Documents Authentication and Registration service

Documents  Authentication and Registration service ምንግዜም ቅድሚያ ለተገልጋይ!

የማይንቀሳቀሱ ንብረቶችን በሽያጭ/ በስጦታ ለማስተላልፍ በተመለከተ ትኩረት የሚያስፈልጋቸው ጉዳዮች ግንቦት 25 ቀን 2018 ዓ.ም 1) በስጦታ፣ በሽያጭ ወይም በሌላ መንገድ ተገልጋዮች ንብረት...
02/06/2026

የማይንቀሳቀሱ ንብረቶችን በሽያጭ/ በስጦታ ለማስተላልፍ በተመለከተ ትኩረት የሚያስፈልጋቸው ጉዳዮች

ግንቦት 25 ቀን 2018 ዓ.ም

1) በስጦታ፣ በሽያጭ ወይም በሌላ መንገድ ተገልጋዮች ንብረት ለማስተላለፍ ሲመጡ ካርታው ከጀርባው የተረጋገጠ መሆን አለበት፡፡ ካርታው ዲጂታል ከሆነ የጀርባ ማህተም አያስፈልገውም፡፡

2) በካርታው ከጀርባ ላይ ንብረቱ በውርስ የተገኘና የወራሾች ዝርዝር የተፃፈበት ከሆነ ተጨማሪ ማስረጃ ማየት ሳያስፈልግ መስተናገድ ይችላሉ፡፡ ሆኖም የንብረቱ መለያ ተጠቅሶ ወራሾች መሆናቸው በደብዳቤ ከተገለጸ አገልግሎቱን መስጠት ይቻላል፡፡

3) በውርስ ወይም በስጦታ የተገኘ ንብረትን ለማስተላለፍ ወይም ለማከራየት የጋብቻ ማስረጃ አይጠየቅም፡፡

4) ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ውጭ የተመዘገቡ የሚንቀሳቀሱም ሆነ የማይንቀሳቀሱ ንብረቶችን የማስተላለፍ ወይም የማከራየት አገልግሎት ማግኘት የሚቻለው ንብረቶቹ በሚገኙበት ክልል/ከተማ አስተዳደር ነው፡፡ ስለሆነም በአዲስ አበባ ከተማ በሚገኙ የተቋሙ ቅርንጫፍ ጽ/ቤቶች ሊስተናገዱ አይችሉም፡፡ የድሬዳዋ ቅርንጫፍ ጽ/ቤትም የሚያስተናግደው በድሬዳዋ ከተማ አስተዳደር የሚመለከተው መ/ቤት የተመዘገቡ ንብረቶችን ብቻ ይሆናል፡፡

5) ከጋብቻ በፊት በተቋሙ ቀርበው የንብረት ማግለል ውል ያደረጉ ወይም በፍ/ቤት ያጸደቁ ተጋቢዎች ንብረታቸውን ለማስተላለፍ ወይም ለማከራየት ሲመጡ የትዳር አጋራቸው ስምምነት አያስፈልግም፡፡ ሆኖም የንብረት ማግለሉ ስምምነት አሁን ጸንቶ ካለው ጋብቻ የትዳር አጋር ጋር የተደረገ ሊሆን ይገባል፡፡

6) አካለ መጠን ላላደረሱ ልጆች ንብረት ለመግዛት ቢቻል ሁለቱም ወላጆች ሊገኙ ይገባል ፡፡ ካልሆነ አባት ወይም እናት ቀርበው መግዛት ይችላሉ፡፡ ሆኖም ከእናትና አባት ውጪ የሆነ ሞግዚት አካላመጠን ባላደረሰው ልጅ ስም ንብረት ለመግዛት በፍ/ቤት የተሰጠ ተጨማሪ ስልጣን ሊቀርብ ይገባል፡፡

7) አካለ መጠን ባልደረሰው ስም ተመዝግቦ የሚገኘውን የማይንቀሳቀስ ንብረት ለመሸጥ ሞግዚቱ እናትና አባትም ቢሆኑ በፍ/ቤት የተሰጠ ተጨማሪ ስልጣን ሊቀርብ ይገባል፡፡

8 ) ያላገባ ማስረጃ ላይ ቀደም ሲል ጋብቻ ስለመኖሩ የሚጠቁም የጊዜ መረጃ ሲኖር ንብረቱ በጋብቻ ወቅት የተፈራ ሊሆን ስለሚችል ንብረቱ የተፈራበትን ጊዜ የሚያመለክት ከሚመለከተው አካል የተሰጠ ተጨማሪ ማስረጃ ሊቀርብ ይገባል፡፡

9) ተነጻጻሪ ካርታ ማለት በአንድ የቦታ ስፋት ውስጥ የተለያዩ ቤቶችና ባለመብቶች ያሉበትና በተለያዩ ሰዎች ሊያዝ የሚችል ነው፡፡ ነገር ግን በዚህ ይዞታ ላይ የባለቤትነት መብት ያለው ሰው የራሱን ካርታ በመያዝ ድርሻውን ጠቅሶ መሸጥ ይችላል፡፡

10) ካርታ ላይ የሚጠቀሰው ቀን ካርታው የተሰጠበትን ቀን እንጂ ንብረቱ የተፈራበትን ቀን በቀጥታ ላያመለክት ይችላል፡፡ ስለሆነም ንብረቱ የተፈራበትን ቀን ለማወቅ አስፈላጊ በሚሆንበት ጊዜ የንብረቱ ባለቤት ተጨማሪ ማስረጃ እንዲያቀርብ መደረግ አለበት፡፡ ለምሳሌ ከመሬት አስተዳደር ለገቢዎች እና ለካርታው ባለቤት የሚሰጡ ደብዳቤዎችን አያይዞ መስራት ይቻላል፡፡

11) የሚንቀሳቀስም ሆነ የማይንቀሳቀስ ንብረትን በሽያጭም ሆነ በስጦታ ለማስተላለፍ የፍቺ ውሳኔ ይዘው የሚቀርቡ ባለጉዳዮች ንብረቱ የጋራ ወይም የግል ስለመሆኑ በፍርድ ቤት የጸደቀ የንብረት ክፍፍል ስምምነት ወይም ውሳኔ ማቅረብ ይኖርባቸዋል፡፡

12) ንብረት በስጦታ ለማስተላለፍ የተሠጠ የውክልና ሥልጣን ስጦታው ለማን እንሚሰጥ እና ንብረቱ ምን አይነት እንደሆነ በውክልናው ላይ በግልፅ መቀመጥ አለበት፡፡ ነገር ግን በውክልና ስጦታ ለመቀበል ሲሆን ስጦታ ይቀበልልኝ የሚለው አገላለጽ በቂ ነው፡፡

13) የጋራ ንብረት በሽያጭ በሚተላለፍበት ጊዜ ገዢው ከንብረት ተጋሪው ውጪ የሆነ እንደሆነ የተጋሪው የቅድሚያ መግዛት መብት መጠበቁን ማረጋገጥ ያስፈልጋል፡፡ በመሆኑም የማይንቀሳቀስ ንብረት ሲሆን ተጋሪውን ምስክር በማድረግ፣ የሚንቀሳቀስ ንብረት ሲሆን ተጋሪው ማረጋገጫ እንዲሰጥ ማድረግ ይቻላል፡፡

14) የማይንቀሳቀስ ንብረት ገዢው የውጭ ሃገር ዜጋ ከሆነ የታደሰ በትውልድ ኢትዮጵያዊ መታወቂያ ወይም በኢንቨስትመንት አዋጁ መሠረት ቢያንስ አሥር ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር ኢንቨስት በማድረግ በሥራ ላይ ማዋሉን የሚገልጽ ማስረጃ እና የኢንቨስትመንት ፈቃድ ሊቀርብ ይገባል፡፡

15) የማይንቀሳቀስ ንብረት ገዢው የውጭ ሃገር ዜጋ ሌላ የመኖሪያ ቤት በስሙ የሌለ መሆኑን የሚገልጽ ከሚመለከተው የንብረት መዝጋቢ አካል ማስረጃ መቅረቡን እንዲሁም ከተቋሙ የመረጃ ቋት መጣራት ያስፈልጋል፡፡

ለመላው የእስልምና እምነት ተከታዮችእንኳን ለኢድ አል-አድሃ (አረፋ) በዓል በሰላም አደረሳችሁ!*******የሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎት  በዓሉ የሰላም እና የደስታ እንዲሆን ይመኛል...
26/05/2026

ለመላው የእስልምና እምነት ተከታዮች
እንኳን ለኢድ አል-አድሃ (አረፋ) በዓል በሰላም አደረሳችሁ!
*******
የሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎት በዓሉ የሰላም እና የደስታ እንዲሆን ይመኛል።

ኢድ ሙባረክ!
********
የሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎት
ምንጊዜም ቅድሚያ ለተገልጋይ!
authentication and registration service

ውክልናን  በተመለከተ ትኩረት  የሚያስፈልጋቸው ጉዳዮች ግንቦት 18 ቀን 2018 ዓ.ም 1) የአስተዳደር ተግባር በፍ/ብ/ህ/ቁ 2204 ላይ የተተረጎመው ሲሆን የወካይ ሀብት የማስቀመጥ፣ የመጠ...
26/05/2026

ውክልናን በተመለከተ ትኩረት የሚያስፈልጋቸው ጉዳዮች

ግንቦት 18 ቀን 2018 ዓ.ም

1) የአስተዳደር ተግባር በፍ/ብ/ህ/ቁ 2204 ላይ የተተረጎመው ሲሆን የወካይ ሀብት የማስቀመጥ፣ የመጠበቅ፣ ከ3 ዓመት ለማያልፍ ዘመን የማከራየት፣ በብድር የተሰጠውን ሀብት የመሰብሰብ፣ ከሀብቱ የሚመጣውን ገቢ ተቀብሎ የማስቀመጥና ለተከፈሉ እዳዎች ደረሰኝ የመስጠት ስራዎች ሁሉ እንደ አስተዳደር ተግባር ይቆጠራሉ፡፡

2) ውክልና ሰጪዎች እኛ ባልና ሚስት ብለው በማንኛውም ሠነድ የማረጋገጥ ሥልጣን በተሰጠው አካል ውክልና ከሰጡ ተወካይ በውክልናው መሰረት አገልግሎት ፈልጐ ሲመጣ በድጋሚ የጋብቻ ማስረጃ እንዲያቀርቡ መጠየቅ ሳያስፈልግ መስተናገድ ይቻላል፡፡

3) የንግድ ማህበራት በመመስረቻ ጽሁፍ እና በመተዳደሪያ ደንባቸው ላይ ስራስኪያጁ ጠበቃ እንዲወክል ግልጽ ሥልጣን ባይሰጠውም ጠበቃ መወከል ይቻላል፡፡ ሆኖም የሽርክና ማህበር ሲሆን በመመስረቻ ጽሁፍ እና በመተዳደሪያ ደንባቸው ሥራ አስኪያጁ ጠበቃ እንዲወክል መፍቀድ አለባቸው፡፡ ውሳኔው በቃለ ጉባዔ ሲሆን አባላት በሙሉ ድምጽ መወሰን አለባቸው፡፡

4) በውክልና ሥልጣን ማስረጃው ላይ ባል ለሚስት ወይም ሚስት ለባሏ ለባለቤቴ ተብሎ በተሰጠ ውክልና ላይ አንዳቸው ለመገልገል ቢመጡ በድጋሚ የጋብቻ ማስረጃ እንዲያቀርቡ አይጠይቅም፡፡

5) ወካይ በስሜ ንብረት ይግዛልኝ ብሎ በሰጠው ውክልና ተወካይ በግልጽ በጋራ ይግዛልኝ ካላለው በስተቀር ከሌላ ሰው ጋር በወካዩ ስም በጋራ መግዛት አይችልም፡፡

6) እናት እና አባት ወይም ሞግዚት ሆነው የተሾሙ አባት ወይም እናት ሞግዚት ለሆኑለት ልጅ የልደት ሠርተፍኬት እና ልዩ ልዩ ሰነዶች ማውጣትና መቀበልን ጨምሮ ንብረት ማስተዳደርን በተመለከተ ውክልና መስጠት ይችላሉ፡፡

7)በፍ/ቤት የተሾመ ማንኛውም ሞግዚት ንብረት ማስተዳደርን በተመለከተ 3ኛ ወገን ለመወከል ቢፈልግ ይህን የሚገልጽ ተጨማሪ ስልጣን ከፍ/ቤት ማምጣት አለበት፡፡

8. )ውል ለማዋዋል ስልጣን በተሰጠው አካል የተሰጠ የውክልና ስልጣን በተቋሙ ቀርቦ መሻር/መተው ይቻላል፡፡

9) ብዙ ሰዎች በአንድነት ውክልና ሰጥተው እያለ አንደኛው ወካይ ብቻውን መጥቶ ተወካዩን መሻር ከፈለገ በፍ/ብ/ህ/ቁ/ 2228 /2/ መሠረት ተወካዩን ለመሻር በቂ ምክንያት ነው ብሎ ያመነበትን በመሻሪያ ሰነዱ ውስጥ አካቶ ተወካዩን መሻር ይችላል፡፡ ውክልና በጋራ ሲሰጥ ጉዳያችን አንድ አይነት ነው ከሚለው በተጨማሪ የጋራ የሚባለውን ጉዳይ መግለጽ ያስፈልጋል፡፡

10).ተወካይ በውክልና ሰነዱ ውስጥ 3ኛ ወገን እንዲወክል ያልተፈቀደለት ቢሆንም በፍ/ሕ/ቁጥር 2215 /3/ ላይ በተቀመጠው መሰረት፡-

√ ድንገተኛ መሰናክል የገጠመው መሆኑን፤

√ የተባለውን ሥራ ለመሥራት የመልካም ሥራ አመራር ያስገደደው መሆኑን፤

√ ስለ ጉዳዩ ለወካዩ ለማሳወቅ ጊዜ የሚያጥረው መሆኑን ገልፆ ለአስተዳደራዊ ተግባራት ብቻ 3ተኛ ወገን ሊወክል ይችላል፡፡

ስነ ምግባርን ያካተተ የአመራርነት ብቃት ስልጠና  ተሰጠ ፡፡ግንቦት 17 ቀን 2018 ዓ. ም በሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎት ለድሬደዋ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት አመራርና ሰራተኞች የህይወት ክ...
25/05/2026

ስነ ምግባርን ያካተተ የአመራርነት ብቃት ስልጠና ተሰጠ ፡፡

ግንቦት 17 ቀን 2018 ዓ. ም

በሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎት ለድሬደዋ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት አመራርና ሰራተኞች የህይወት ክህሎትና የአመራር ብቃት አካቶ ትግበራ ስልጠና ተሰጠ።

በተቋሙ የሴቶችና ማህበራዊ ጉዳይ አካቶ ትግባራ ስራ ክፍል አዘጋጅነት በድሬደዋ ከተማ ለ አራት ቀናት በተካሄደው የህይወት ክህሎት እና የአመራርነት ብቃት አካቶ ትግበራ እንዲሁም የስራ ላይ ስነ ምግባር ስልጠና ላይ የቅርንጫፍ ጽ/ቤቱ አመራሮችና ባለሙያዎች ተሳትፈዋል።

ከሴቶችና ህጻናት ሚኒስቴር በመጡት አሰልጣኝ የተሰጠው ይህ ስልጠና ሰራተኞች ያላቸውን አቅምና እዉቀት እንዲገመግሙና ክህሎታቸውን ከማጎልበቱ ባሻገር ልምድ እንዲለዋወጡ ከፍተኛ ጠቀሜታ እንደሚኖረው የሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎት የድሬዳዋ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት ስራ አስኪያጅ ወ/ሮ ትእግስት አየለ ገልጸዋል፡፡ ስራ አስኪያጇ አክለውም «እንደዚህ አይነት ስልጠናዎች በየወቅቱ መሰጠት አለባቸው» ሲሉም ያሳሰቡ ሲሆን፤ በሰልጣኞች የነቃ ተሳትፎ እንዲደረግም ጥሪ አቅርበዋል።

የስልጠናዉ አላማ የሕይወት ክህሎቶች ላይ ግንዛቤ ለመፍጠር፣ መሰረታዊ የሆኑ የሕይወት ክህሎቶችን ለይቶ ለመረዳት እና በስራ ቦታ ላይ ምቹ ስነምህዳርን ለመፍጠር አስቻይ ሁኔታን ለመፍጠር እንዲሁም ዜጎች በተሰማሩበት የስራ መስክ ውጤታማ እና ብቁ እዲሆኑ ለማስቻል ያለመ መሆኑ በመድረኩ ላይ ተገልጿል።

ስልጠናው የሴት አመራሮች የአመራርነት ክህሎትን ከማሳደግ ባሻገር የመሪነትን ጽንሰ ሃሳብን ላይ በበቂ ሁኔታ ግንዛቤ ለመስጠት እና ያላቸውንም መልካም ተሞክሮዎች እንዲያዳብሩ ከፍተኛ ጠቀሜታን እንደሚያስገኝ እንዲሁም በሰራ ቦታ ከተገልጋዮች ጋር የሚኖር ተግባቦት እና በተሰማሩበት የስራ መስክ ላይ የሚኖር ስኬታማነትን የሚመለከት የእውቀትና ክህሎት ያካተተ ነበር፡፡

በስልጠናው 49 ሰልጣኛች የተሳተፉ ሲሆን፤ 32 ሴቶች እና 17ቱ ወንድ ሰራተኞች ናቸው፡፡

 #መረጃ
18/05/2026

#መረጃ

የቃብድ (Earnest) ምንነትና ሕጋዊ ማዕቀፍ
መግቢያ
ሰዎች በእለት ከእለት እንቅስቃሴያቸው የተለያዩ ሕጋዊ ተግባራትን ያከናውናሉ። ከእነዚህ ሕጋዊ ተግባራት አንዱ ውል ነው። ጠዋት ታክሲ ከመሳፈር ጀምሮ የተለያዩ ሸቀጦችን መግዛት፣ ቤት መከራየት፣ የተለያየ ዋጋ ያላቸውን ንብረቶች መሸጥና መግዛት በየእለቱ በሰዎች የሚከናወኑ የውል ውጤቶች ናቸው። ውል በሁለትና ከዚያ በላይ በሆኑ ሰዎች መካከል የሚደረግ ለአንዱ ወገን መብትን የሚሰጥ፣ ለሌላው ወገን ተነጻጻሪ ግዴታን የሚጥል ሕጋዊ ስምምነት ነው። በዚህ ስምምነት ሂደት እንደውሉ ሁኔታ ተዋዋይ ወገኖች ውል ለመፈጸሙ ማረጋገጫ ይሆናቸው ዘንድ ቃብድ ሊቀባበሉ ይችላሉ፡፡ በዚህ ጽሑፍ የቃብድን ምንነትና በአገራችን ያለውን ሕጋዊ ማእቀፉ በአጭሩ እንመለከታለን፡፡

የቃብድ ምንነት
በ1993 ዓ.ም በኢትዮጵያ ቋንቋዎች ጥናትና ምርምር ማዕከል የታተመው የአማርኛ መዝገበ ቃላት (ገጽ 176) ቃብድ (ቀብድ) እቃን ለመግዛት ወይም ለማሰራት በቅድሚያ የሚከፈል ገንዘብ፣ መያዣ እንደሆነ ትርጉም ሰጥቶታል። በሌላ በኩል ብላክ የሕግ መዝገበ ቃላት በ8ኛ እትሙ (Black’s Law Dictionary, 8th ed.) “Earnest is a nominal payment or token act that serves as a pledge or a sign of good faith, esp. as the partial purchase price of property”. በሚል ይተረጉመዋል። ይህ ወደ አማርኛ ሲመለስ ቃብድ ማለት በተለይም ለአንድ ንብረት ግዥ እንደ መያዣ ወይም ቅን ልቦና መገለጫ የሚሰጥ አነስተኛ ክፍያ ሲሆን ይህም አብዛኛውን ጊዜ ከጠቅላላው የሽያጭ ዋጋ ላይ በከፊል የሚታሰብ ክፍያ ነው የሚል ይሆናል።

የቃብድ ሕጋዊ ማዕቀፍ
የፍትሐብሔር ሕግ ከቁጥር 1883 እስከ 1885 ስለቃብድ የደነገገ ሲሆን በእነዚህ ድንጋጌዎች መሠረት ቃብድ እንደ ውል ማረጋገጫ ተደርጎ ይቆጠራል። ይኸውም አንዱ ወገን ለሌላኛው ወገን ቃብድ መስጠቱ በማያከራክር ሁኔታ ውል መደረጉን እንደሚያረጋግጥ በፍትሐብሔር ሕጉ በቁጥር 1883 በግልጽ ተደንግጓል። በዚህም ቃብድ ውሉ በቁርጠኝነት እንዲቀጥል የመፈጸም ፍላጎት ማሳያ ነው። ውሉ ሲፈጸምም ሌላ ተቃራኒ ስምምነት ከሌለ በስተቀር ቃብድ የተቀበለው ወገን በፍትሐብሔር ሕጉ ቁጥር 1884 መሠረት ከሚገባው ገንዘብ ላይ ታሳቢ ያደርጋል ወይም ቀብድ ለሰጠው ወገን ተመላሽ ያደርጋል። ለምሳሌ በሽያጭ ውል ላይ ውሉ ሲፈጸም ለሻጭ የተሰጠው ቃብድ ከሽያጭ ዋጋው ላይ ታሳቢ ይደረጋል።

ሌላው እዚህ ጋር የሚነሳው ውሉ ቢፈርስ የቃብዱ እጣ ፈንታ ምን ይሆናል የሚለው ሲሆን ለዚህም የፍትሐብሔር ሕጉ ቁጥር 1885 ግልጽ መፍትሔ አስቀምጧል። ይኸውም
 ቃብድ የሰጠው ሰው ውሉን ካፈረሰ የሰጠውን ቀብድ የማስመለስ መብት የለውም። ውል ማፍረስ የሚችለው ቃብዱን በመተው ነው። በአንፃሩ ቃብድ የተቀበለው ሰው ውሉን ካፈረሰ የተቀበለውን ቃብድ እጥፍ አድርጎ ለሰጪው የመመለስ ግዴታ አለበት።

እዚህ ጋር ልብ ሊባል የሚገባው የቃብድ ገንዘብ ተቀባዩ የተቀበለውን ቃብድ አጠፌታ ከፍሎ ውሉን እንዲያፈርስ የሚገደደው በግራ ቀኙ ወገኖች መካከል ሕጋዊ ሥርዓቱን የጠበቀ የፀና ውል ሲኖር ስለመሆኑ የፌዴራል ሰበር ሰሚ ችሎት በቅጽ 26 በሰ/መ/ቁ. 211204 እና 215762 አስገዳጅ የሕግ ትርጉም ሰጥቶበታል። በእነዚህ ውሳኔዎችም ቃብድ ከሽያጭ ዋጋ ከፊል/ቅድሚያ/ ክፍያ የሚለይበት መንገድ ተገልጿል። ይኸውም ውሉ ሲፈርስ ቅድመ ክፍያ በሆነ ጊዜ ግራ ቀኙ ከውሉ በፊት ወደነበሩበት ሁኔታ ይመለሳሉ። ስለሆነም በቅድመ ክፍያ ጊዜ ሻጭ ውሉን ቢያፈርስ የተከፈለው ገንዘብ ብቻ ለገዥ ተመላሽ የሚደረግ ሲሆን ቃብድ ተከፍሎ የነበረ ሲሆን ሻጭ ውሉን ቢያፈርስ የቃብዱን አጠፌታ ለገዥ የመክፈል ግዴታ አለበት።(የፍትሐብሔር ሕግ ቁጥር 1885(2)፣ 1815(1))

ማጠቃለያ
በተለያዩ የውል ሂደቶች ቃብድ መክፈልም ሆነ መቀበል የራሱ የሆነ ውጤት ያስከትላል። በተለይም በሽያጭና ኪራይ ውል ሂደት ቀብድ መክፈልና መቀበል የተለመደ ሲሆን ቃብድ ሰጪ ውሉን ካላከበረ የከፈለው ገንዘብ እንደማይመለስ፣ ተቀባይ ደግሞ ውሉን ካላከበረ የወሰደውን ገንዘብ እጥፍ አድርጎ የመመለስ ግዴታ ሊመጣ እንደሚችል ተገንዘቦ በጥንቃቄ መዋዋል ይገባል። ከዚህም በተጨማሪ ውሉ አስፈላጊ የሆኑ ሕጋዊ ፎርማሊቲዎችን መጠበቅ እና ቃብድ መሆኑ በግልጽ መስፈር እንዳለበት ግንዛቤ ሊወሰድ ይገባል።

በንቃተ ሕግና ሥልጠና ዳይሬክቶሬት የተዘጋጀ

የፍትሕ ሚኒስቴርን የማህበራዊ ሚዲያ ትስስር ገፆችን እና ድረ-ገፅን ይቀላቀሉ
Website
https://www.justice.gov.et
Facebook
https://www.facebook.com/MOJEthiopia/
(x) Twitter
https://x.com/MOJEthiopia
YouTube channel
https://youtube.com/...3701...
Telegram
https://t.me/fdreattorneyGeneral_externa

ሌላ የአገልግሎት የክፍያ አማራጭ የሰነዶች ማረጋገጫ እና ምዝገባ አገልግሎት ክፍያዎንበሲቢኢ ብር በቀላሉ ይፈፅሙ! ✅  የሲቢኢ ብር ፕላስ መተግበሪያዎን ከፍተው 'ክፈል’ / ‘Pay’ ወደሚለው...
14/05/2026

ሌላ የአገልግሎት የክፍያ አማራጭ

የሰነዶች ማረጋገጫ እና ምዝገባ አገልግሎት ክፍያዎን
በሲቢኢ ብር በቀላሉ ይፈፅሙ!


✅ የሲቢኢ ብር ፕላስ መተግበሪያዎን ከፍተው 'ክፈል’ / ‘Pay’ ወደሚለው አማራጭ ይግቡ፤

✅ ‘ሂሳብ ክፍያ’/ ‘Pay Bill’ የሚለውን ይምረጡ፤

✅ ‘Gov Services’ የሚለውን ተጭነው ወደ ‘Dars (Documents Authentication and Registration Service)’ አማራጭ ይግቡ፤

✅ የቢል ማጣቀሻ ቁጥር (Bill Reference Number) አስገብተው የክፍያ መጠኑን በማረጋገጥ ክፍያዎን ይፈፅሙ፡፡

**************
#ክፍያዎን

ይህንን ያውቃሉ? ግንቦት4 ቀን 2018 ዓ.ም የሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎት  በቀን ከስድስት ሺህ በላይ ተገልጋዮች በማስተናገድ  በርካታ  ልዩ ልዩ አገልግሎቶችን ተደራሽ  እያደረገ...
12/05/2026

ይህንን ያውቃሉ?

ግንቦት4 ቀን 2018 ዓ.ም

የሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎት በቀን ከስድስት ሺህ በላይ ተገልጋዮች በማስተናገድ በርካታ ልዩ ልዩ አገልግሎቶችን ተደራሽ እያደረገ ይገኛል፡፡ ከነዚህ አገልግሎቶች አንዱ ከጋብቻ በፊት የሚደረግ የግል ንብረትን ማግለል ውል ሰነድ አረጋግጦ መመዝገብ፣ (የቤተሰብ ህ/ ቁ/42) ነው፡፡

*ይህንን አገልግሎት ለማግኘት ተገልጋዮች ማሟላት ያለባቸው ቅድመሁኔታዎች የሚከተሉት ናቸው :-

ሀ. የሚረጋገጠውን የውል ሰነድ ይዘት በተቋሙ የአገልግሎት መስጫ ሲስተም ተሞልቶ የጉዳይ መከታተያ ቁጥር መያዝ ፤

ለ. የፈራሚዎች አና የእንዳንዳቸው ሁለት ሁለት ምስክሮች፤ የነዋሪነትና እና ፋይዳ መታወቂያ ፤

ሐ. የተዋዋዮች የአገልግሎት ጊዜው ያላለፈበት ያላገባ ማስረጃ ፤

መ. የሚገለለው ንብረት የባለቤትነት ማስረጃ ፡፡

የጥልቅ ሐዘን  መግለጫበተቋማችን ቅርንጫፍ አራት ጽ/ቤት በሰነድ ማረጋገጥና መመዝገብ የስራ መደብ ሲያገለግሉ የነበሩት አቶ አዳሙ ኤልያስ ገለልቻ በተወለዱ በ45 ዓመታቸው በድንገተኛ ህመም ከ...
11/05/2026

የጥልቅ ሐዘን መግለጫ

በተቋማችን ቅርንጫፍ አራት ጽ/ቤት በሰነድ ማረጋገጥና መመዝገብ የስራ መደብ ሲያገለግሉ የነበሩት አቶ አዳሙ ኤልያስ ገለልቻ በተወለዱ በ45 ዓመታቸው በድንገተኛ ህመም ከዚህ ዓለም ድካም በሞት ተለይተዋል፡፡

አቶ አዳሙ ኤልያስ ገለልቻ ስርአተ የቀብር ስነ ስርአት የሚፈጸመው ዛሬ ከቀኑ 7:00 ሰዓት በሸገር ከተማ አስተዳደር ቡራዩ ማርያም ማዘጋጃ አካባቢ ነው፡፡

የሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎት አመራር እና ሰራተኞች በአቶ አዳሙ ድንገተኛ ህልፈት የተሰማንን ጥልቅ ሀዘን እየገለጽን ፈጣሪ ነፍሳቸውን በአጸደ ገነት እንዲያሳርፍል፤ ለቤተሰብና ወዳጆቻቸው መጽናናትን እንዲሰጥ ከልብ እንመኛለን ፡፡

ነፍስ በሰላም በአጸደ ገነት ትረፍ::

ዋና ዳይሬክተር አቶ ሀሚድ ኪኒሶ የቴሌሳይን አገልግሎትን በተመለከተ  ከአዲስ ዘመን ጋዜጣ ጋር ያደረጉት ቆይታ ክፍል 2  አዲስ ዘመን ጋዜጣ ሚያዚያ 28  ቀን 2018 ዓ.ም እትም የፌዴራል ...
06/05/2026

ዋና ዳይሬክተር አቶ ሀሚድ ኪኒሶ የቴሌሳይን አገልግሎትን በተመለከተ ከአዲስ ዘመን ጋዜጣ ጋር ያደረጉት ቆይታ

ክፍል 2

አዲስ ዘመን ጋዜጣ ሚያዚያ 28 ቀን 2018 ዓ.ም እትም

የፌዴራል ሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎት የሰነድ ማረጋገጥ አገልግሎትን ሙሉ በሙሉ በዲጂታል አማራጭ ለማከናወን የሚያስችል “ቴሌ-ሳይን” የተሰኘ አገልግሎት መጋቢት 22 ቀን 2018 ዓ.ም. ይፋ አድርጓል። ኢትዮ- ቴሌኮም ከውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር፣ ከፍትህ ሚኒስቴር እና ከፌዴራል ሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎት ጋር በመተባበር ደህንነቱ የተጠበቀ፣ ድንበር ተሻጋሪ እና ዜጋ-ተኮር አገልግሎቶችን ለመስጠት የሚያስችል ብሄራዊ የዲጂታል ፊርማ ወይም “ቴሌ-ሳይን” የተሰኘ አገልግሎትን በይፋ አስጀምረዋል። የቴሌ-ሳይን አገልግሎት ከዓለምአቀፍ ህጎች ጋር የተጣጣመ በመሆኑ፣ በውጪ ሀገር የሚገኙ ዜጎች ጭምር ባሉበት ሆነው መጠቀም የሚችሉበት መሆኑ ተነግሯል።

ተለምዷዊ የሆነውን የማንዋል የአገልግሎት አሰጣጥን ወደ ሙሉ ዲጂታል ተሞክሮ በመቀየር ለሀገራዊ የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን መፋጠን የላቀ ሚና የሚጫወት ቴክኖሎጂ እንደሆነም ታውቋል። ማንኛውም አገልግሎቱን መጠቀም የሚፈልግ ዜጋ የቴሌ- ሳይን መተግበሪያን ከፕለይ ስቶር በማውረድ እና መስፈርቶች በማሟላት መጠቀም እንደሚቻል ተጠቁሟል። ይህ ሀገራዊ ሥርዓት በኢትዮጵያ የዲጂታል ትራንስፎርሜሽን ጉዞ ውስጥ ትልቅ የታሪክ ምዕራፍ መሆኑም ተጠቅሷል። ቴሌ-ሳይን በዲጂታል መንገድ ከሚያከናውናቸው ዋና ዋና አገልግሎቶች መካከል አንዱ የውክልና ሥልጣን ሲሆን፣ ይህም የዳያስፖራው ማኅበረሰብም ሆነ በሀገር ውስጥ የሚገኙ ዜጎች በአካል ኤምባሲ ወይም ቢሮ ሳይገኙ የውክልና ሥልጣን ለመስጠትም ሆነ ውክልናቸውን ለማንሳት ያስችላቸዋል። በባለፈው አምዳችን ቴሌ-ሳይን እየሰጠ ያለውንአገልግሎት በተለይ አገልግሎት ምን ማለት እንደሆነ፣ አገልግሎቱን ማስጀመር ለምን እንዳስፈለገ፣ በተቋሙ ምን ምን አገልግሎቶች በቴሌ-ሳይን እንደተካተቱና በሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች ላይ የፌዴራል ሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎት ዋና ዳይሬክተር አቶ ሀሚድ ኪኒሶ ማብራሪያ ሰጥተዋል።

በዛሬው አምዳችን ደግሞ የቴሌ-ሳይን አገልግሎት የሚያገኙት እነማን እንደሆኑ፣ አገልግሎቱን ለማግኘትስ ምን ማከናወን እንደሚያስፈልግ ለአቶ ሀሚድ ኪኒሶ ጥያቄ አቅርበንላቸው የሚከተለውን ምላሽ ሰጥተዋል።

አዲስ ዘመን፡- የቴሌ-ሳይን አገልግሎት የሚያገኙት እነማን ናቸው? አገልግሎቱን ለማግኘትስ ምን ማከናወን ያስፈልጋል?

አቶ ሀሚድ፡- አገልግሎቱን ማግኘት የሚችለው ሰፊው ተገልጋይ ህዝብ ነው። አገልግሎቱ ለሁሉም ክፍት ነው። የትኛውም የማህበረሰብ ክፍል አገልግሎቱን ማግኘት ይችላል። አስተዳደራዊ ውክልና ግለሰብም ድርጅቶችም ሊሰጥ ይችላል። ስለዚህ ለማንም ክፍት ነው። እከሌ የሚባል የተገደበ የለም። ተገልጋይ የአስተዳደራዊ ውክልና እሰጣለሁ፣ የትምህርት ዶክመንቴን እንዲያወጣልኝ እሰጣለሁ፣ ንብረቴን የሆነ ነገር እንዲያስተዳድርልኝ እሰጣለሁ፣ የጠበቃ ውክልና ለእከሌ እሰጣለሁ፣ ክስ ያለበት ወይም ደግሞ ለመክሰስ ሲፈልግ ማንኛውም ሊሆን ይችላል። ስለዚህ ከማህበረሰቡ አንፃር የተገደበ አይደለም። ለሁሉም ክፍት የሆነ ነው። ቴሌ-ሳይን አገልግሎት ለማግኘት ከሚያስፈልጉ ነገሮች አንዱ እንዳልኩት የፋይዳ ተመዝጋቢ መሆን ነው። ይህንን አገልግሎት ለመጀመር መታወቂያ የሚሆን የፋይዳ መታወቂያ ነው። የፋይዳ ተመዝጋቢ መሆን አለባቸው። የፋይዳ ቁጥር መያዝ ይኖርባቸዋል። ሌላኛው እንደአገልግሎት አይነቱ ይለያያል። ለምሳሌ የጠበቃ ውክልና ከሆነ የጠበቃ ፈቃዱን፣ ወይም ደግሞ ቁጥሩን ወይም የተለያዩ መረጃዎችን ሊሆን ይችላል። አስፈላጊ መረጃ ሲስተሙ የሚጠይቀውን መረጃ ለመሙላት መረጃ ሊኖራቸው ይገባል። የሌሎች ውክልናዎችም ከሆኑ የቤተሰብ ከሆነ ዝምድናቸውን የሚገልፅ ነገር ያስፈልጋል;;
ለአብነት ባልና ሚስት ከሆኑ ባልና ሚስት መሆናቸውን የሚያሳይ መረጃ ሊኖር ይገባል። አስተዳደራዊ ውክልና ከሆነ ደግሞ ብዙ ነገር አያስፈልገውም። እሱ ላይ ዋነኛው ብሄራዊ መታወቂያ ካለው የተለየ መረጃ ስለማይጠይቅ አገልግሎት ማግኘት ይችላሉ። ሌላኛው የሚያስፈልገው ነገር ቀደም ሲል እንደነበረው የአገልግሎት ክፍያ ነው። ቀደም ሲል ቀጥታ በአካል የሚመጡ ይከፍሉ የነበረውን መክፈል ያስፈልጋል። ከዚያም ባሻገር ከኢትዮ-ቴሌኮም ጋር አሁን ስምምነት ውስጥ ስንገባ ተጨማሪ የአገልግሎት ክፍያ ኢትዮ-ቴሌኮም የሚያስከፍለው አለ። 450 ብር ተጨማሪ ክፍያ ያስከፍላል። ይህንን ሲስተም ኢትዮ-ቴሌኮም ሲያለማ ወጪ አለውና ማህበረሰቡ ጊዜ ሳያባክን፣ ቤቱ ሆኖ የታክሲና የሌሎች ወጪዎች ሳይኖሩበት ቤቱ ሆኖ አገልግሎቱን ስለሚያገኝ ማለት ነው። በመጨረሻ ሰርቲፊኬት (የምስክር ወረቀት) እዚያው ኦንላይን ላይ ማግኘት ይቻላል። የምስክር ወረቀቱ በኢሜይሉ ነው የሚመጣለት። አትሞ ማውጣት ብቻ ነው።

አዲስ ዘመን፡- በአገልግሎቱ ተጠቃሚ ይሆናሉ ተብለው የሚታሰቡ አካላትን ቴሌ-ሳይን እንደተጀመረ የማስተዋወቁ ሥራ ምን ያህል ነው?

አቶ ሀሚድ፡- ከማስተዋወቁ ጋር በተያያዘ እንግዲህ ማስተዋወቅ የጀመርነው መጋቢት 22 ቀን 2018 ዓ.ም. ነው ለማህበረሰቡ ይፋ የተደረገው። ሁሉም ባለበት ኢትዮ-ቴሌኮምም እኛም እንደዚሁ ደግሞ ባለድርሻ አካላት ባሉበት ሚዲያ በተገኘበት ላውንች(ይፋ) የተደረገ ስለሆነ አንዱ በሚዲያ ማስተዋወቅ ነው። ከዚያ ጀምሮ ማስተዋወቅ የተጀመረበት ነው። ሌላው ደግሞ ማህበራዊ ሚዲያዎችን የተቋማቱን ማህበራዊ ሚዲያ በመጠቀም አስተዋውቀናል። በብሮሸሮች(በራሪ ወረቀቶች) በዚህ አግባብ የማስተዋወቅ ሥራ ተጀምሯል። ይህ ይሁን እንጂ በቂ ነው ብለን አናምንም። ተጨማሪ የማስተዋወቅ ሥራዎች መሠራት አለባቸው። የማስተዋወቅ ሥራው መሠራት ያለበት ከሁለት ጉዳይ አንፃር ነው። አንዱ ተገልጋዩ ይህንን የአገልግሎት አይነት መጀመሩን አውቆ እንዲገለገልበት ከማድረግ አንፃር ማስተዋወቅ ያስፈልጋል። ሁለተኛው ደግሞ ይህን ዶክመንት/ማስረጃ ተገልጋዮች አሁን ከወሰዱ በኋላ ወደ ሌላ አካል ሄደው ነው ተግባራዊ የሚያደርጉት። ለምሳሌ የአንድ ጠበቃ ውክልና የሰጠ ሰው ውክልናው የት መሄድ አለበት? ፍርድ ቤት ላይ ሄዶ ነው ሥራ ላይ የሚውለው፤ ወይም ደግሞ ሌላ አካል ጋ ሄዶ ሥራ ላይ ይውላል። ስለዚህ ሌሎች አካላት ቀደም ብለው ከለመዱት ከወረቀት ውክልና አሁን ይለይባቸዋል። የኦንላይን አገልግሎቱ ማስረጃ ቀደም ሲል ከነበረው ይለያል። ስለዚህ ይህ አገልግሎት መጀመሩ፣ ሲስተሙ መጀመሩ አገልግሎት ሰጪ ሌሎች አካላትም ማወቅ ስላለባቸው ከዚህ ከሁለቱ አንፃር ማስተዋወቅ ይጠበቅብናልና እንደቅርብ ጊዜ መጀመሪያችን በቂ ነው የማስተዋወቅ ሥራ ተካሂዷል ብለን አናምንም። ከተጀመረ ሶስት ሳምንት እንደዚህ ሆኖታልና ስለዚህ በቂ ማስተዋወቅ ሥራ እየሠራን ተጨማሪ አገልግሎቶችን ደግሞ በተለይ እየጨመርን ስንሄድ ማህበረሰቡ እያወቀው ይሄዳል ብለን እናምናለን

አዲስ ዘመን፡- የቴሌ-ሳይን አገልግሎትመስጠት ከተጀመረ በኋላ ምን የታየ ተግዳሮት አለ? ተግዳሮቱን ለመፍታትስ የተከናወነ ተግባር ካለ ቢጠቀሱልን?

አቶ ሀሚድ፡- ከተግዳሮቱ አንዱ አዲስ አሠራር መሆኑ ነው። አዲስ ነገር ሲመጣ ከለመድነው ለመላቀቅ ከባድ ነው (resistance to change)። የተለመደው የወረቀት ነው፣ ወረቀት መታቀፍ ነው። ለቴክኖሎጂ ቅርብ አለመሆን ችግር አለ። ከዚህ ጋር ተያይዞ በተቋሙ ውስጥ ራሱ ያለው ከለመደው ወጥቶ የወረቀት ሥራውን ትቶ ባለንብረቱ ሳይመጣ ሲስተም ውስጥ ብቻ አይቶ ያንን አፕሩቭ አድርጎ (አፅድቆ) ለማለፍ የአእምሮ ዝግጁነት ያስፈልጋል። በራሱ አዲስ ነገር ስለሆነ እሱንም ማሳመኑና ባለሙያውን ችግር የለውም፤ ሪስክ/ችግር/ አያመጣም፤ ብሎ እንዲያምን ማድረግ ራሱ ሥራ የሚፈልግ ነው። እንደገና ደግሞ ከማህበረሰቡ አንፃር ማህበረሰቡም አንደኛ ከማወቅ አንፃር፣ መረጃ ከማግኘት አንፃር እንደ ተግዳሮት የሚታይ ነው። ሁለተኛ ደግሞ መረጃው ራሱ ቢኖር ለቴክኖሎጂ ቅርብ ያለመሆን ጉዳይ እንደ አንድ ተግዳሮት የሚታይ ነው።
አዲስ ዘመን፡- የቴሌ-ሳይን አገልግሎት መሰጠት ከተጀመረ በኋላ የአገልግሎቱ ተጠቃሚዎች እርካታ ምን ይመስላል?

አቶ ሀሚድ፡- የማስተዋወቅ ሥራው በጅምር ላይ ቢሆንም በመጀመሪያው ካስተዋወቅንበት ጊዜ ጀምሮ ህብረተሰቡ ደስተኛ ነው። ምክንያቱም ከዚህ ቀደም ይህን አይነት አገልግሎት ለማግኘት ሲያወጣ የነበረው ጊዜ፣ ይጨርስ የነበረው ገንዘብ ቀላል አይደለም። እንግልቱ ቀላል አይደለም። ሌላ ሥራ ነው፤ ሥራ ነው ይሆንባችሁ የነበረው። ይሄ የቴሌ-ሳይን አገልግሎት በጣም ድራማቲክ ነው የሚሆንባቸው። ‹‹እንዴ! እውነት ነው እንዲህ አይነት ነገር?! ምን ማለት ነው?! ይሄን አገልግሎት በቃ የትም ሳልሄድ ቤቴ ወንበር ላይ ቁጭ ብዬ በራሴ የምጨርስበት። እዛ ሳልሄድ ሁሉ ነገር የሚያልቅበት። ይሄ ነገር በጣም ድራማቲክ የሆነ ሺፍት ነው›› ይላሉ። ከፍተኛ አድናቆትን ከፍተኛ እርካታን ያፈራንበት ጉዳይ ነው፡፡ እንደአጠቃላይ ሲታይም መንግስትም ይህን መሰል አገልግሎቶች እንዲሰጡ እየሠራ ስለሆነ ህብረተሰቡ የለውጡ መንግስትን በከፍተኛ ሁኔታ ሲያመሰግን የነበረበት እና ይሄ ሊበረታታ ሊጠናከር እንደሚገባ የሚገልጽበት ሁኔታ ነው ያለው። ሁሉም ዜጋ እንዲጠቀምበት የማስተዋወቁን ሥራ በስፋት በመሥራት በቀጣይ የተገልጋዩን ቁጥር ለማብዛት ተግተን እንሠራለን። ሠራተኛውንም እያሰለጠን፤ እያለማመድን፤ እንሄዳለን። አንዳንድ ነገሮችንም ደግሞ ከባለጉዳይ/ ከተገልጋይ አኳያ እያየን አስተያየት እየወሰድን እያረምን፣ እያዳበርን እየሄድን ያለበት አግባብም አለ።

አዲስ ዘመን፡- የቴሌሳይን አገልግሎት ህብረተሰቡ ተጠቃሚ እንዲሆን የሚያስተላልፉት መልዕክት?
አቶ ሀሚድ፡- የማስተላልፈው መልዕክት የሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎት ሁሌ በለውጥ ውስጥ ያለ ተቋም ነው። ህብረተሰቡን ቀለል ባለ ሁኔታ እያገለገለ ይገኛል። እንደ ሌላ ተቋም በሥራ ሰዓት ብቻ የተገደበ አይደለም አገልግሎቱ። የምሳ ሰዓት እኛ ተቋም ክፍት ነው። እስከ ምሽት አንድ ሰዓት አገልግሎት እንሰጣለን። ቅዳሜ ሙሉ ቀን አገልግሎት እንሰጣለን። በተለያየ አግባብ የህብረተሰቡ ፍላጎት እስከአሁንለመጠበቅ ልዩ አገልግሎት የሚባለውን ጭምር አለን። መደበኛውን አገልግሎት ለማግኘት ወረፋ ለሚሆንበት እና ለሚቸኩሉት ልዩ አገልግሎት ተብሎ እስከማመቻቸት ደርሰናል። እንደውም ወደተቋሙ ሳይመጡ፣ ሳይሰለፉ በኦንላይን ወረፋ የሚይዙበት ስርዓት ተግባራዊ አድርገናል። ሀሰተኛ ሰነድን እና ማጭበርበርን ለመቀነስ ብዙ ጥረት አድርገናል። ይህን መሰል ተግባር በማከናወኑ ሁሌ በለውጥ ውስጥ ያለ ተቋም ነው። ለተገልጋይ እርካታ የሚሠራ ተቋም መሆኑ ይታወቃል። አሁን ከደረስንበት አንጻር ደግሞ የ2030 ዲጂታል ስትራቴጂን ሥራ ላይ ከማዋል አንጻር በአንድ በኩል አገልግሎታችን መሶብ እንዲገባ ተደርጓል። የመሶብ አንድ አገልግሎት በአሁኑ ሰዓት አዲስ አበባ ላይ ስድስት ደርሷል። የፌዴራሉ አንድ አለ አዲስ አበባ ውስጥ ሰባት ማዕከላት ላይ ገብተናል። የመሶብ አገልግሎት ማለት ሁሉም ተቋማት እዛው ኖረው ተገልጋዩ እዛው ጀምሮ እዛው ጉዳዩን የሚጨርስበት እና ቀልጣፋ አገልግሎት የሚሰጥበት ነው። ስለዚህ ህብረተሰባችን እንዲያውቀው የሚገባው ወደ አስራ አምስት አገልግሎት ነው ተቋማችን መሶብ ውስጥ ያስገባው። በቀጣይ ደግሞ ሁሉንም አገልግሎት መሶብ እንዲገባ እየሠራን ነው። ሁሉም አገልግሎት ወረቀት አልባ እንዲሆን እየሠራን ነው ያለነው። በአጭር ጊዜ ውስጥ ከወረቀት እንላቀቃለን፤ ዲጂታላይዝ ይሆናል። የመሶብ አገልግሎትም ቢሆን በአካል ሄዶ ነው እስካሁን ሲገለገሉበት የነበረው። እሱንም ጭምር የሚያስቀር ተገልጋዩ ካለበት ሆኖ አገልግሎት የሚያገኝበት ስርዓት እየጀመርን ስለሆነ አሁን በጀመርነው በቴሌ-ሳይን አገልግሎት ወደ ተቋማችን መምጣት ሳያስፈልግ በተለያዩ ማህበራዊ ሚዲያ፣ በፌስቡካችን፣ በሌሎች ሚዲያዎች እና በዌብሳይታችን ላይ በተገለጸው መሰረት የቴሌሳይን መተግበሪያከአፕስቶር በማውረድ እና ቅደም ተከተሉን መሰረት በማድረግ የሚፈልጉትን አገልግሎት ሳይለፉ፣ ወጪ ሳያወጡ ጊዜያቸውን ተጠቅመው ከቤታቸው ሆነው አገልግሎት ማግኘት ቢጀምሩ የሚል ጥሪ አቀርባለሁ። ሌሎቹን ተጨማሪ አገልግሎቶች ወደቴሌ-ሳይን ለመውሰድ፣ ወደ ወረቀት አልባ ለማድረግ እንደዚሁም ተገልጋይ ካለበት ሆኖ እንዲገለገል ጭምር ተጨማሪ ሥራዎችን እየሠራን ስለሆነ ከህብረተሰቡ የሚጠበቀው ለቴክኖሎጂ ቅርብ መሆን ነው። ከቴክኖሎጂ ጋር ቅርብ በመሆን ጊዜያችንን በመቀነስ፣ ወጪያችንን በመቀነስ ሁሉም የህብረተሰብ ክፍል ተገልጋይ እንዲሆን በዚህ አጋጣሚ መልዕክት ማስተላለፍ እፈልጋለሁ::

እንኳን ለ85ኛው የኢትዮጵያ አርበኞች ድል መታሰቢያ በዓል አደረሰዎ!የሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎት
05/05/2026

እንኳን ለ85ኛው የኢትዮጵያ አርበኞች ድል መታሰቢያ በዓል አደረሰዎ!

የሰነዶች ማረጋገጫና ምዝገባ አገልግሎት

Address

Addis Ababa
29935

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when Documents Authentication and Registration service posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Contact The Organization

Send a message to Documents Authentication and Registration service:

Share