27/05/2026
ትናንት፣ ዛሬና ነገ....
በሀገራችን ውስጥ በሚዛን ሊያዝ የሚገባው ነገር በትናንት፣ በዛሬና በነገ መካከል ያለው ምልከታ ነው፡፡ ትናንትን ፈፅሞ የመቀደስም ሆነ ትናንትን ፈፅሞ የማርከስ ጉዞ ሀገርን ያለ ወረት ያስቀራል።
ዛሬንና ነገን ማቃለልም ሆነ ዛሬና ነገን የሁሉም ነገር መጀመሪያ ማድረግ ሀገርን ያለ መነሻ ያስቀራል፡፡ ብልፅግና ትናንት ከዛሬና ከነገ ጋር በሚዛን የሚታይበትን መርሕ ይከተላል፡፡
• ከትናንቱ መልካሙን መውሰድ፤ እንከኑን ማረም
• ዛሬን፣ በትናንት መሠረት ላይ ገንብቶ በሚገባ መጠቀም
• ለነገ ተግባብቶ ወረት ማቆየት
ትናንትን ከዛሬና ነገ ጋር በሚዛን ለማየት እንዲቻል፣ የትናንት ቁርሾዎችን የምናክምባቸው፣በትናንትጉዞ ላይ የምንግባባባቸው ፤ ነገን በጋራ የምንተልምባቸው መንገዶችን መከተል አለብን ብሎ ያምናል፡፡
እነዚህም፡-
👉በሰከነ ምክክር አዲስ ቃል ኪዳን ማሠር ፤
ጠንካራና ቅቡልነት ያለው ሀገረ መንግሥት በፅኑ መሠረት ላይ ለመገንባት፣ ሀገራዊ መግባባትን መፍጠር እንደሚያስፈልግ ፓርቲያችን በቀዳሚነት አስቀምጧል፡፡ለዘመናት በመሠረታዊ ሀገራዊ ጉዳይ እንኳን ያላግባቡን ጉዳዮች በሀገራዊ ምክክር ምላሽ እንዲያገኙ ቁርጠኛ አቋምም አለው። ፓርቲያችን ብሔራዊ መግባባት ለሀገረ መንግሥቱ ግንባታ የማዕዘን ድንጋይ እንደሆነ ያምናል።
የፖለቲካ ማኅበረሰቡ የትናንት ቅራኔዎችን በመግባባትና በዕውቅና፣ በዕርቅና በሽግግር ፍትሕ መፍታት እንዳለበት እናምናለን፡፡ ስለዚህም በስክነትና በዕውቀት፣ ሀገራዊ ምክክሩ እንዲሠምር ሕዝባችንና የፖለቲካ ልሂቃን አዎንታዊ ሀገራዊ ድርሻቸውን እንዲወጡ ጥሪ አናቀርባለን።
በዚህ የጸና እምነታችንና መሻታችን የተነሣ የኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽንን በማቋቋም ሂደት እንደ ፓርቲና እንደ መንግሥት የሚጠበቅብንን አድርገናል፡፡
የሕዝብ ተሳትፎን በማረጋገጥ፣ ለኮሚሽኑ ሥራ አስፈላጊ የሆኑትን የፋይናንስ፣ የሎጀስቲክስና የመረጃ አቅርቦቶችን ያለተዐቅቦ በማሟላት፣ እንዲሁም ነጻነቱን በማክበር ባለፈው ምርጫ ዘመን ቃል የገባንውን በተግባር ፈፅመናል።
በቀጣይ አምስት ዓመታትም፡-
በኢትዮጵያ ሀገራዊ የምክክር ኮሚሽን መሪነት በሂደት የሚደረስባቸው ውሳኔዎችና ምክረ ሐሳቦች ይኖራሉ ብለን ተስፋ እናደርጋለን፡፡
እነዚህን ውሳኔዎችና ምክረ ሐሳቦች ወስደን ለሕገ መንግሥት ማሻሻያዎች፣ ለፖለቲካ ሥርዓት ማሻሻያዎች፣ ለሰብአዊ መብቶች ማሻሻያዎች እና ለቀደሙ በደሎች የመፍትሔ መንገዶች አድርገን እንደ ፓርቲና መንግሥት ለመፈጸምና ለማስፈጸም እንሠራለን።
👉በሽግግር ፍትሕ መሥመር፤ ቁርሾን መሻር ፤
በኢትዮጵያ ለዘመናት የኖሩ በደሎች፣ ቁርሾዎችና የሰብአዊ መብት ጥሰቶች አሉ፡፡ እነዚህን በተመለከተ ፈውስ የሚሰጥ ፍትሕን እና ይቅርታን ለማረጋገጥ የሽግግር ፍትሕ እንደሚያስፈልገን ፓርቲያችን ያምናል። ይህንን መሠረት በማድረግም ባለፉት ዓመታት ሕጋዊና ተቋማዊ ሥራዎች ተጀምረዋል፡፡
በቀጣይ ዓመታትም፡-
ለተፈጸሙ በደሎች እና የሰብአዊ መብት ጥሰቶች በሽግግር ፍትሕ ማዕቀፍ የወንጀል ምርመራና ክስ፣ እውነትን የማፈላለግ እና ይፋ የማውጣት ተግባር፣ በቅድመ ሁኔታ ላይ የተመሠረተ ምሕረት፣ ግለሰባዊ እና ማኅበረሰባዊ ዕርቅ ለማስፈን እንሠራለን፡፡
ይህንንም ተግባራዊ ለማድረግ ሕጋዊና ባህላዊ መንገዶችን እንጠቀማለን፤ ማካካሻና ተቋማዊ ማሻሻያን ይተገበራል።በዚህም ተጎጂዎችን ማዕከል ያደረገ የሽግግር ፍትሕ እንደ ሀገር እንዲተገበር እንሠራለን።
የብሔራዊ መግባባት፣ የዕርቅና የፍትሕ ሂደት እንዲሠምር የሀገራትን ተሞክሮ ከሀገራዊ ነባራዊ ሁኔታ ጋር አስማምተን እንጠቀማለን። እንዲሁም ባሕላዊ የግጭት አፈታትና የዕርቀ ሰላም ሥርዓቶችን እንደየአካባቢው እንተገብራለን፡፡ ይህንንም በማድረግ ሀገራዊ አንድነታችንን እና ብሔራዊ መግባባታችንን እናጠናክራለን፡፡
የሽግግር ፍትሕ ሂደት ከተፅዕኖ እና ከፖለቲካዊ ጣልቃ ገብነት ነጻ እና ገለልተኛ ሆኖ እንዲከናወን እናደርጋለን፡፡ ተአማኒነቱን እና ቅቡልነቱን ለማረጋገጥ፣ ሐቅ አፈላላጊ ኮሚሽን፣ ልዩ ዐቃቤ ሕግና ልዩ ችሎት ይቋቋምለታል፡፡
በእነዚህ ተቋማት በሚመራ ምርመራና ዳኝነት አማካኝነት እንዲከናወን በማድረግ፣ የሽግግር ፍትሕ ያስቀመጣቸውን ብሔራዊ ግቦች እንዲመታ እናደርጋለን።
👉የተሐድሶ ፕሮግራም ፤
በተለያዩ አካባቢዎች ነፍጥ አንግተው ጫካ የገቡ አካላት ወደ ሰላም መንገድ እንዲመጡ ፓርቲያችን ሲሠራ ቆይቷል፡፡ በዚህ መንገድም በሺዎች የሚቆጠሩ ታጣቂዎች የሰላም አማራጭን ተቀብለው ገብተዋል።
እነዚህ ታጣቂዎች በተሐድሶ ፕሮግራም ውስጥ እንዲያልፉ ማድረግ ይገባናል፡፡ ታጣቂ ቡድኖች እንዲበተኑ፤ ታጣቂዎች ትጥቅ እንዲያወርዱ እና ወደ ሰላማዊው መንገድ እንዲቀላቀሉ ለማድረግ የቦታ፣ የገንዘብ፣ የቴክኒክ እና የሥነ ልቦና ዝግጅት ይፈልጋል፡፡
ለዚህ ታላቅ ተግባር የሚያስፈልገውን የሰው ኃይል፣ የበጀትና የቁሳቁስ ዝግጅት በማከናወን የተሐድሶን ፕሮግራም በተሟላ መልኩ ለማከናወንና የጸና ሰላምን ለመመሥረት ፓርቲያችን ይሠራል፡፡
#ኢትዮጵያንወደተምሳሌትሀገር
#ብልፅግናፓርቲንይምረጡ