26/05/2026
የሀላባ ቁሊቶ ከተማ አስተዳደር ብልጽግና ፓርቲ የፐብሊክ ሰርቫንት ግንባር ህብረት አመራሮች ለተለያዩ አቅመ ደካሞች ማዕድ አጋሩ!!
በሀላባ ቁሊቶ ከተማ አስተዳደር የብልጽግና ፓርቲ የፐብሊክ ሰርቫንት ግንባር የብልጽግና ህብረት አመራሮች፣ በከተማዋ ለሚገኙ አቅመ ደካማ እና አነስተኛ ገቢ ያላቸው ወገኖች ለበዓል የሚሆን የአስቤዛ ድጋፍ በማድረግ ደስታቸውን ተጋርተዋል።
ይህ የማዕድ ማጋራት መርሃ ግብር "አብሮነትና መረዳዳት የባህላችን መገለጫ ነው" በሚል መሪ ቃል የተከናወነ ሲሆን፣ ዋና ዓላማውም በዓላትን አስመልክቶ በዝቅተኛ የኑሮ ደረጃ ላይ የሚገኙ የማህበረሰብ ክፍሎች ያለምንም ችግር በዓሉን በደስታና በሰላም እንዲያሳልፉ ለማስቻል ነው።
የሀላባ ቁሊቶ ከተማ አስተዳደር ብልጽግና ፓርቲ የኢኮኖሚ ቁ 1 ብልጽግና ህብረት ሰብሳቢ አቶ ሱልጣን እማም ሁሴን በማዕድ ማጋራት ስነ-ስርዓቱ ላይ እንደገለጹት ማዕድ ማጋራት ልመናን ከመቅረፍ ባለፈ፣ በማህበረሰቡ መካከል ያለውን ፍቅር፣ አንድነት እና የመረዳዳት እሴት ይበልጥ ያጠናክራል ብሏል።
ድጋፉ ለበዓል ብቻ የሚቆም ሳይሆን፣ ወደፊትም አቅመ ደካሞችን በዘላቂነት ለመደገፍ የሚደረገው ጥረት አካል መሆኑን ገልጸዋል።
የማዕድ ማጋራቱ ተጠቃሚ የሆኑት አቅመ ደካሞች በበኩላቸው፤ በአስቸጋሪ ወቅት የተደረገላቸውን ይህንን የበዓል አስቤዛ ድጋፍ ስለተደረገላቸው፣ስላስታወሷቸውና ከጎናቸው ስለቆሙ ያላቸውን ታላቅ ምስጋና እና ምርቃት ለግሰዋል።