27/05/2026
"ምርጫው በሰላም እንዲጠናቀቅ በቂ እና አስተማማኝ የጸጥታ ዝግጅት ተደርጓል" እሸቱ የሱፍ (ዶ.ር)
7ኛው ጠቅላላ ምርጫ በሰላም እንዲከናወን የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች ሲከናወኑ መቆየታቸውን የአማራ ክልል ሰላም እና ጸጥታ ቢሮ ኀላፊ እሸቱ የሱፍ (ዶ.ር) ገልጸዋል።
ምርጫው በሰላማዊ መንገድ እንዲካሄድ ለማስቻል በምርጫ ክልል እና በምርጫ ጣቢያዎች የሰው ኀይል ሥምሪት መደረጉንም ጠቁመዋል።
በተለይም በምርጫው ዕለት የሰላም እና የጸጥታ ችግሮች እንዳይፈጠሩ የክልሉ የጸጥታ ኀይል ከፌዴራል የጸጥታ መዋቅር ጋር በመቀናጀት ወደ ሥራ መገባቱን ዶክተር እሸቱ የሱፍ አረጋግጠዋል።
አሁን ላይ በክልሉ ባሉ ሁሉም የምርጫ ክልሎች እና ጣቢያዎች መራጩ ድምጹን መስጠት የሚችልበት አስተማማኝ ሰላም መኖሩን እና በቂ የጸጥታ ዝግጅት መደረጉንም ኀላፊው አብራርተዋል።
የጸጥታ ኀይሉ በተጠንቀቅ የቆመው ለሀገር ሉዓላዊነት እና ሕዝቡ ይመራኛል ብሎ ያመነበትን መንግሥት በሰላም እና በነጻነት እንዲመርጥ ነው ብለዋል።
የክልሉ መንግሥት ምርጫን ለማደናቀፍ የሚንቀሳቀስን ኀይል እንደማይታገስ ያነሱት ኀላፊው እንዲህ ዓይነት ክስተቶችን የጸጥታ ኀይሉ በአግባቡ የመምራት እና እርምጃ የመውሰድ ኀላፊነቱን እንደሚወጣም አረጋግጠዋል።