06/07/2026
በጎፋ ዞን ሣውላ ከተማ የ2018 የግብር አሰባሰብና የ2019 የንግድ ፈቃድ ዕድሳት ዘመቻ አስመልክቶ የተካሄደ የማስፈጸሚያ መድረክ
#ሣውላ፣
ሰኔ 29/2018 ዓ.ም
የሣዉላ ከተማ ገቢዎች ጽ ቤት
በጎፋ ዞን ሣውላ ከተማ የ2018 የግብር ዓመት የግብር አሰባሰብና የ2019 የንግድ ሥራ ፈቃድ ዕድሳት ሥራዎችን በተቀናጀና ውጤታማ መንገድ ለማስፈጸም ያለመ የማስፈጸሚያ መድረክ በከተማው ተካሂዷል። በመድረኩ የከተማው አመራሮች፣ የገቢ፣ የንግድ፣ የፋይናንስ፣ የማዘጋጃ ቤት፣ የመሬት አስተዳደር፣ የህግ አስከባሪ አካላት፣ የቀበሌ አመራሮችና ሌሎች ባለድርሻ አካላት በስፋት ተሳትፈዋል።
ሰነዱን ያቀረቡት የሣውላ ከተማ ምክትል ከንቲባና የገቢዎች ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ጌታሁን ኩማ እንዳብራሩት፣ የ2018 የግብር ዓመት የግብር አሰባሰብና የ2019 የንግድ ፈቃድ ዕድሳት ሥራ በቅድመ ዝግጅት፣ በቅንጅትና በዘመናዊ ቴክኖሎጂ ተደግፎ መፈጸም የሚገባ ሀገራዊ ተልዕኮ መሆኑን ገልጸዋል። ለዚህም የገቢ ጽ/ቤትና የንግድ ጽ/ቤት በጋራ የማስፈጸሚያ ዕቅድ በማዘጋጀት ከሁሉም ባለድርሻ አካላት ጋር በቅርብ በመቀናጀት እንደሚሰሩ አስረድተዋል።
አቶ ጌታሁን ኩማ እንደገለጹት፣ በ2017 የግብር ዓመት የተመዘገቡ ጠንካራ አፈጻጸሞች ለ2018 ሥራ ጥሩ መነሻ ቢሆኑም የታዩ ጉድለቶችን በመለየት እንዳይደገሙ ማድረግ ወሳኝ መሆኑን ጠቁመዋል። በተለይ የግብር ከፋዮች መረጃን ማጥራት፣ የሲስተም አጠቃቀምን ማስፋት፣ የቴሌብር ክፍያን ማሳደግ፣ የታክስ ከፋዮችን ሕግ ተገዥነት ማጠናከርና የባለድርሻ አካላትን ቅንጅት ማሳደግ የዘመቻው ዋና ትኩረቶች መሆናቸውን ገልጸዋል።
እንዲሁም የግብር አስተዳደሩን ለማዘመን በSIGTAS ሲስተም፣ በኢ-ፋይሊንግ፣ በኢ-ፔይመንትና በቴሌብር የሚሰጠው አገልግሎት የግብር ክፍያን ቀላል፣ ፈጣንና ግልጽ እንደሚያደርገው ጠቅሰው፣ በቀጣይ ሁሉም የግብር ከፋዮች ዘመናዊ የክፍያ ሥርዓትን እንዲጠቀሙ የማስተዋወቅና የድጋፍ ሥራ እንደሚጠናከር ገልጸዋል።
በተጨማሪም ሰነድ ያቀረቡት የሣውላ ከተማ ንግድ ጽ/ቤት ኃላፊ አቶ ታደለ ሰለሞን እንዳብራሩት፣ የ2019 የንግድ ሥራ ፈቃድ ዕድሳት ሥራ ከግብር አሰባሰብ ጋር በአንድ ማዕከል ተቀናጅቶ እንደሚከናወን ገልጸዋል። ይህም የአገልግሎት ፍጥነትን በማሻሻል የተገልጋዮችን እንግልት እንደሚቀንስና የንግድ ፈቃድ ዕድሳትን በጊዜው እንዲፈጽሙ ምቹ ሁኔታ እንደሚፈጥር ገልጸዋል።
አቶ ታደለ አክለውም ሕገ-ወጥ ንግድን መከላከል፣ ያልታደሱ ፈቃዶችን በጊዜው ማደስ፣ ከግብር ሥርዓቱ ውጭ ያሉ ነጋዴዎችን ወደ ሥርዓቱ ማስገባትና ከሌሎች ተቋማት ጋር የመረጃ ልውውጥን በማጠናከር ገቢን ማሳደግ የተቋሙ ቀዳሚ ተግባራት መሆናቸውን ገልጸዋል።
በመድረኩ ንግግር ያደረጉት የሣውላ ከተማ ክብር ከንቲባ አቶ በላይነህ ባህሩ እንደገለጹት፣ የግብር አሰባሰብ የመንግሥት ገቢን ከማሳደግ ባለፈ የከተማውን ልማት የሚያጠናክር መሠረታዊ ተግባር መሆኑን ገልጸዋል። ስለሆነም ሁሉም አመራር፣ ባለሙያ፣ የቀበሌ አመራሮች፣ የህግ አስከባሪ አካላትና የህብረተሰቡ ክፍሎች በተጠናከረ ቅንጅት እንዲሰሩ አሳስበዋል።
ከንቲባው በተለይ የግብር ከፋዮች ግዴታቸውን በወቅቱ በመወጣት ለከተማው ልማት ያላቸውን አስተዋጽኦ እንዲያጠናክሩ ጥሪ ያቀረቡ ሲሆን፣ ሁሉም ተቋማት በአገልግሎት ጥራት፣ በፍትሃዊነትና በተጠያቂነት በመስራት የህዝቡን እምነት ማጠናከር እንደሚገባ ገልጸዋል።
በተመሳሳይ የሣውላ ከተማ ብልፅግና ፓርቲ ቅ/ጽ ቤት ኃላፊ አቶ ከተማ ከበድ እንደገለጹት፣ የግብር አሰባሰብ የመንግሥት ሥራ ብቻ ሳይሆን የሁሉም ዜጎች የጋራ ኃላፊነት መሆኑን ጠቁመዋል። በመሆኑም የፓርቲ አደረጃጀቶች፣ የወጣቶችና የሴቶች ክንፎች፣ የታክስ አምባሳደሮችና ሌሎች ማህበራዊ አደረጃጀቶች በቅስቀሳ፣ በግንዛቤ ፈጠራና በሕዝብ ንቅናቄ ሥራ በንቃት እንዲሳተፉ ጥሪ አቅርበዋል።
አቶ ከተማ ከበድ አክለውም፣ የሕግ ተገዥነትን በማጠናከር፣ የግብር አጭበርባሪነትን በመከላከልና ህብረተሰቡ ደረሰኝ የመጠየቅ ባህሉን እንዲያጠናክር በተቀናጀ መንገድ መስራት የሚያስፈልግ መሆኑን ገልጸዋል።
በመጨረሻም በመድረኩ የተሳተፉ አካላት የ2018 የግብር አሰባሰብና የ2019 የንግድ ፈቃቭ
ድ ዕድሳት ሥራዎችን በተቀናጀ አመራር፣ በውጤታማ ቅንጅትና በህዝብ ተሳትፎ በማከናወን የታቀደውን ግብ ለማሳካት በጋራ እንደሚሰሩ ቃል ገብተዋል።
Facebook
የሣዉላ ከተማ አስተዳደር ገቢዎች ጽ/ቤት/Sawla Town Administration Revenue Office
Telegram
t.me/SawlaTownRevenueOffice