17/09/2026
እንኳን ደስ ያላችሁ !
በሰንበቴ ጤና አጠባበቅ ጣቢያየ OR ክፍል የቀዶ ህክምና አገልግሎት ተጀመረ!
በሰንበቴ ጤና አጠባበቅ ጣቢያ የቀዶ ህክምና አገልግሎት ዛሬ በይፋ መጀመሩ ለከተማችንና ለአካባቢው ህብረተሰብ ትልቅ የጤና አገልግሎት እመርታ ነው።
በተለይም ከወሊድ ጋር ተያይዘው የሚከሰቱ አስቸኳይ የጤና ችግሮች ሲያጋጥሙ እናቶች ለህክምና ወደ ሩቅ ጤና ተቋማት መጓዝ የሚያስከትለውን የጊዜ፣ የመጓጓዣና የወጪ እንግልት ለማስቀረት የአገልግሎቱ መጀመር ወሳኝ ሚና ይኖረዋል።
ይህም አስቸኳይ ህክምና የሚፈልጉ እናቶች በአካባቢያቸው ፈጣንና ተገቢ የህክምና ድጋፍ እንዲያገኙ በማድረግ ከመዘግየት ጋር ተያይዞ ሊከሰት የሚችለውን የጤና ጉዳትና ሞት ለመቀነስ የሚያግዝ ነው።
የአገልግሎቱ ጠቀሜታ በመጀመሪያው ቀንም ተጨባጭ ሆኗል። ሁለት እናቶች በቀዶ ጥገና ልጆቻቸውን በሰላም መገላገል ችለዋል። ይህም በአካባቢው የቀዶ ህክምና አገልግሎት መኖሩ ለእናቶችና ለሕፃናት ህይወት ጥበቃ ያለውን ትልቅ ፋይዳ ያሳያል።
የሰንበቴ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ኑረዲን አህመድ የዚህን አስፈላጊ አገልግሎት መጀመር በማስመልከት ለመላው የከተማዋ ነዋሪዎች፣ ለጤና ባለሙያዎችና ለጤና ተቋሙ አመራር የእንኳን ደስ አላችሁ መልእክት አስተላልፈዋል።
ከንቲባው የቀዶ ህክምና አገልግሎቱ መጀመር ከዚህ በፊት ህሙማንን ለሩቅ ጤና ተቋም ለመላክ የነበሩ እንግልቶችን በማስቀረት፣ የህክምና ጊዜን በማሳጠርና አስቸኳይ ህክምናን በቅርበት በማቅረብ የእናቶችንና የሕፃናትን ህይወት ለመጠበቅ የሚያግዝ ትልቅ ስኬት መሆኑን ገልጸዋል።