09/09/2024
የአዲስ አበባ ከተማ የመንግስት ልማት ድርጅቶች አስተዳደር ባለስልጣር በልደታ ክ/ከተማ አዲስ ዓመትን ምክንያት በማድረግ ለ30 አባወራዎች G+1 የመኖሪያ ቤት ገንብቶ አስተላለፈ።
ባለስልጣኑ በስሩ ያሉ የልማት ድርጅቶችን በማስተባበር ለ30 አባወራዎች G+1 የሆኑ መኖሪያ ቤቶችን ሰርቶ በማጠናቀቅ ያስተላለፉት ማለትም ቄራዎች ድርጅት፣ ኤግዚብሽን ማዕከልና ገበያ ልማት፣ ከነማ ፋርማሲ እና የኮንስትራክሽን፣ ዲዛይን ፣ ግንባታና ማማከት ድርጅትን በማስተባበር አዲስ ህንፃ ማስገንባት የቁልፍ ርክክብ መርሀ ግብርም አካሂደዋል ።
የአዲስ አበባ የመንግስት የልማት ድርጀቶች አስተዳደር ባለስልጣን ፅ/ቤት ኃላፊ አቶ አባወይ ዮሐንስ ዛሬ ከጳጉሜ ቀናት 4ኛው ቀን የህብር ቀን ነው በዕለቱም አብሮነትና ትብብርን የምናከብርበት መልካም ተግባራትን የምናከናውንበት ኢትዮጵያዊነትን የምናጎላበት ዕለት ነው እንኳን አደረሳችሁ ብለዉ፣ይህ ቦታ ከወራት በፊት ለዕይታም ለመኖሪያም ምቹ አልነበረም ነገር ግን በከተማውና በክፍለ ከተማው አመራሮችና በጎ ፍቃደኛ የህብረተሰብ ክፍሎች ትብብር በፍጥነት ተሰርቶ በማጠናቀቅ ለቤት ባለዕድለኞች ማስረከብ ተችሏል ብለዋል።
ድርጅታችን የነዋሪዎችን ችግር ለማቃለል የሚሰራ ነው ያሉት አቶ አባወይ በዛሬው ዕለት ተመርቆ ለባዕድለኞች የተረከበው ቤት 40 ሚሊየን ብር የሚገመት ገንዘብ ወጪ በማድረግ ከመኖሪያነት ባለፈ ለንግድ፣ ለዕድር፣ ለካፍቴሪያና ለተለያዩ ዘርፎች የሚያገለግሉ ክፍሎችን አካቶ ተሰርቷል። በመሆኑም የአካባቢው ነዋሪዎች አዲሱን አመት በአዲስ ቤትና በአዲስ መንፈስ እንዲያከብሩ ከማድረግ ባሻገር ለስራ ዕድል ፈጠራውም ምቹ ሁኔታ ተፈጥሮላቸዋል ብለው በሌሎች የክፍለ ከተማው አካባቢዎችም ላይ የልማት ስራዎችን በጋራ መስራቱን አጠናክረን እንቀጥላለን ብለዋል።
የልደታ ክፍለ ከተማ ዋና ስራ አስፈጻሚ ወ/ሮ አበባ እሸቴ ለቤት እድለኞች እንኳን ደስ አላችሁና ለዘመን መለወጫ እንኳን አደረሳችሁ በማለት ካለፉት 6 አመታት ጀምሮ ለጳጉሜ ቀናት የተለያዩ ስያሜዎች በመስጠት ህብረተሰቡን ተጠቃሚ የሚያደርጉ ሰው ተኮርና የመሰረተ ልማት ስራዎች ሲሰራባቸው ቆይተዋል በዛሬው ዕለትም ጳጉሜ 4 የህብር ቀን በሚል በህብረት በአንድነትና በፍቅር ተሳስበን ብሎም ወገናችን ከችግር ተላቀው በአዲስ መንፈስ ወደ አዲሱ ዘመን እንዲሸጋገሩ የማድረግ ስራን እየሰራን እንገኛለን ብለዋል።
በመጨረሻም የከተማ፣ የክፍለ ከተማና የወረዳ አመራሮች የተገነቡ ቤቶችን የጎበኙ ሲሆን ለስራው መቀላጠፍ አስተዋጽኦ ላበረከቱ አካላትም እውቅና ተሰጥቷል።