22/05/2026
"ውሳኔው ለጥቂቶች ሥልጣን ሲባል የትግራይን ሕዝብ ለከፋ ችግር የሚዳርግ ነው"
-ጀነራል ሳሞራ ዩኑስ የቀድሞ ኢታማዦር ሹም
+++++++++++++
፡ በትግራይ ክልል የቀድሞው ምክር ቤትንና የቀድሞ ሕወሓት የተወሰኑ አመራሮችን ወደ ሥልጣን የመመለስ ውሳኔ ሕዝቡን ለከፍተኛ ስጋትና ችግር እየዳረገው መሆኑን ጀነራል ሳሞራ ዩኑስ ተናገሩ።
ጀነራል ሳሞራ የትግራይ ክልልን ወቅታዊ ጉዳይ አስመልክተው ለአዲስ ዘመን ጋዜጣ እንደገለጹት፤ የተወሰኑ የቀድሞው ሕወሓት አመራሮች ለራሳቸው የሥልጣን ጥም ብቻ ሲሉ የሕዝብን የመምረጥና በመረጠው መሪ የመተዳደር መብት እያፈኑ ነው። የእነዚህ ቡድኖች ውሳኔ ጥቂቶችን ብቻ የሚወክል እንደሆነም ገልጸዋል።
በቅርቡ በትግራይ ክልል ሕዝብ ስም የተላለፈው ውሳኔ ከመቶ በማይበልጡ ሰዎች የተወሰነ መሆኑን የገለጹት ጀነራሉ፤ ይህም ውሳኔ “በጣም መጥፎ እና በሀገር ውስጥም ሆነ በውጭ የሚገኘውን ትግራዋይ ያስጨነቀና ስጋት ላይ የጣለ መሆኑን ጠቁመዋል።
ጀነራሉ፤ ውሳኔው የሚያሳየው የቀድሞው ሕወሓት ውስን አመራሮች የሚያሳስባቸው የትግራይ ሕዝብ ልማትና ሰላም ሳይሆን የግል ሥልጣናቸውና ጥቅማቸው መሆኑን ገልጸዋል።
ውሳኔው በተለይ ጊዜያዊ አስተዳደሩን ሲመሩት በነበሩት አቶ ጌታቸው ረዳ ላይ የተሸረበው ሴራ አሁንም በጀነራል ታደሰ ወረደ ላይ መቀጠሉን ያረጋገጠ እንደሆነ ጠቅሰው፤ ይህ ሕገ ወጥ አካሄድን ህጋዊ አስመስሎ የማቅረብ ጉዳይ እንደሆነም አመልክተዋል።
የቀድሞው ምክር ቤትንና የቀድሞ ሕወሓት ውስን አመራሮችን ወደ ሥልጣን የመመለስ ውሳኔ ፤ሥልጣን እንደገና ለመያዝና ለውጥን ለመቃወም የተዘየደ ስልት መሆኑን ጠቁመዋል።
በአሁኑ ጊዜ የሚታየው የፖለቲካ እንቅስቃሴ ዓላማው የፌዴራል መንግሥቱ የሚያካሂደውን ሀገራዊ ምርጫ ለማሰናከል የታለመ ሊሆን እንደሚችል ጠቅሰው፤ የትግራይ ሕዝብ ላለፉት ስምንት ዓመታት የመምረጥ መብቱ ታፍኖ መቆየቱን አስታውሰዋል።
“መንግሥትነታችንን መለስን ወይም ወደ ቀድሞ አቋማችን ተመልሰናል” የሚለው ውሳኔ በፌዴራል መንግሥቱም ሆነ በሕገ-መንግሥቱ ተቀባይነት የሌለውና አደገኛ አካሄድ መሆኑን ጀነራሉ አስገንዝበዋል።
ጀነራል ሳሞራ፤በትግራይ ክልል የሚገኙ ጀነራሎችና ከፍተኛ መኮንኖች በሥልጣን ላይ ለመቆየት የሚፈልጉት ፤ በጦርነቱ ወቅት ለደረሰው የሰው ሕይወት መጥፋት ተጠያቂነትን ስለሚፈሩ እንደሆነ ገልጸዋል። በአሁኑ ጊዜ ታጣቂዎቹ በተለያየ ውሳኔ ምክንያት መበተናቸውና ሕዝቡም አመራሩን እንደጠላው ተናግረዋል።
የፌዴራል መንግሥት ጉዳዩን በረጋ መንፈስና በብስለት እንዲፈታው አስገንዝበው፤የክልሉ ጀነራሎችና ኮሎኔሎች በትግራይ ክልል የደረሰው ችግር “ይበቃል” በማለት የታጠቁ ኃይሎች ወደ ተሐድሶ እንዲገቡና ፖለቲከኞቹም ሥልጣን እንዲለቁ ግፊት እንዲያደርጉ ጥሪ አቅርበዋል።
የተፈረመው የፕሪቶሪያ የሰላም ስምምነት ለሕዝቡ የሰላም እፎይታን ቢሰጥም፤ አሁን ላይ ያለው የስልጣን ሽኩቻ ሕዝቡን ወደ በለጠ ጭንቀት እየከተተው እንደሚገኝ ተናግረዋል።
የትግራይ ሕዝብ ከእዚህ በላይ እነዚህን የቀድሞው ሕወሓት ውስን አመራሮች መታገስ እንደሌለበትና አዲስ ኃይል እንዲመጣ ግፊት እንዲያደርግ ጥሪ አቅርበዋል።
በሔርሞን ፍቃዱ
#ትግራይ #ሀገራዊምርጫ