26/05/2026
የባሕርዳር ከተማ አሥተዳደር የመኖሪያ ቤት መሥሪያ ቦታ ካሳ ክፍያን ይፋ አደረገ።
----------------------
ባሕር ዳር: ግንቦት 17/2018 ዓ.ም :- የባሕርዳር ከተማ አሥተዳድር ከንቲባ ኮሚቴ ዛሬ ባካሄደው አስቸኳይ ስብሰባ ልዩ ልዩ ውሳኔዎችን ማስተላለፉን ከከተማ አሥተዳደሩ ኮሙኒኬሽን የተገኘው መረጃ አመልክቷል።
ከውሣኔዎች መካከልም የመንግሥትና የግል ተቋማት እና የጸጥታ አካላት የመኖሪያ ቤት መሥሪያ ቦታ ካሳ ይገኝበታል።
ከተማ አሥተዳደሩ በቅርቡ ከ780 በላይ የመኖሪያ ቤት ኅብረት ሥራ ማኅበራት እውቅና መስጠቱ ይታወቃል። ከንቲባ ኮሚቴው አንድ በቤት ማኅበር የተደራጀ አባል 2 መቶ 20ሺህ ብር ለካሣ ክፍያ መክፈል የሚጠበቅበት መሆኑን ነው ዛሬ የወሰነው።
ኾኖም ግን የከተማ አሥተዳደሩ ከንቲባ ኮሚቴ የዝቅተኛና የመካከለኛ ነዋሪዎችን የመቆጠብ አቅም ግምት ውስጥ በማስገባት እና ዜጎችን የቤት ማኅበር ተጠቃሚ እንዲሆኑ በማሰብ ለቅድመ ቁጠባ አባላት የከፈሉትን 120ሺህ ብር የካሳ ክፍያው አካል እንዲሆን በሙሉ ድምጽ መወሰኑ ተገልጿል።
በዚህም 120ሺህ ብር የቆጠበ የማኅበር አባል ለካሣ ክፍያ የሚጠበቅበት ተጨማሪ 100 ሺህ ብር መኾኑ ነው የተጠቀሰው። ይህንም በባንክ እንዲከፍል ተደርጎ የመኖሪያ ቤት መሥሪያ ቦታ ተጠቃሚ መሆን እንደሚቻል ተገልጿል።
ከንቲባ ከሚቴው ይህ ውሣኔ በማስታወቂያ ከተገለፀበት ጊዜ ጀምሮ የየማኅበሩ አባላት በተፈቀደው አጭር ቀናት ከላይ የተገለፀውን ክፍያ በባንክ ገቢ ማድረግ እንደሚጠበቅባቸው አስታውቋል።
@አሚኮ