22/05/2026
የዱባይ-ኢትዮጵያ የቢዝነስ ትስስር ፎረም በአዲስ አበባ በይፋ ተጀመረ
————-
በኢትዮጵያና በተባበሩት ዐረብ ኤምሬቶች (ዱባይ) መካከል ያለውን የንግድ፣ የኢንቨስትመንትና የቱሪዝም ትብብር ይበልጥ ለማጠናከር ያለመ የ“Dubai-Ethiopia Business Connect” መድረክ ዛሬ ግንቦት 14 ቀን 2018 ዓ.ም በአዲስ አበባ በይፋ ተካሂዷል።
ይህንን መድረክ ለመካፈል የዱባይ የንግድና ኢንዱስትሪ ምክር ቤት ፕሬዝዳንትና ዋና ሥራ አስፈጻሚ ክቡር መሐመድ አሊ ረሺድ ሉታ የመሩት የ36 አባላት የንግድ ልዑክ አዲስ አበባ የተገኘ ሲሆን በኢትዮጵያ በኩል ደግሞ ከ250 በላይ የንግድ ማኅበረሰብ አባላትና ከፍተኛ የመንግሥት ተቋማት ተወካዮች በፕሮግራሙ ላይ ታድመዋል።
በመድረኩ ላይ መልዕክት ያስተላለፉት በተባበሩት ዐረብ ኤምሬቶች የኢፌዲሪ ልዩ መልዕክተኛና ባለሙሉ ሥልጣን አምባሳደር ክቡር ዶ/ር ጀማል በከር በሁለቱ አገራት መካከል እየተጠናከረ የመጣው ስትራቴጂካዊ ግንኙነት ለግል ዘርፉ ሰፊ የገበያና የኢንቨስትመንት ዕድሎችን እየፈጠረ መሆኑን ገልጸው የኤምሬቶች ባለሀብቶች በኢትዮጵያ ምቹ በሆኑ የኢንቨስትመንት መስኮች ላይ እንዲሰማሩ ጥሪ አቅርበዋል።
የዱባይ ንግድ ምክር ቤት ፕሬዝዳንትና ዋና ሥራ አስፈጻሚ ክቡር መሐመድ አሊ ረሺድ ሉታ በበኩላቸው ኢትዮጵያ በምስራቅ አፍሪካ ያላትን ስትራቴጂካዊ የንግድ ተመራጭነት ጠቅሰው የዱባይ ኩባንያዎች አጋርነታቸውን ለማስፋትና አዳዲስ የንግድ ዕድሎችን ለመፍጠር ጽኑ ፍላጎት እንዳላቸው አስታውቀዋል።
በመድረኩ በኢትዮጵያ ኢንቨስትመንት ኮሚሽንና የሚመለከታቸው አካላት አማካኝነት በኢትዮጵያ ስላሉት ወቅታዊና ምቹ የኢንቨስትመንት ዕድሎች፣ ማበረታቻዎችና የሪፎርም ሥራዎች በተለይም በግብርና፣ በግብርና ማቀነባበሪያ፣ በማኑፋክቸሪንግ፣ በቱሪዝም፣ በሎጅስቲክስ እና በታዳሽ ኃይል ዘርፎች ዙሪያ ለዱባይ የንግድ ልዑክ ሰፊ ገለጻ ተደርጓል።
ዱባይ ቻምበርስ ከ300,000 በላይ አባላት ያሉት ሲሆን፣ በቀጠናው ካሉ ትልልቅ እና ተፅዕኖ ፈጣሪ የንግድ ድርጅቶች መካከል አንዱ ሲሆን ይህ የቢዝነስ ትስስር መድረክ በሁለቱ አገራት የግል ዘርፎች መካከል ቀጥተኛ ግንኙነትን (B2B) ለመፍጠርና የጋራ የንግድ ልውውጥን ወደ ላቀ ደረጃ ለማሸጋገር ትልቅ መሠረት የጣለ መሆኑ ተገልጿል።
Jemal Beker
Ethiopian News AgencyThe Ministry of Foreign Affairs of Ethiopia
Ethiopian Broadcasting Corporation