የቋራ ወረዳ ፍትህ ጽ/ቤት/Quara wereda justice office

የቋራ ወረዳ ፍትህ ጽ/ቤት/Quara wereda justice office ይህ ድህረ ገጽ የተለያዩ አዋጆች፣ደንቦች፣መመሪያዎች፣ውሳኔዎች፣የህግ ማብራሪያዎች፣ ለህብረተሰቡ ለማሳወቅ የተከፈተ ነው።

የቋ/ወ/ፍትህ/ጽ/ቤት በቀን  05/06/2018 ዓ/ም ከቋ/ወ/ፖሊስ ጽ/ቤት ና ከቋ/ወ/ ፍርድ ቤት ጋር ዉይይት አካሄደ:-በውይይቱም*ስለአገልግሎት አሰጣጥ፣*ስለእስረኞች የዋስትና ፍቃድ አሰጣ...
12/02/2026

የቋ/ወ/ፍትህ/ጽ/ቤት በቀን 05/06/2018 ዓ/ም ከቋ/ወ/ፖሊስ ጽ/ቤት ና ከቋ/ወ/ ፍርድ ቤት ጋር ዉይይት አካሄደ:-በውይይቱም
*ስለአገልግሎት አሰጣጥ፣
*ስለእስረኞች የዋስትና ፍቃድ አሰጣጥ፣
*ስለአጋር የፍትህ ተቋማት ያሉ ችግሮችን መለየት እና ለችግሮች የመፍትሔ አቅጣጫ ማስቀመጥ በሚሉ ሀሳቦች ዉይይት አካሂደዋል።

19/12/2025

👉በሊዝ የተያዘ መሬት ላይ ግንባታ መጀመሪያና ማጠናቀቂያ የጊዜ ገደብ

✂️ሀ) ግንባታ ማስጀመሪያ

አንድ ግለሰብ/ድርጅት በከተማ ቦታ ላይ በሊዝ የተረከበው ቦታ ላይ የሊዝ ውል ከፈረመበት ቀን ጀምሮ ለቦታው በተቀመጠው ደረጃ መረሰት ግንባታ እንዳለበት የሚደነግግ የጊዜ ጣሪያ ተቀምጧል።

በሊዝ ቦታ ላይ የግንባታ መጀመሪያ የጊዜ ጣሪያ፦ ለአንሰተኛ ደረጃ ግንባታዎች = 6 ወር፣ ለመካከለኛ ደረጃ ግንባታዎች = 9 ወር፣ እና ለከፍተኛ ደረጃ ግንባታዎች = 18 ወር ነው።

ሆኖም ግን እንደ አካባቢው ነባራዊ ሁኔታ ወይም በተለያዩ ምክንያቶች በተጠቀሱት የጊዜ ገደቦች ግንባታ ሳይጀመር ቢቀር ለአንድ ዙር ብቻ የሚፈቀድ ለአንሰተኛ ደረጃ ግንባታዎች 6 ወር፣ ለመካከለኛ ደረጃ ግንባታዎች 9 ወር፣ ለከፍተኛ ደረጃ ግንባታዎች አንድ ዓመት ተጨማሪ የግንባታ ማስጀመሪያ ጊዜ በግንባታ ፍቃድ ሰጪው አካል ከማስጠንቀቂያ ደብዳቤ ጋር ሊሰጣቸው ይችላል።

✂️ለ) ግንባታ ማጠናቀቂያ

በሊዝ ቦታ ላይ ግንባታ የማጠናቀቂያ የጊዜ ገደብ፦ ለአንሰተኛ ደረጃ ግንባታዎች 24 ወራት፣ ለመካከለኛ ደረጃ ግንባታዎች 36 ወራት፣ እና ለከፍተኛ ደረጃ ግንባታዎች 48 ወራት ነው።

ነገር ግን የአካባቢው የግንባታ ፍቃድ ሰጪ አካል ካመነበት የግንባታውን ውስብስብነት እያየ ሊያራዝምለት ይችላል።

ሆኖም ግን ለግንባታ ማጠናቀቂያ የሚሰጠው ጊዜ በማንኛውም ምክንያት (ሁኔታ) ቢሆን ለአንሰተኛ ደረጃ ግንባታዎች 2 ዓመት 6 ወር፣ ለመካከለኛ ደረጃ ግንባታዎች 4 ዓምት፣ እና ለከፍተኛ ደረጃ ግንባታዎች ከአምስት ዓመት መብለጥ የለበትም።

17/12/2025
08/12/2025

የስጦታ ውሉ በተዘዋዋሪ የመሬት ሽያጭ ውጤት ያለው ከሆነ ተቀባይነት የለውም

ተጠሪዎች ከመሠረቱት ሕገ ወጥ በሆነ ስጦታ ውል አማካኝነት መብት አቋቁሜያለሁ በሚል የአመልካቾችን አውራሽ በሐይል እና በጉልበት የያዙት ይዞታ ለቀው እንድያስረክቡ በሚል ያቀረቡት የዳኝነት ጥያቄ የውልን መፍረስ ዳኝነት ጥያቄ የሚጠበቅ ሳይሆን ፍ/ቤቱ በራሱ በሕገወጥ መንገድ የተገኘ የመሬት ይዞታ ጋር ተያይዞ የመጣ ክርክር በመሆኑ የስጦታ ውሉ በተዘዋዋሪ የመሬት ሽያጭ ውጤት በሚያስከትል መልኩ ስምምነት የተደረገበት በመሆኑ በሕግ ዘንድ ተቀባይነት የለውም በማለት ክርክሩን ውድቅ ማድረግ ሲገባው የስጦታ ውሉን እውቅና በመስጠት እና ተጠሪዎች በዚሕ ሕጋዊ ባልሆነ የውል ግንኙነት አማካኝነት በይዞታው ላይ ለረጂም ጊዜ ግብር መገበራቼው የይዞታው ባለመብት ያደርጋቸዋል በማለት አመልካቾች ክርክር ያስነሳውን ይዞታ ለቀው ለተጠሪዎች ያስረክቡ በሚል የተሰጠው ውሳኔ ከሕግ አተገባበር እና ማስረጃ ምዘና አንጻር መሠረታዊ የሕግ ስሕተት ስለመሆኑ በሰበር መ/ቁ=257723 ቀን ታሕሳስ 25/2017 ተወስኗል።

ለዕጩ ዓቃብያነ ህግ የወጣ የስራ ቅጥር የውድድር ማስታወቂያ
07/12/2025

ለዕጩ ዓቃብያነ ህግ የወጣ የስራ ቅጥር የውድድር ማስታወቂያ

29/07/2023
የአምራች ና የአስመራች ውል/Contract farming/ ለመያዝ መሟላት ያለባቸው ሰነዶች
10/07/2023

የአምራች ና የአስመራች ውል/Contract farming/ ለመያዝ መሟላት ያለባቸው ሰነዶች

02/07/2023

የንግድ ሥራ ፈቃድ አጠቃምን አስመልክቶ ሕጉ ምን ይላል?

@ትርጓሜ፤
የንግድ ሥራ ፈቃድ አንድን በሕግ የተፈቀደ የንግድ ተግባር/ሥራ ለማከናወን የሚያስችልና አግባብነት ካለው ፈቃድ ሰጪ አካል የሚሰጥ ፈቃድ ነው፡፡ በመደበኛነት የንግድ ፈቃድን የሚሰጡ አካላት ሁለት ሲሆኑ እነዚህም በፌደራል መንግስት ደረጃ የንግድ ሚኒስቴር ሲሆን በክልል ደረጃ ደግሞ የንግድ ቢሮ ናቸው፡፡

ከነዚህ ሁለት አካላት በተጨማሪ የንግድ ፈቃድን የሚሰጡ ሌሎች አግባብነት ያላቸው የአስተዳደር አካላትም አሉ፡፡ እነዚህ አካላት ከሥራው ልዩ ባህሪ አንጻር ፈቃዱን ለመስጠት የሚያስችሉ ልዩ የብቃት ማረጋገጫዎችን የሚጠይቁ ከመሆናቸውም ባሻገር የንግድ ሥራውን ለመምራትና ለመቆጣጠር ራሱን የቻለ ሙያዊ ችሎታን ስለሚጠይቁ ነው፡፡ ለምሳሌ፡- የማዕድን ፍለጋና ልማት ሥራዎችን በመለከተ ፈቃድ የሚሰጠው የማዕድን ሚኒስቴር/አግባብነት ያለው የክልል አካል ነው፤ የሚዲያ ሥራዎችን በተመለከተ የንግድ ሥራ ፈቃዱን የብሮድካስ ባለስልጣን ይሰጣል፤ የባንክ፣ የመድን እና የማይክሮ ፋይናንስ ንግድ ሥራዎችን ደግሞ ብሄራዊ ባንክ ፈቃድ የሚሰጥ ይሆናል፡፡ ሌሎች አካላትም አሉ፡፡

- ይዘት፡-
የንግድ ሥራ ፈቃድ የተለያዩ መረጃዎችን የያዘ ሠነድ ነው፡፡ የንግድ ሥራ ፈቃድ በይዘት ደረጃ የነጋዴውን/የድርጅቱን ስም፣ የሚሰራውን ሥራ፣ አድራሻውን፣ የግብር ከፋይ መለያ ቁጥር (TIN)፣ የሰጨውን አካል ማንነት፣ የተሰጠበትን ጊዜና የመሳሰሉትን ጉዳዮች የሚይዝ ነው፡፡

- መብትና ግዴታ፤
የንግድ ሥራ ፈቃድ አጠቃቀምን አስመልክቶ የንግድ ምዝገባና ፈቃድ አዋጅ ቁጥር 980/2008 የተለያዩ ድንጋጌዎችን አስቀምጧል፡፡ የንግድ ፈቃድ ያለው ሰው በሕግ የተሰጡት መብቶች ያሉትን ያህል ግዴታዎችም አሉት፡፡ ከእነዚህ ግዴታዎች ውስጥ አንዱና ዋነኛው የንግድ ሥራ ፈቃድ በስሙ የተሰጠው ሰው/ድርጅት ፈቃዱን ለተሰጠው የንግድ ሥራ መስሪያ ብቻ እንዲውል የማድረግ ግዴታ አለበት፤ በሌላ አነጋገር ፈቃዱ ለተሰጠው ነጋዴ እና ለመነገድ ብቻ የሚያገለግል ግላዊ /personal document/ ሰነድ ነው፡፡ ስለሆነም የንግድ ሥራ ፈቃድ ከተሰጠበት ዓላማ ውጭ መገልገል፤ ለምሳሌ፡- ፈቃዱን ለሌላ ሰው ማከራየት፣ ማዋስ፣ በስጦታ፣ በመያዣነት ወይም በሌላ ማናቸውም አኳኋን ፈቃዱን አሳልፎ መስጠት አይፈቀድለትም፡፡

2. የንግድ ሥራ ፈቃድን በማከራየት ወይም በሌላ አኳኋን ከተሰጠበት ዓላማ ውጭ ሲገለገል የተገኘ ነጋዴ የሕግ ተጠያቂነቱ ምንድን ነው?

የንግድ ምዝገባና ፈቃድ አዋጅ ቁጥር 980/2008 የንግድ ሥራ ፈቃዱን ያከራየ፣ ያዋሰ ወይም በመያዣነት ሌላ ሰው እንዲገለገልበት አሳልፎ የሰጠ መሆኑ ሲረጋገጥ አስተዳደደራዊ እና የወንጀል ተጠያቂነቶችን ያስከትልበታል፡፡ አስተዳደራዊ ተጠያቂነቱ ንግድን በሚመራውና በሚመራው የንግድ ሚኒስቴር ወይም የንግድ ቢሮ ወይም በሌላ ፈቃድ ሰጪ አካል በነጋዴው ላይ የሚተላለፍ እርምጃ ሲሆን በዚህም መሰረት የመጀመሪያው የንግድ ሥራ ፈቃድ እገዳ (አንቀጽ (29)(1) (ሠ) ይመልከቱ) ሲሆን ሁለተኛው ደግሞ የንግድ ሥራ ፈቃድ ስረዛ ነው (አንቀጽ (30(1)(ሐ) ይመልከቱ)፡፡

ሌላኛው ተጠያቂነት ደግሞ የወንጀል ኃላፊነት ነው፡፡ ከላይ የተጠቀሰውን ተግባር የፈጸመ ነጋዴ ከብር 50,000 እስከ ብር 100,000 በሚደርስ የገንዘብ መቀጫ እና ከ5 ዓመት እስከ 10 ዓመት በሚደርስ ጽኑ እስራት ይቀጣል (አንቀጽ 49(4)ን ይመልከቱ)፡፡ ነጋዴው የውጭ አገር ዜጋ ሲሆን ደግሞ ቅጣቱ ከፍ ብሎ ከብር 200,000 እስከ ብር 300,000 በሚደርስ የገንዘብ መቀጫና ከ7 ዓመት - 15 ዓመት በሚደርስ ጽኑ እስራት ይቀጣል፡፡

3. የንግድ ፈቃድን ተከራይቶ የሚሰራ ሰው ያለበት የሕግ ተጠያቂነት ምንድን ነው?

ቀደም ሲል እንደገለጽነው ማንኛውም ሰው የንግድ ሥራን ለመስራት አስቀድሞ ሕጋዊ የሆነ የጸና የንግድ ሥራ ፈቃድ መያዝ ይኖርበታል፡፡ አንድ የንግድ ሥራ ፈቃድ ለአንድ ነጋዴ ብቻ የሚያገለግል ግላዊ ፈቃድ ነው፡፡ ስለሆነም ግለሰቡ የሌላ ሰውን የንግድ ሥራ ፈቃድ በኪራይ በመያዝ የንግድ ሥራ እያከናወነ ቢገኝ ያለንግድ ፈቃድ የንግድ ሥራ እያከናወነ እንዳለ ይቆጠራል ማለት ነው፡፡ ይህም ደግሞ አስተዳደራዊና የወንጀል ተጠያቂነቶችን ያስከትልበታል፡፡ የንግድ ምዝገባና ፈቃድ አዋጁ አንቀጽ 49(2) የጸና የንግድ ሥራ ፈቃድ ሳይኖረው እየነገደ የተገኘ ሰው የንግድ ሥራ ሲካሄድባቸው የነበሩ የንግድ ዕቃዎች እና የአገልግሎት መስጫና የማምረቻ መሳሪያዎች መወረሳቸው እንደተጠበቁ ሆነው ከብር 150,000 እስከ ብር 300,000 በሚደርስ መቀጫ እና ከ 7 ዓመት እስከ 15 ዓመት በሚደርስ ጽኑ እስራት የሚቀጣ ይሆናል ማለት ነው፡፡

GMS law office !

የዳኝነት ሳይከፈል በነፃ ስለሚቀርብ ክስ   ማንኛውም የፍትሐብሔር ክስ ሲከፈት በፍርድ ቤት ለሚሰጠው የዳኝነት አገልግሎት የዳኝነት እንዲከፈል ይጠበቃል፡፡ ክስ ለማቅረብ የፈለገ ወገን ለሚያገ...
08/06/2023

የዳኝነት ሳይከፈል በነፃ ስለሚቀርብ ክስ

ማንኛውም የፍትሐብሔር ክስ ሲከፈት በፍርድ ቤት ለሚሰጠው የዳኝነት አገልግሎት የዳኝነት እንዲከፈል ይጠበቃል፡፡ ክስ ለማቅረብ የፈለገ ወገን ለሚያገኘው የዳኝነት አገልግሎት መክፈል የሚገባውን የዳኝነት ገንዘብ ለመክፈል የሚያስችል የገንዘብ አቅም የሌለው ከሆነ ለግዜው የዳኝነት መክፈል ባለመቻሉ ብቻ መብቶቹን እንዳያጣ የፍትሐብሔር ሥነ ሥርአት ህጉ መፍትሄ አስቀምጧል፡፡ በዚህ አጭር ፅሁፍ የዳኝነት ሳይከፈል በነፃ ስለሚቀርብ ክስ ምንነት እና ስለሚቀርብበት ሥነ ሥርዓት እንመለከታለን፡፡

የዳኝነት ሳይከፈል በነፃ የሚቀርብ ክስ ምንነት

በ1958 ዓ.ም በወጣው የፍትሐብሔር ሥነ ሥርአት ህግ ቁጥር 467 መሰረት የዳኝነት ሳይከፈል በነፃ የሚቀርብ ክስ ማለት ገንዘብ የሌለው እና ገንዘብ ለማግኘት የማይችል ማንኛውም ደሀ ሰው የዳኝነት ሳይከፍል በነፃ ፋይል ክፍቶ ክስ የሚያቀርብበት ሂደት ነው፡፡

የዳኝነት ሳይከፈል በነፃ የሚቀርብ ክስ ሥነ-ሥርዓት

በፍትሐብሔር ሥነ ሥርዓት ህግ ቁጥር 467 መሰረት ዳኝነት መክፈል የማይችል ደሀ ሰው የዳኝነት ገንዘብ በሙሉ ወይም በከፊል ሳይከፍል የነፃ ፋይል ማስከፈት የሚችለው ከክሱ አቤቱታ ጋር የነፃ ዳኝነት ማመልከቻ በቃለ መሀላ አስግፎ ዋናውን ጉዳይ ለሚያየው ፍርድ ቤት ሲያቀርብ ነው (ቁ.468)፡፡ ፍርድ ቤቱም ማመልከቻውን ተመልክቶ ስለአመልካች የሀብት ሁኔታ እና ስለማመልከቻው ተገቢነት አስፈላጊ ማስረጃ ለማግኘት አመልካችን ወይም ወኪሉን አስቀርቦ ሊጠይቀው ይችላል፡፡

ፍርድ ቤቱ የቀረበው ማመልከቻ ሲመረምር የሚነቀፍበት ምክንያት ካላገኘ በፍትሐብሔር ሥነ ሥርዓት ህግ ቁጥር 471 መሰረት አመልካች ድሀ ስለመሆኑ እንዲያስረዳ እና በአንፃሩም አመልካቹ ሀብት አለው የሚሉ ሰዎች እንዳሉ እንዲያስረዱ ቀጠሮ በመስጠት ከቀጠሮ አስር ቀን በፊት ለባለጋራው ማስታወቂ እንዲደርሰው ማድረግ ይጠበቅበታል፡፡ ማስረጃው ተሰምቶ ከተመረመረ በኋላ ፍርድ ቤቱ ማመልከቻውን ሊቀበል ወይም ውድቅ ሊያደርግ ይችላል፡፡ ማመልከቻው ተቀባይነት ካገኘ አመልካቹ ዳኝነት ሳይከፍል ያቀረበው ክስ ዳኝነት እንደተከፈለበት እንደማንኛውም ክስ ተቆጥሮ በመደበኛ ሥነ ሥርአት ይመራል፡፡

ይህም ውሳኔ በነፃ ዳኝነት የቀረበው ክስ ቀጥሎ የመጨረሻ ውሳኔ እስኪያገኝ ድረስ የሚያገለግል እና ማስረጃነቱ የሚቀጥል ሲሆን ይህ ማስረጃ ግን ለሌሎች ክርክሮች እንደ ማስረጃ ሊሆን አይችልም፡፡ በይግባኝ ደረጃ የሚሄድ ክርክር አመልካች ይግባኝ ባይ ከሆነ በነፃ ይግባኝ መዝገብ እንደ አዲስ ይከፈትልኝ እስካላለ ድረስ በነፃ እንዲከራከር በስር ፍርድ ቤት የተሰጠው የድህነት ማስረጃ አያገለግለውም፡፡ ነገር ግን በይግባኝ ክርክሩ መልስ ሰጪ ከሆነ የድህነት ማስረጃው ያገለግለዋል (ቁ.474)፡፡

በሌላ በኩል ዳኝነት ሳይከፈል በነፃ እንዲታይ የሚቀርብ ማመልከቻ ተቀባይነት ላያገኝ ይችላል፡፡ በፍትሐብሔር ሥነ ሥርዓት ህግ ቁጥር 470 መሰረት ማመልከቻው ተቀባይነትን ላያገኝ የሚችለው፡-

 አመልካቹ ድሀ አለመሆኑ ከተረጋገጠ፣
 በነፃ ለመክሰስ ያቀረበው ነገር የማያስከስስ የሆነ እንደሆነ፣
 ክስ ከማቅረቡ ከሁለት ወር በፊት የነበረውን ንብረት ለሌላ ሰው አስተላልፎ እንደሆነ ወይም በማጭበርበር መንገድ ንብረቱን አዛውሮ ከሆነ ወይም ዳኝነት ከመክፈል ለመዳን ዘዴ ፈጥሮ ከሆነ፣
 ክርክር በሚያቀርብበት ንብረት ወይም መብት ውስጥ ሌላ ሶስተኛ ሰው እንዲጠቀም ወይም ማናቸውንም መብት እንዲያገኝ ተዋውሎ ወይም ተስማምቶ እንደሆነ ነው፡፡

የዳኝነት ሳይከፍል ልከራከር የሚለው ማመልከቻ ውድቅ ከተደረገ በዚሁ ጉዳይ ድጋሚ መቅረብ የማይችል ሲሆን ክስ ማቅረብ የሚችለው የዳኝነት ክፍያ እንዲሁም የነፃ ዳኝነት እንዲፈቀድለት ባቀረበ ጊዜ ባለጋራው ለመቃወም ያወጣውን ወጪና ኪሳራ ከፍሎ እንደሆነ ከፍሐብሔር ሥነ ሥርዓት ህግ ቁጥር 477 መረዳት ይቻላል፡፡

በነፃ ለመከራከር የተፈቀደለት ሰው በነፃ የመከራከር መብቱን ሊያጣ የሚችልባቸው ሁኔታዎች
በፍሐብሔር ሥነ ሥርዓት ህግ ቁጥር 475 መሰረት የዳኝነት ሳይከፈል በነፃ መከራከር ማስረጃ ዋጋ ሊያጣ የሚችል ሲሆን ይኸውም

 ክርክሩ እንዲሰማ በተቀጠረው ቀነ ቀጠሮ የዳኝነት ሳይከፈል በነፃ ልከራከር ባይ ሳይቀርብ የቀረ እንደሆነ ወይም የማወክ፣ የማስቸገርና የተንኮለኛነት ጠባይ ያሳየ እንደሆነ፣
 ክርክሩ በሚቀጥልበት ጊዜ ሀብት ያለው መሆኑ የተገለፀበት እንደሆነና በነጻ ዳኝነት መጠቀም ወይም በዚህ መቀጠል የማይገባው መሆኑን ፍርድ ቤቱ የተረዳ እንደሆነ፤
 ለክርክሩ መነሻ በሆነው ሀብት ላይ ሌላ ሶስተኛ ወገን ጥቅም እንዲያገኝ ስምምነት አድርጎ የተገኘ እንደሆነ ነው፡፡

ሀብት ያለው መሆኑ ተገልፆበት ወይም ለክርክሩ መነሻ በሆነው ሀብት ላይ ሌላ ሶስተኛ ወገን ጥቅም እንዲያገኝ ስምምነት አድርጎ በመገኘቱ በነፃ መከራከር መብቱ የተሰረዘበት ሰው ተገቢውን የዳኝነትና ማናቸውንም ለፍርድ ቤት የሚከፈለውን ገንዘብ እንዲከፍል ይታዘዛል፡፡

በነፃ እንዲከራከር የተፈቀደለት ድሀ በክርክሩ የመርታት ወይም ሀብት የማግኘት ውጤት
በነፃ እንዲከራከር የተፈቀደለት ሰው የዳኝነት ሳይከፍል የሚከራከርበትን ጉዳይ ራሱ በፍርድ አፈፃፀም የረታ እንደሆነ ፍርድ አስፈፃሚው በፍሐብሔር ሥነ ሥርዓት ህግ ቁጥር 476 መሰረት ለመንግስት የሚገባውን የዳኝነት ገንዘብና ማናቸውንም ወጪ ከረታው ሀብት ላይ ተቀናሽ በማድረግ ገቢ ካደረገ በኋላ ቀሪው ሀብት ረቺው እንደ ፍርዱ እንዲረከብ ማድረግ እንዳለበት ተደንግጎአል፡፡ ሌሎች በነፃ ለመዳኘት የሚቀርቡ ማመልከቻዎችና ይህንን ለመመርመር የሚያስፈልጉ ማናቸውም ወጭዎች ሁሉ ለዳኝነት ከሚከፈል ገንዘብ ጋር የሚታሰቡ እንደሆኑ ከፍሐብሔር ሥነ ሥርአት ህግ ቁጥር 479 መረዳት ይቻላል፡፡

በተጨማሪም የዳኝነት ሳይከፍል የሚከራከር ወገን ማስረጃው በተሰጠው በአስር አመት ግዜ ውስጥ ወይም ክርክሩ በሚቀጥልበት ጊዜ ሀብት ካገኘ ይህንኑ አስታውቆ ዳኝነቱን መክፈል እንዳለበት በፍሐብሔር ሥነ ሥርአት ህግ ቁጥር 478 ስር ተደንግጎ ይገኛል፡፡ ገንዘብ አግኝቶ እያለ ይህንን የማያስታወቅ ወይም የመክፈል ግዴታውን ባይወጣ በአታላይነት ወንጀል እንደሚጠየቅ በድንጋጌው ተመልክቷል፡፡

ዳኝነት ሳይከፈልበት በነፃ የሚቀርብ ክስ የዳኝነት ለመክፈል አቅም ያጡ ሰዎች ገንዘብ በማጣት መብቶቻቸውን እንዳያጡ ለማድረግ በህጉ የተቀመጠ መፍትሄ ሲሆን በዚሁ መልኩ የተከራከረ ሰው ሀብት ሲያገኝ በአግባቡ አስታውቆ የዳኝነት መክፈል ይጠበቅበታል፡፡ ስለሆነም ገንዘብ ሲያገኙ መክፍል እንደተጠበቀ ሆኖ የዳኝነት ለመክፈል አቅም የሌላቸው የህብረተሰብ ክፍሎች ገንዘብ ማጣታቸው ዳኝነት እንዳያገኙ እንደማይከለክላቸው አውቀው ተገቢውን ማስረጃ በማቅረብ በህጉ በተቀመጠው መልኩ መስተናገድ ይችላሉ፡፡

በፍትህ ሚኒስቴር የንቃተ ህግ ትምህርት እና ስልጠና ዳይሬክቶሬት የተዘጋጀ

ለምን እራቴን /ምግብ አልሰራሽም በማለት የ15 ዓመት እድሜ የሆናትን ህፃን  ልጁን ጭካኔ በተሞላበት ሁኔታ ደብድቦ የገደለው ተከሳሸ በ18 ዓመት ፅኑ እስራት ቅጣት ተቀጣ ፤~~~~~~~~~~~...
22/03/2023

ለምን እራቴን /ምግብ አልሰራሽም በማለት የ15 ዓመት እድሜ የሆናትን ህፃን ልጁን ጭካኔ በተሞላበት ሁኔታ ደብድቦ የገደለው ተከሳሸ በ18 ዓመት ፅኑ እስራት ቅጣት ተቀጣ ፤
~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~

ተከሳሸ አለፈ አዲሱ ገብሬ የተባለ ተከሳሸ ነዋሪነቱ ቋራ ወረዳ ወርቂና ቀበሌ ሲሆን ነሐሴ 12 ቀን 2014 ዓም በግምት ከምሽቱ 3:00 ሲሆን ቋራ ወረዳ ወርቂና ቀበሌ ወንበልጌ ተብሎ ከሚጠራው ልዩ ቦታ ከመኖሪያ ቤቱ ውስጥ የ15 ዓመት እድሜ የሞላትን ልጁን ህፃን #ሳልጠይቅሸ #አለፈን ለምን እራቴን አዘጋጅተሸ አልጠየቅሽኝም በሚል ምክንያት እጇን እና እግሯን በሰንሰለት በማሰር በዱላ እና በሲባጎ በተደጋጋሚ ደብድቦ የገደላት መሆኑን በማስረጃ በማረጋገጥ የቋራ ወረዳ ፖሊስ ፅ/ቤት ምርመራ አጣርቶ ለምዕራብ ጎንደር ዞን ዐቃቤ ህግ መምሪያ መዝገቡን ልኳል።

የዞን ዐቃቤ ህግም የምርመራ መዝገቡ እንደደረሰው መዝገቡን በመመርመር ተከሳሹ የገዛ ልጁን ለምን ምግብ አላዘጋጀሽም በሚል ምክንያት በአሰቃቂ ሁኔታ ደብድቦ የገደላት በመሆኑ የኢፌድሪ የወንጀል ህግ አንቀፅ 539 (1-ሀ) በመጥቀሰ በከባድ የሰው ግድያ ወንጀል ክሰ መስርቶ ተከራክሯል።

ተከሳሹም ወንጀሉን አልፈፀምኩም በማለት ክዶ የተከራከረ ቢሆንም ዐቃቤ ህግ ምስክሮችን አስቀርቦ ያሰማ ሲሆን ፍ/ቤቱም ዐቃቤ ህግ እንደክሱ አመሰራረት ያስረዳ በመሆኑ ተከሳሹ የዐቃቤ ህግን ክስ እንዲከላከል ብይን ሰጥቷል።

ተከሳሹም የመከላከያ ምስክር የለኝም በማለቱ የምዕራብ ጎንደር ዞን ከፍተኛ ፍ/ቤትም የጥፋተኝነት ፍርድ የሰጠ ሲሆን የዐቃቤ ህግንና የተከሳሹን የቅጣት አስተያየት ካዳመጠ በሗላ ዛሬ በቀን 12/07/2015 ዓም በዋለው ችሎት ተከሳሹንና መሰል የወንጀል ድርጊት የሚፈፅሙ ግለሰቦችን ያርማል ፣ ያስተምራል ያለውን #የ18 ዓመት ፅኑ እስራት ቅጣት ወስኗል።

ከወንጀል ታሪኩ መረዳት እንደሚቻለው ወላጆች ለአቅመ አዳም ያልደረሱ ልጆቻቸውን መንከባከብ ሲገባቸው ከአቅማቸው በላይ የሆነ ስራ በማሰራት ለብዙ በደል እየዳረጉ መሆኑ ነው። ይህ ድርጊት ደግሞ ህፃናትን ለሰባዊ መብት ጥሰት የሚዳርግ በመሆኑ ወላጆች ህፃናትን መንከባከብ ፣ ማስተማር ፣ የሚገባቸው መሆኑን እንገልፃለን
መረጃው የምዕራብ ጎንደር ዞን ፍትህ መምሪያ ነው።

12/07/2015 ዓም
ገንዳ ውሃ

የመንግስት አወቃቀር እና የስልጣን ክፍፍል በኢ.ፌ.ዲ.ሪ. ህገ-መንግስትየኢ.ፌ.ዲ.ሪ ህገ-መንግስት በውስጡ ካካተታቸው ጉዳዮች መካከል የመንግስት አወቃቀር እና ስርአተ መንግስትን የተመለከተው...
22/03/2023

የመንግስት አወቃቀር እና የስልጣን ክፍፍል በኢ.ፌ.ዲ.ሪ. ህገ-መንግስት

የኢ.ፌ.ዲ.ሪ ህገ-መንግስት በውስጡ ካካተታቸው ጉዳዮች መካከል የመንግስት አወቃቀር እና ስርአተ መንግስትን የተመለከተው አንዱ ነው፡፡ የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ ስርዓተ መንግስት ፓርላሜንታዊ እንደሆነ እና የመንግስት አወቃቀሩ ፌዴራላዊ እንደሆነ ይደነግጋል፡፡ በተጨማሪም የኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዲሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ በፌዴራል መንግስት እና በክልሎች የተዋቀረ ሲሆን የፈዴራል መንግስት እና ክልሎች የሚኖራቸውን የስልጣን ክፍፍል በዝርዝር አካቶ ይገኛል፡፡ በዚህ አጭር የንቃተ-ህግ ፅሁፍ በህገ-መንግስቱ የፌዴራል እና የክልል መንግስታትን የስልጣን አወቃቀር እና ክፍፍል እንመለከታለን፡፡

• የመንግስት የስልጣን አካላት አወቃቀር

የኢትዮጵያ ፌደራላዊ ዴሞክሲያዊ ሪፐብሊክ በፌደራል መንግስትና በክልሎች የተዋቀረ ሆኖ የፌደራሉ መንግስትና ክልሎች የየራሳቸው ህግ አውጪ፣ ሕግ አስፈፃሚና የዳኝነት ስልጣን እንዳላቸው በአንቀፅ 50(1) እና (2) ተደነግጓል፡፡ የፌደራሉ መንግስት ከፍተኛ የስልጣን አካል የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ሲሆን ተጠሪነቱም ለሀገሪቱ ህዝብ ነው፡፡ በተመሳሳይ የክልል ከፍተኛ የስልጣን አካል የክልሉ ምክር ቤት ሆኖ ተጠሪነቱም ለወከለው ክልል ሕዝብ ነው፡፡ የክልል ምክር ቤት በክልል ሥልጣን ስር በሆኑ ጉዳዮች የክልል የሕግ አውጪ አካል ሆኖ የኢ.ፌ.ዲ.ሪ. ህገ መንግስትን መሰረት በማድረግ በክልል ደረጃ ህግ ማውጣት ስልጣን እንዳለው በህገ መንግስቱ አንቀፅ 50(5) ስር ተደንግጓል፡፡

የፌዴራል መንግስት ሥልጣንና ተግባር

የፌዴራሉ መንግስት ሥልጣንና ተግባራት በህገ-መንግስቱ አንቀፅ 51 ስር የተዘረዘሩ ሲሆን እነሱም
 ህገ መንግስቱን መጠበቅ፣ መከላከል
 የአገሪቱን አጠቃለይ የኢኮኖሚና የልማት ፖሊሲ፣ ስትራቴጂና ዕቅድ ማውጣት፣ ማስፈፀም።
 የጤና፣ የትምህርት፣ የባህልና ታሪካዊ ቅርስ የሳይንስና ቴክኖሎጂ ሀገር አቀፍ መመዘኛዎችና መሰረታዊ የፖሊሲ መለኪያዊችን መውጣት፣ ማስፈፀም
 የሀገሪቱን የፋይናንስ፣ የገንዘብ የውጪ ኢንቨስትመነት ፖሊሲዎችና ስትራቴጂዎችን ማውጣት፣ ማስፈፀም
 የመሬት፣ የተፈጥሮ ሀብትና የታሪክ ቅርሶች አጠቃቀምና ጥበቃን በተመለከተ ሕግ ማውጣት
 የሀገርና የህዝብ የመከላከያና የደህንነት እንዲሁም የፌደራል መንግስት የፖሊሲ ሀይል ማደራጀት፣ መምራት
 ብሔራዊ ባንክን ማስተዳደር፣ ገንዘብ ማተም፣ መበደር፣ የውጪ ምንዛሪና የገንዘብ ልውውጥን መቆጣጠር፣ ክልሎች ከውስጥ ምንጮች ስለሚበደሩበት ሁኔታ ሕግና መመሪያን ማውጣት
 የውጪ ግንኙነት ፖሊሲን መወሰን፣ ፖሊሲውንም ማስፈፀም፣ ዓለም አቀፍ ስምምነቶችን መዋዋል፣ ማፅደቅ
 የአየር፣ የባቡር፣ የባሕር መጓጓዣ፣ የፖስታና የቴሌኮሙኒኬሽን አገልግሎቶች እንደዚሁም ሁለት ወይም ከሁለት በላይ ክልሎችን የሚያገናኙ አውራ መንገዶችን ማስፋፋት፣ ማስተዳደር፣ መቆጣጠር
 ለፌደራሉ መንግስት በተሰጡት የገቢ ምንጮች ክልል(ወሰን) ግብርና ቀረጥ መጣል፣ ማስተዳደር፣ የፌዴራል መንግስት በጀት ማርቀቅ፣ ማፅደቅ፣ ማስተዳደር
 ሁለት ወይም ከሁለት በላይ የሆነ ክልሎችን የሚያስተሳስሩ ወይም ድንበር ተሻጋሪ የሆኑ ወንዞችና ሀይቆችን አጠቃቀም መወሰን፣ ማስተዳደር
 በክልሎች መካከል የሚደረግን የንግድ ግንኙነትና የውጭ ንግድን መምራት፣ መቆጣጠር
 በፌዴራል መንግስት ገንዘብ የተቋቋሙ አንድ ወይም ከአንድ ክልል በላይ የሚሸፍኑ የአገልግሎት ተቋሞችን ማስተዳደር፣ ማስፋፋት
 ከክልል አቅም በላይ የሆነ የፀጥታ መደፍረስ ሲያጋጥም በክልሉ መስተዳዳር ጥያቄ መሰረት የሀገሪቱ የመከላከያ ሀይል ማሰማራት፡፡
 በህገ መንግስቱ መሰረት የተረጋገጡትን የፖለቲካ መብቶች ለማስፈጸም አስፈላጊ የሆኑ የፖለቲካ ድርጅቶችን እንዲሁም ምርጫን በሚመለከት ሕጎችን ማውጣት
 በሀገሪቱ በአጠቃላይም ሆነ በተወሰኑ የሀገሪቱ ክፍሎች የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ማወጅ፣ አዋጁን ማንሳት
 የዜግነት ጥያቄን መወሰን
 የኢምግሬሽንና የፓስፖርት፣ ወደ ሀገር የመግቢያና የመውጫ ጉዳዮችን፣ ስለስደተኞችና ስለ ፖለቲካ ጥገኝነት መወሰን፣ መምራት
 የፈጠራና ድርሰት መብቶችን ፈቃድ መስጠት፣ መጠበቅ
 አንድ ወጥ የመለኪያ ደረጃዎችና የጊዜ ቀመር ማውጣት
 የጦር መሣሪያ ስለመያዝ ሕግ ማውጣት ናቸው፡፡

የክልሎች ሥልጣንና ተግባር

በኢ.ፌ.ዴ.ሪ. ህገ መንግስት አንቀፅ 52 ስር እንደተደነገገው በህገ መንግስቱ ለፌደራሉ መንግስት በተለይ ወይም ለፌደራሉ መንግስትና ለክልሎች በጋራ በግልፅ ያልተሰጠ ሥልጣን የክልል ሥልጣን ነው፡፡ ይህ እንዳለ ሆኖ የክልሎች ሥልጣንና ተግባር የሚከተሉትን ያጠቃልላል፡፡

 ራስን በራስ ማስተዳደርን ዓላማ ያደረገ ክልላዊ መስተዳድር ማዋቀር፣ የህግ የበላይነት የሰፈነበት ዴሞክራሳዊ ሥርዓት መገንባት፣ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. ህገ መንግስትን መጠበቅ፣ መከላከል
 የክልል ሕገ መንግስትና ሌሎች ሕጎችን ማውጣት፣ ማስፈፀም
 የክልሉን የኢኮኖሚ፣ ማህበራዊና የልማት ፖሊሲ ስትራቴጂና ዕቅድ ማውጣት፣ ማስፈፀም
 የፌዴራሉ መንግስት በሚያወጣው ሕግ መሰረት መሬትና የተፈጥሮ ሀብትን ማስተዳደር
 ለክልሉ በተወሰነው የገቢ ምንጭ ወሰን ግብርና ታክስ መጣል፣ መሰብሰብ፣ የክልሉን በጀት ማውጣት፣ ማስፈፀም
 የክልሉን መስተዳድር ሠራተኞች አስተዳደርና የስራ ሁኔታዎች በተመለከተ ሕግ ማውጣት፣ ማስፈፀም፣ ሆኖም ለአንድ የሥራ መደብ የሚያስፈልጉ የትምህርት፣ የስልጠናና የልምድ መመዘኛዎች ከአጠቃላይ የሀገሪቱ መመዘኛዎች ጋር የተቀራረቡ መሆናቸውን የማረጋገጥ ሀላፊነት ይኖርበታል፡፡

 የክልሉን የፖሊስ ሀይል ማደራጀት፣ መምራት፣ የክልሉን ሰላምና ጸጥታ የመጠበቅ ሀላፊነት የክልሎች ስልጣን እንደሆነ በህግ መንግስቱ ተደንግጓል፡፡
የፌዴራሉ መንግስትና የክልሎች ሥልጣን በኢ.ፌ.ዴ.ሪ. ህገ መንግስት የተወሰነ በመሆኑ ለፌዴራሉ መንግስት የተሰጠው ሥልጣን በክልሎች መከበር አለበት፣ ለክልሎች የተሰጠው ሥልጣንም እንዲሁ በፌዴራሉ መንግስት መከበር አለበት፡፡

ማጠቃለያ
የፌዴራል መንግስት እና ክልሎች በህገ መንግስቱ በተሰጣቸው የስልጣን ልክ በመስራት፣ አንዱ የአንዱን ስልጣን እና ሀላፊነት በማክበር የሚጠበቅባቸወን የማስተዳደር ሥራ በአግባቡ መስራት ይጠበቅባቸዋል፡፡

በንቃተ ህግ ትምህርት እና ስልጠና ዳይሬክቶሬት የተዘጋጀ

የፌዴራል የአስተዳደር ሥነ-ሥርዓትን ህግ      መግቢያ መንግስታዊ አሰራር ለሕዝብ ግልፅ በሆነ መንገድ መከናወን አለበት፡፡ ማናቸውም የመንግስት ባለሥልጣን ኃላፊነቱን ሲያጓድል ተጠያቂ እንደ...
22/02/2023

የፌዴራል የአስተዳደር ሥነ-ሥርዓትን ህግ

መግቢያ

መንግስታዊ አሰራር ለሕዝብ ግልፅ በሆነ መንገድ መከናወን አለበት፡፡ ማናቸውም የመንግስት ባለሥልጣን ኃላፊነቱን ሲያጓድል ተጠያቂ እንደሚሆን በኢትዮጵያ ህገ መንግስት በተቀመጡ መሠረታዊ መርሆዎች ተመላክቷል፡፡ በዚህ መርህ የአስተዳደር ተቋማት በሰዎች መብቶችና ጥቅሞች ላይ የሚያወጠጧቸው መመሪያዎች እና የሚሰጧቸው ውሳኔዎች በሕግ የሚመሩ መሆን አለባቸው፡፡ በሀገራችን እነዚህ መመሪያዎች የሚወጡበት እና ውሳኔዎች የሚሰጡበት ሂደት በአስተዳደር ሥነ ሥርአት ህግ የሚመራ ይሆናል፡፡ በዚህ አጭር ፅሁፍ ስለ አስተዳደር ሥነ-ሥርዓት ህግ ምንነት፣ መርሆዎች፣ መመሪያ የማዉጣት ስልጣን፣ የመመሪያ አመዘጋገብ ሥርዓትን እንዲሁም በተለያየ አካል የሚሰጡ አስተዳደራዊ ዉሳኔዎችና ሊከተሉ ስለሚገባው ሥነ ስርዓት እንዳስሳለን፡፡

የአስተዳደር ሥነ-ሥርዓትን ህግ ምንነት

የአስተዳደር ሥነ-ሥርዓት ህግ ከሥነ ሥርአት ህጎች (procedural law) የሚመደብ ሲሆን የአስተዳደር ተቋማት የሚያወጧቸው መመሪያዎች እና የሚሰጧቸው ውሳኔዎች የሚመሩበትን እንዲሁም ቅሬታዎች የሚፈቱበትን ሂደት የሚደነግግ ህግ ነው፡፡ የአስተዳደር ተቋም ማለት አስፈፃሚ አካል ሆኖ በሕግ የተደራጀ የመንግሥት መሥሪያ ቤት ሲሆን ለፌደራል መንግሥት ተጠሪ የሆኑ የከተማ አስተዳደር አስፈፃሚ አካላትን እንደሚጨምር በፌደራል አስተዳደር ሥነ ሥርአት አዋጅ ቁጥር 1183/2012 አንቀፅ 2(1) ሥር ትርጓሜ ተሰጥቶታል፡፡

የአስተዳደር ተቋማት መመሪያ የማውጣት ስልጣንና ሂደት

መመሪያ ማለት የህግ አውጪው አካል በሚሰጠው ስልጣን መሰረት በአስተዳደር ተቋም የሚወጣ እና በሰዎች መብት ወይም ጥቅም ላይ ውጤት የሚያስከትል የህግ ሰነድ ሲሆን በሥራ ላይ ያለ መመሪያን የሚያሻሽል ወይም የሚሽር የህግ ሰነድንም እንደሚጨምር ከአዋጁ አንቀፅ 2(2) መረዳት ይቻላል፡፡ ማንኛውም የአስተዳደር ተቋም መመሪያ ከማውጣቱ በፊት መመሪያ ለማውጣት ስልጣን ያለው መሆኑን ማረጋገጥ ይገባዋል (አንቀፅ 8)፡፡ የአስተዳደር ተቋሙ መመሪያ የማውጣት ስልጣን ያለው መሆኑ ሲረጋገጥ ሊያወጣ የሚገባውን መመሪያ በተገቢው ጊዜ ማዉጣት አለበት፡፡ ይህም እናት ህጉ መመሪያ እንዲያወጣ በአስገዳጅ ሁኔታ በደነገገ ጊዜ በ3 ወራት ውስጥ አስገዳጅ ባልሆነ ሁኔታ በተደነገገ ጊዜ ደግሞ በተገቢው ጊዜ ውስጥ መመሪያውን ማውጣት አለበት፡፡ አንድ የአስተዳደር ተቋም ሊያወጣው የሚገባዉን መመሪያ በተገቢው ጊዜ ሳያወጣ ቢቀር መመሪያውን እንዲያወጣ ማንኛውም ሰው በፅሁፍ ሊጠይቅ ይችላል፡፡ ጥያቄውን ለመመለስ የአስተዳደር ተቋም በ30 የሥራ ቀናት ውስጥ መመሪያውን የማውጣት ሂደት መጀመር ወይም መመሪያውን ማውጣት የማይችል ከሆነ ምክንያቱን በመግለፅ ጥያቄውን ውድቅ ማድረግ አለበት፡፡

መመሪያ የሚያወጣ ተቋም በቅድሚያ ስለሚያወጣው ረቂቅ መመሪያ ሰፊ ስርጭት ባለው ጋዜጣ፣ በተቋሙ ድህር ገፅ እና በሌሎች መገናኛ ብዙሀን ዝርዝር መረጃ የያዘ ማስታወቂያ ማውጣት ይገባዋል (አንቀፅ 8)፡፡ በተጨማሪም የመመሪያውን ረቂቅ ለሚመለከታቸው የአስተዳደር ተቋማትና ሌሎች ባለድርሻ አካላት ለአስተያየት መላክ አለበት፡፡ ተቋሙ ለአስተያየት መስጫ የሚወስነው ጊዜ ካበቃ በኋላ አስተያየት ለመስጠት በቂ ጊዜ የተመደበለት የውይይት መድረክ በማዘጋጀት ግብአት ማሰባሰብ ይጠበቅበታል፡፡

በተጨማሪም የሚወጣው መመሪያ ርእሰ ጉዳይ፣ የመመሪያውን አወጣጥ መርሃ ግብር፣ የረቂቅ መመሪያው ዝግጅት ሚገኝበትን ደረጃ፣ የታተሙ ማስታወቂያዎች ካሉ፣ አስተያየት ስለሚቀርብበት ጊዜ፣ የተሰበሰቡ አስተያየቶችንና በአስተያየቶቹ ላይ የተወሰዱ አቋሞችን በዝርዝር በመዝገብ አደራጅቶ ማስቀመጥ አለበት፡፡ ይህን ሂደት መመልከት የፈለገ ማንኛዉም ሰው የተደራጀዉን ሰነድ መመልከት ወይም አስፈላጊውን ወጪ ሸፍኖ ኮፒ መውሰድ ይችላል፡፡
በመጨረሻም ረቂቅ መመሪያውን ከማፅደቁ በፊት ለአስተያየት ለፍትህ ሚኒስቴር መላክ ያለበት ሲሆን ሚኒስቴሩ በ15 ቀናት ውስጥ ያለውን አስተያየት መስጠት ይጠበቅበታል፡፡

ሚኒስቴሩ በተጠቀሰው ጊዜ ውስጥ አስተያየት ካልላከ አስተያየት እንደሌለው ተቆጥሮ የማፅደቁ ሂደት ይቀጥላል፡፡ መመሪያ ከፀደቀም በኋላ ከነማብራሪያ ፅሁፉ ለፍትህ ሚኒስቴር ተልኮ መመዝገብ አለበት፡፡ ይህም መመሪያውን ለላከው አስተዳደር ተቋም እንዲያውቀው መደረግ ያለበት ሲሆን ከዚህ ቀን ጀምሮ በተቋሙ ድህረ ገፅ ላይ በመጫን፣ አሳትሞ ለሚመለከታቸው አካላት በመላክ፣ ቅጂውን ማግኘት የሚፈልግ ሰው መመሪያ ባለበት መመልከት እንዲችል ወይም ወጪውን ሸፍኖ ኮፒ ማግኘት እንዲችል በማመቻቸት ለህዝብ ክፍት እና ተደራሽ እንዲሆን ማድረግ አለበት፡፡

በሌላ በኩል ማንኛውም የአስተዳደር ተቋም ይህ አዋጅ ከመውጣቱ በፊት በሥራ ላይ የነበረ መመሪያን ይህ አዋጅ በወጣ ከ90 ቀናት ባልበለጠ ጊዜ ውስጥ ለፌደራል የፍትህ ሚኒስቴር በመላክ እንዲመዘገብ የማድረግ ግዴታ ጥሏል፡፡ በዚህ አግባብ ያልተመዘገበ እና በድህረ ገፅ ላይ ያልተጫነ ማናቸውም መመሪያ ተፈፃሚነት አይኖረውም፡፡

መመሪያ ለህዝብ ግልፅ ማድረግ የማይፈቀድባቸው ሁኔታዎች

አዋጁ አንቀፅ 11 ማንኛውም የአስተዳደር ተቋም መመሪያ ሲያወጣ የተጠቀሰውን ሂደት የማይከተልባቸው ልዩ ሁኔታዎችን ደንግጓል፡፡ ይኸውም የአስቸኳይ ጊዜ ሁኔታ በመኖሩ በህጉ የተቀመጡ ግዴታዎቹ ውስጥ ለማለፍ ጊዜ የማይፈቅድ ሲሆን፣ ስለመመሪያው ቅድመ ማስታወቂያ ማውጣቱ የሕዝብን ጥቅም የሚጎዳ ሆኖ ሲገኝ እንዲሁም ቅድመ ማስታወቂያ ማውጣቱ የመመሪያውን ተፈፃሚነት ፋይዳ ቢስ የሚያደርግ ሆነ ሲገኝ ናቸው፡፡ መሰል ሁኔታዎች ሲኖሩ ተቋሙ ምክንያቱን የያዘ ዝርዝር መግለጫ ማዘጋጀት ይጠበቅበታል፡፡

አስተዳደራዊ ጥያቄዎችና ውሳኔዎቹ የሚመሩበት መርሆች

አስተዳደራዊ ውሳኔ ማለት መመሪያ ማውጣትን ሳይጨምር የአስተዳደር ተቋም በዕለት ተዕለት ተግባሩ በሰዎች መብት ወይም ጥቅም ላይ ሚሰጠው የአስተዳደር ውሳኔ ነው፡፡ የአስተዳደራዊ ጉዳዮች የሚወስን ሰው የሚከተሉትን መርሆች መከተል ይኖርበታል፡፡ እነሱም ውሳኔ ለመስጠት ሀላፊነት የተሰጠው መሆን፣ ውሳኔ ሲሰጥ በሕግ የተሰጠ ሥልጣን ወሰንን አለማለፍ፣ የግል እና የሕዝብ ጥቅምን ማመዛዘን፣ ሙያዊ ትጋትና ሥነ ምግባርን በመከተል ውሳኔ መስጠት፣ በአግባቡ ማዳመጥ፣ በቅን ልቦና መወሰን፣ ለውሳኔው በቂ ምክንያት መስጠት፣ ከተገልጋዩ ጋር የሥጋ ወይም የጋብቻ ዝምድና ያለው ከሆነ ወይም በማናቸውም ሁኔታ የጥቅም ግጭት ካለ እራስን ከዉሳኔ ማግለል፣ የተገልጋዮችን እኩልነት ማክበር፣ በተገቢው ጊዜ መወሰን፣ ተገማች መሆን ወይም በፍሬ ነገር ተመሳሳይ በሆኑ ጉዳዮች ተመሳሳይ ውሳኔ ማሳለፍ እና በውሳኔ አሰጣጡ ግልፅነትን የተከተለ ሂደት መከተል ናቸው፡፡

ለአስተዳደራዊ ውሳኔ የሚቀርብ ጥያቄ ጉዳዩ በሚመለከተው ሰው ወይም በወኪሉ እንዲሁም በሚመለከተው የአስተዳደር ተቋም አነሳሽነት ሊጀመር ይችላል (አንቀጽ 20)፡፡ የአስተዳደር ውሳኔ ጥያቄ በፅሑፍ ሆኖ እንደሁኔታው በአካል፣ በተመዘገበ ፖስታ ወይም በኤሌክትሮኒክ ዘዴ ሊቀርብ ይችላል፡፡ አቤቱታ በፅሑፍ ሲቀርብ ቀን፣ የአቤቱታ አቅራቢው ወይም ወኪሉ ስም፣ ፊርማ እና አድራሻ፣ የሚፈፅመው ተቋም ስም፣ የአቤቱታ አቅራቢው መብት ወይም ጥቅም፣ ተቋሙ ሊፈፅመው የሚገባ አስተዳደራዊ ተግባር እና የሚቀርቡ ምክንያቶች ማካተት ያለበት ሲሆን ተያያዥ ማስረጃዎች ተያይዘው መቅረብ ይኖርባቸዋል፡፡

አቤቱታ የቀረበለት ተቋም አቤቱታውን የተቀበለ መሆኑን መዝግቦ የማረጋገጫ ፅሑፍ መስጠት አለበት፡፡ ውሳኔውን የሚሰጠዉ ሰው ሙያዊ ትጋትና ሥነ ምግባርን በተላበሰ መልኩ የፍሬ ነገሩን እና ማስረጃ በሚገባ ማዳመጥ፣ መመርመር፣ የሕዝብን አስተያየት ማዳመጥ እንዲሁም የጥቅም ግጭትን ካለ ራስን ማግለል ይኖርበታል፡፡ የሚሰጠው ዉሳኔ የተገልጋይን የግል ጥቅም እና በአስተዳደር ተቋሙ ዓላማ የተመለከተውን የሕዝብ ጥቅም ማመዛዘን አለበት /አንቀጽ 25/፡፡

የአስተዳደር ውሳኔ የሚሰጥበት ሥነ ሥርዓት

በአዋጁ አንቀፅ 36 እና 37 መሰረት ማንኛውም አስተዳደራዊ ውሳኔ ከመሰጠቱ በፊት ጉዳዩ በሚገባ መሰማት ያስፈልጋል፡፡ ጉዳዩ በሚሰማበት ጊዜ ባለጉዳዩ በክርክሮች ሂደት ሁሉ ተገኝቶ ምስክርነት የመስጠት፣ ምስክሮችን እና ሌሎች ማስረጃዎችን የማቅረብ፣ የማሰማት እንዲሁም ተቃራኒ ወገን የሚያቀርበውን ማስረጃ መመርመርና የማስተባበል መብት አለው፡፡ የአስተዳደር ተቋሙ ማስረጃ ለማግኝት ከፈለገ በክርክሩ ተካፋይ ከሆነ ወገን ወይም ሌሎች ማናቸውንም አስፈላጊ ማስረጃዎችን ለማግኘት ሕጋዊ ዘዴዎችን መጠቀም ይችላል፡፡

ውሳኔ

በአስተዳደሩ የተሰጠው ውሳኔ ከነምክንያቱ ለተገልጋዩ በፅሑፍ መሠጠት አለበት፡፡ ውሳኔውም በፅሑፍ ሆኖ የውሳኔ ቀንና ቁጥር፣ የተቋሙን ስም፣ በክርክሩ ተካፋይ የሆኑ ወገኖችን አድራሻ፣ አከራካሪ ፍሬ ነገር፣ የማስረጃዎች ትንተና፣ የፍሬ ነገር እና የሕግ ትንታኔ እና በጉዳዩ ላይ ተሰጠውን ውሳኔ መያዝ ይኖርበታል፡፡ በጉዳይ ለተሰጣቸው ውሳኔ ቅሬታ ካላቸው ለሚመለከታው አካል በህግ የተቀመጠዉ ጊዜ ሣያልፍ በሌላ የፍትህ መድረክ መብታቸውን ለማረጋጋጥ ይረዳል፡፡ በተሰጠዉ ዉሳኔ የማይመለስ ጉዳት የሚደርስ ሆኖ ከተገኘ ወሳኔው እንዲታገድለት ውሳኔውን ለሰጠው ተቋም አቤቱታ ሊያቀርብ ይችላል፡፡ አቤቱታው ተቀባይነት ካገኘ ጉዳዩ እንደገና እንዲታይ ወይም የውሳኔውን ማናቸውም ክፍል ሊያግደው ይችላል (አንቀጽ 41)፡፡

ቅሬታ የሚፈታበት ሥነ ሥርዓት

ማንም ሰው በተሰጠው ውሳኔ ላይ ቅሬታ የማቅረብ ህገ መንግሰታዊ መብት አለው፡፡ ቅሬታ የሚቀርበው በተቋሙ ለተቋቋመው የቅሬታ ማስተናገጃ አካል ይሆናል፡፡ በዚህ አዋጅ አንቀጽ 45 መሰረት ቅሬታ የቀረበበት ውሳኔ ተመርምሮ እስኪወሰን ድረስ ዉሳኔው አይፈጸምም፡፡ ሆኖም የውሳኔው ሳይፈፀም መቆየት በሕዝብ ላይ የማይመለስ ጉዳት የሚያስከትል ከሆነ የአስተዳደር ተቋሙ የበላይ ኃላፊ ዉሳኔው እንዲፈፀም ሊያዝ ይችላል፡፡ የቅሬታ ማስተናገጃ አካል ቅሬታውን በሚገባ መመርመር እና የውሳኔ ሀሳብ ለአስተዳደር ተቋሙ የበላይ ኃላፊ ወይም እሱ ለወከለው የሥራ ኃላፊ ማቅረብ አለበት፡፡ የበላይ ኃላፊ ወይም እሱ የወከለው የሥራ ኃላፊ በቅሬታ ማስተናገጃ አካል የቀረበለትን የውሳኔ ሀሳብ ተመልክቶ የመጨረሻ ውሳኔ ይሰጣል (አንቀጽ 46)፡፡ ይህ ውሳኔ ወዲያውኑ በፅሑፍ ለቅሬታ አቅራቢው መስጠት አለበት፡፡ በፅሑፍ የሚሰጥበት ዋና ዓላማ የክለሳ አቤቱታ ለፍርድ ቤት ለማቅረብ ስሚያግዝ ነው፡፡

በፍርድ ቤት የሚሰጥ የክለሳ ውሳኔ

ከላይ በተመለከተው አስተዳደራዊ ውሳኔ መሰረት ቅሬታ ያደረበት ማንም ሰው ለፍርድ ቤት ለክለሳ ማቅረብ ይችላል፡፡ በአንቀፅ 49 መሰረት ጉዳዩን የሚመከለተው የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ነው፡፡ ቅሬታውም የአስተዳደር መመሪያውን በተመለከተ ወይም በተሰጠው ውሳኔን የተመለከተ ይሆናል፡፡ የአስተዳደር ውሳኔን በተመለከተ የመጨረሻ ፍርድ የሚሰጠው ከፍተኛ ፍርድ ቤት ሲሆን መመሪያን የተመለከተ ቅሬታ ሲሆን ደግሞ ለጠቅላይ ፍርድ ቤት ይግባኝ ሊቀርብበት ይችላል (አንቀጽ 49 (1 እና 2)፡፡

የአስተዳደር መመሪያ በፍርድ ቤት የሚከለሰው በሶስት ምክንያቶች ሲሆን ይህም
1. በዚህ አዋጅ የተመለከቱትን የሥነ ሥርዓት ድንጋጌዎች ሳይከተል የወጣ መሆኑ ሲረጋገጥ
2. ከተቋሙ የሥልጣን ገደብ ውጪ የወጣ ሲሆን፣
3. ከመመሪያ በላይ ከሆኑ ሌሎች ህጎች የሚቃረን ሲሆን ሲገኝ ነው፡፡

በሌላ በኩል የአስተዳደር ውሳኔ የሚከለሰው በዚህ ከላይ ተጠቀሱ አስተዳደራዊ ጥያቄዎችና ውሳኔዎቹ የሚመሩባቸውን መርሆዎች የጣሰ ሲሆን ነው (አንቀጽ 50 (1 እና 2)፡፡ ቅሬታው መመሪያው ከፀደቀበት ቀን በሚቆጠር በ90 ቀናት ጊዜ ውስጥ መቅረብ የሚገባው ሲሆን ውሳኔውን የተመለከተ ከሆነ ዉሳኔ ከታወቀበት ቀን ጀምሮ በሚቆጠር የ30 ቀናት ጊዜ ውስጥ መቅረብ እንዳለበት ተመላክቷል፡፡ ለውሳኔ ክለሳ አግባብነት ያላቸው የፍትሐብሔር ሥነ-ሥርዓት ሕግ ድንጋጌዎች ተፈፃሚ የሚሆኑ ሲሆን ፍርድ ቤት ዉሳኔውን ወይም መመሪያዉን ሊያፀና ወይም በሙሉ ወይም በከፊል ሊሽር ይችላል (አንቀፅ 57)፡፡

ማጠቃለያ

የአስተዳደራዊ የሥነ ሥርዓት ህግ ዜጎች ተገቢውን አስተዳደራዊ አገልግሎት እንዲያገኙ እና ቅሬታ ሲኖራቸውም እስከ ፍርድ ቤት ቀርበው መብታቸውን ማረጋገጥ የሚችሉበትን ሥርዐት የዘረጋ በመሆኑ ማህበረሰቡ ይህን በመረዳት መብትና ግዴታውን በማረጋገጥ ለህጉ ተፈፃሚነት የበኩሉን ድርሻ ሊወጣ ይገባል፡፡

በንቃተ ህግ ትምህርትና ስልጠና ዳይሬክቶሬት የተዘጋጀ

Address

Gonderoch

Website

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when የቋራ ወረዳ ፍትህ ጽ/ቤት/Quara wereda justice office posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

Share