15/05/2026
በደቡብ ኦሞ ዞን ሐመር ወረዳ በ 24 ሚሊዮን ብር ወጪ የተገነባው ዘመናዊ የቁም እንስሳት ግብይት ማዕከል ተመረቀ
አርባምንጭ ግንቦት 7 /2018 ዓ.ም በደቡብ ኦሞ ዞን ሐመር ወረዳ ካራ ቆርጮ የተገነባዉ የአንደኛ ደረጃ የቁም እንስሳት ግብይት ማዕከል የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል መስኖና ቆላማ አካባቢ ቢሮ ኃላፊ ክቡር አቶ ኤካል ነትር ፣ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ም/ቤት ምክትል አፌ ጉባኤ ክብርት ወ/ሮ ወላይቴ ቢቶ እና የሐመር ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ ክቡር አቶ ሳሙኤል ጋርሾ በተገኙበት ተመርቆ ለአገልግሎት ክፍት ሆኗል።
በምረቃው ሥነ-ሥርዓት ላይ የደቡብ ኢትዮጵያ ክልል መስኖና ቆላማ አካባቢ ቢሮ ኃላፊ አቶ ኤካል ነትር ማዕከሉ በክልሉ ቆላማ አከባቢዎች ኑሮ ማሻሻያ ፕሮጀክት (LLRP) ፕሮጀክት ድጋፍ መገንባቱን ገልፀዋል።
ፕሮጀክቱ በተያዘለት ጊዜ ተጠናቆ ለአገልግሎት መብቃቱ እንዳስደሰታቸዉ ኃላፊዉ ገልፀው ይህም መንግሥት ለዘርፉ የሰጠውን ትኩረትና የኢኮኖሚ አካታችነት ማሳያ መሆኑን አስሴድተዋል።
አያይዘውም በካራ ቆርጮ የተገነባው ዘመናዊ ደረጃ አንድ የእንሰሳት የገበያ ማእከል ህገወጥ የንግድ ግብይትን ከማስቀረት እና ከመቆጣጠር አንፃር ሚናው ከፍተኛ መሆኑን አስታውቀዋል ።
በ24 ሚሊዮን ብር ወጪ የተገነባው የካራ ቆርጮ የአንደኛ ደረጃ የቁም እንስሳት ግብይት ማዕከል በሐመር ወረዳ በኛንጋቶም ወረዳ ኬንያ ቱርካና ደረጃ የሚታየውን የገበያ መሰረተ ልማት ስብራት ለመሙላት ትስስሩን ለማጠናከር የተያዘው ዕቅድ አካል መሆኑን ተገልጿል ።
የሐመር ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ ክቡር አቶ ሳሙኤል ጋርሾ እንደገለጹት፣ የገበያ መሰረተ ልማት "ስብራትን" መጠገን የንግድ ትስስርን ማጠናከር በመንግስት የሀገር በቀል የኢኮኖሚ ማሻሻያ አጀንዳ ውስጥ ዋነኛው የትኩረት አቅጣጫ መሆኑን ገልፀዋል።
በምረቃው ሥነ-ሥርዓት ላይ የክልሉ ከፍተኛ የሥራ ኃላፊዎችና የህብረተሰብ ተወካዮች የተገኙ ሲሆን፣ ማዕከሉ ለደቡብ ኦሞ ዞን ኢኮኖሚያዊ ዕድገት አዲስ ምዕራፍ እንደሚከፍት ተገልጿል።