01/06/2026
በሰርጋቸው እለት ድምጽ የሰጡ ሙሽሮች
ሙሽሮቹ በሆሳዕና ከተማ በሌሞ 01 የምርጫ ክልል በሄጦ ቀበሌ መስኪድ ሰፈር ምርጫ ጣቢያ 07 በመገኘት ድምጻቸውን ሰጥተዋል።
ሙሽራ ሰላሙ ዳንኤል እንደገለጸው የሰርጋቸው እለትና የምርጫው ቀን በመገጣጠሙ አጋጣሚውን ተጠቅመው ድምጽ ሰጥተዋል።
በሰርጋችን እለት በርካታ ፕሮግራሞች ቢኖሩብንም ምርጫው የእኛንም ሆነ የሀገራችንን የቀጣይ እጣ ፈንታ የሚወሰንበት በመሆኑ ድምጻችን ሰጥተናል ብሏል።
እለቱ የሰርጋችን ቀን ቢሆንም ኢትዮጵያን ማስቀደም ስላለብን ድምጻችንን ሰጥተናል ያለው ሙሽራው ለኢትዮጵያም ሆነ ለእኛ ይበጃል ያልነውን መርጠናል ሲል አክሏል።
የሚሰጡት ድምጽ የእነሱንም ሆነ የሀገሪቱን የቀጣይ እጣ ፈንታ የተሻለ ከማድረግ አኳያ ያለው ሚና ከፍተኛ መሆኑን በመረዳት የደስታ ፕሮግራማቸውን አቋርጠው ድምፃቸውን ለመስጠት በምርጫ ጣቢያው መገኘታቸውን ተናግሯል።
ሙሽሪት ብሩክ ገብሬ በበኩሏ የሰርግ ቀናቸው ከምርጫ ቀኑ ጋር በመገጣጠሙ በምርጫው ድምፅ በመስጠት አሻራቸውን ለማኖር ወስነው እንደነበር አስታውሳለች።
የድምፅ መስጫው ቀን ከሰርጋቸው ቀን ጋር አንድ በመሆኑ የተለየ ደስታ እንደፈጠረባት ተናግራለች።
በምርጫው በመሳተፍ ይሆነኛል ለምትለው ፓርቲ ድምጿን መስጠት በመቻሏ ከራሷ አልፎ የሀገሯን እጣ ፈንታ እንድትወስን እድል የፈጠረላት በመሆኑ ድርብ ደስታን እንደፈጠረላትም ገልፃለች።