆነ በዉጪ ኢንስፔክሽን ሥራዎች መረባረብ ያስፈልጋል፡፡ ያለ ፈቃድ የሚሰሩትን፣ ባልጸና ፈቃድ የሚሰሩትን፣ ዋጋ ዝርዝር ያልለጠፉትን፣ ፈቃድ ያልለጠፉትን፣ ከተፈቀደላቸዉ ዉጪ የሚሰሩትን በአዋጁ መሰረት ወደ ህጋዊ መስመር ማስገባት ያስፈልጋል ያሉት ወ/ሪት መስከረም ዛፉ የሚዛን ምርመራ ሥራዎችን በመስራት ህብረተሰቡን ከመበዝበዝ መታደግ ያስፈልጋል ብለዋል፡፡
ሸማች ክበባትን በየተቋማት ማደራጀት/ማጠናከር፣ ለገበያዎች የይዞታ ማረጋገጫ ሰነድ እንዲዘጋጅ ማድረግና ገበያዉ እንድዘምን መስራት ያስፈልጋል ያሉት የመምሪያዉ ኃላፊ የንግድ ሥርዓቱ እንድዘምንና/E-trade/ ወደ ትግበራ የገቡ መዋቅሮች በምንም ዓይነት ሰበብ ሥራዉ እንዳይቀለበስ በትኩረት መከታተል ያስፈልጋል፡፡
በሰብልም ሆነ በቁም እንስሳት ዘርፍ የድልልና ፈቃድ ያወጡ በተሻሻለዉ ፈቃድ መስጫ መደብ መሰረት ፈቃዱ ተመላሽ እንድደረግ ያሳሰቡት ኃላፊዋ ለቁም እንስሳት ነጋዴዎች የባጅ ሥርዓቱ ተጠናክሮ እንድቀጥል አሳስበዋል፡፡
ከቤቱ በተነሱ በተለያዩ ጉዳዮች ከሚመለከተዉ አካል ጋር ለመነጋገርና ችግሮቹን ለመፍታት ይሰራል ያሉት ኃላፊዋ የተቋሙን ተልዕኮ ለማሳካት ሁሉም በቅንጂት ርብርብ እንዲያደርግ አሳስበዋል፡፡
መጋቢት 23/2015 አ/ምንጭ