08/12/2023
ዜ ና ፍ ት ህ
በሙስና ወንጀል ተጠርጥረው የተከሰሱ 4 ግለሰቦች በሕግ ተቀጡ፡፡
👉1ኛ ተከሳሽ አቶ መለሰ መስቀለ የተባለው በኦሞ ማይክሮ ፋይናንስ ተቋም የምዕራብ አባያ ወረዳ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት የደንበኞች አገልግሎት ኦፊሰር ሆኖ በሚሠራበት ወቅት ያንቀሳቀሰው ሂሳብ በኦዲት ሲመረመር ከ30 ደንበኞች ቁጠባ ሂሳብ ላይ ደንበኞቹ ሳያውቁና ሳይፈቅዱ ብር 211,300.84 (ሁለት መቶ አሥራ አንድ ሺህ ሦስት መቶ ብር ከሰማኒያ አራት ሳንትም) ተቀናሽ በማድረግ ወንድሙ ወደሆነው 2ኛ ተከሳሽ አቶ መድን መስቀለ ሂሳብ ቁጥር በማዛወር እንዲሁም ከ2 ደንበኞች ሂሳብ ቁጥር ብር 34,000 (ሳላሳ አራት ሺህ ብር) ወደ ራሱ ሂሳብ ቁጥር ካዛወረ በኃላ መልሶ ወደ 2ኛ ተከሳሽ አካውንት ቁጥር በማዛወር፣2ኛ ተከሳሽም ከ1ኛ ተከሳሽ ጋር በመመሳጠር በራሱ አካውንት ያልቆጠበውንና የራሱ ያልሆነውን ገንዘብ በድምሩ ብር 245,300.84 (ሁለት መቶ አርባ አምስት ሺህ ሦስት መቶ ብር ከሰማኒያ አራት ሣንትም) ወጪ በማድረግ የማይገባ ጥቅም ማግኘታቸው በኦዲት የተረጋገጠ በመሆኑ፣
👉እንዲሁም 1ኛ ተከሳሽ ተቋሙ የአሠራር ለውጥ በማድረግ የደንበኞችን ሂሳብ ወደ ኮር ባንክንግ (ኦን ላይን ሲስተም) ማስገባቱን አጋጣሚ በመጠቀም ደንበኞች ገንዘብ ወጪ ለማድረግ ሲመጡ የወጪ ማዘዣ ሰነድ ራሱ በማዘጋጀት ደንበኞች ከሚፈልጉት ገንዘብ መጠን በላይ እየመዘገበ ወይም እየጻፈ በማስፈረም እና አስመስሎ በመፈረም ቁጥራቸው 166 በሆኑ ደንበኞች ሂሳብ ላይ በትርፍነት የገባ ብር 741,638 (ሰባት መቶ አርባ አንድ ሺህ ስድስት መቶ ሳላሳ ስምንት ብር) ወጪ በማድረግ በድምሩ 1ኛ ተከሳሽ ብር 986,938.84 (ዘጠኝ መቶ ሰማኒያ ስድስት ሺህ ዘጠኝ መቶ ሳላሣ ስምንት ብር ከሰማኒያ አራት ሳንትም) ለግል ጥቅሙ በማዋል በድርጅቱ ጥቅም ላይ ከፍተኛ ጉዳት በማድረሱ፣
👉2ኛ ተከሳሽም በዋና ወንጀል አድራጊነት ተካፋይ በመሆን ብር 245,300.84 (ሁለት መቶ አርባ አምስት ሺህ ሦስት መቶ ብር ከሰማኒያ አራት ሣንትም) ወጪ በማድረግ የተጠቀሙ በመሆናቸው 1ኛ እና 2ኛ ተከሳሾች በክስ አንድ የኢፌዲሪ የወ/ህ/ቁ 32 (1) (ሀ) ፣ 33 እና የሙስና ወንጀሎችን ለመደንገግ በወጣው አዋጅ ቁጥር 881/2007 በአንቀጽ 4 (1) እና 31 (2) በመተላለፍ በፈጸሙት ከባድ እምነት ማጉደል የሙስና ወንጀል፣
👉 3ኛ ተከሳሽ አቶ አድማሱ ጃጃርሶ የተባለው በቅርንጫፍ ጽ/ቤቱ የውስጥ ኦዲተር ሆኖ በሚሠራበት የገንዘብ ዝውውር ከደንበኞች ሂሳብ ቁጥር ወደ ሌላ ደንበኛ ሂሳብ ቁጥር የገንዘብ ዝውውር የሚፈጸመው የውስጥ ኦዲተር ሲያረጋግጥ ብቻ ሆኖ ሳለ 1ኛ ተከሳሽ ብር 245,300.84 (ሁለት መቶ አርባ አምስት ሺህ ሦስት መቶ ብር ከሰማኒያ አራት ሣንትም) ከደንበኞች አካውንት ደንበኞች ሳይፈቅዱና ሳያውቁ በሕገ ወጥ መንገድ ወደ ራሱ እና ወደ 2ኛ ተከሳሽ ሂሳብ ቁጥር ዝውውር ሲያደርግ ዝውውሩን በማረጋገጥና በቸልተኝነት በመፍቀድ፤
👉4ኛ ተከሳሽ አቶ ደበላ ደባልቄ የተባለውም የቅርንጫፍ ጽ/ቤቱ ሥራ አስኪያጅ ሆኖ በሚሠራበት ወቅት በኃላፊነቱ ከተቋሙ ደንበኞች ሂሳብ ቁጥር ወደ ሌላ ደንበኞች ሂሳብ ቁጥር የገንዘብ ዝውውር የሚፈጸመው ሥራ አስኪያጁ ሲያፀድቅ ብቻ ሲሆን 1ኛ ተከሳሽ ብር 245,300.84 (ሁለት መቶ አርባ አምስት ሺህ ሦስት መቶ ብር ከሰማኒያ አራት ሣንትም) ከደንበኞች አካውንት ደንበኞች ሳይፈቅዱና ሳያውቁ በሕገ ወጥ መንገድ ወደ ራሱ እና ወደ 2ኛ ተከሳሽ ሂሳብ ቁጥር ዝውውር ሲያደርግ ዝውውሩን በማፅደቅ በቸልተኝነት በመፍቀዱ ደንበኞች ገንዘብ ባልተገባ መንገድ እንዲመዘበር በማድረጋቸው 3ኛ እና 4ኛ ተከሳሾች በክስ 2 እና በክስ 3 የሙስና ወንጀሎችን ለመደንገግ የወጣውን አዋጅ ቁጥር 881/2007 በአንቀጽ 13 (7) ላይ የተመለከተውን በመተላለፍ በፈጸሙት የመንግስት ወይም የሕዝባዊ ድርጅት ሥራን በማያመች አኳኃን በመምራት የሙስና ወንጀል በጋሞ ዞን ፍትህ መምሪያ የሙስና ነክ ወንጀሎች ዐቃቤ ሕግ በኩል ክስ ቀርቦባቸው፣
👉 ግራ ቀኙን ሲያከራክር የቆየው የጋሞ ዞን ከፍተኛ ፍ/ቤት 2ኛ የወንጀል ችሎት ዐቃቤ ሕግ በተከሳሾች ላይ ያቀረበው ክስ በሰውና በሰነድ ማስረጃ በመረጋገጡ ተከሳሾችን በተከሰሱበት የሕግ ድንጋጌ ሥር ጥፋተኛ ናቸው በማለት ፍርድ በመስጠት፣
👉 ዛሬ 26/03/2016 ዓ.ም በዋለው የወንጀል ችሎት 1ኛ ተከሳሽን በ9 ዓመት ጽኑ እስራት እና በ15,000 ብር የገንዘብ መቀጮ እንድቀጣ፣
👉 2ኛ ተከሳሽን በ9 ዓመት ጽኑ እስራትና በ10,000 ብር የገንዘብ መቀጮ እንዲቀጣ፣
👉 3ኛ እና 4ኛ ተከሳሾች እያንዳንዳቸው በ3 ዓመት ቀላል እስራትና በ5,000 ብር የገንዘብ መቀጮ እንዲቀጡ ቅጣት ጥሎባቸዋል፡፡
አንድ የመንግሥት ወይም የሕዝባዊ ድርጅት ሠራተኛ የመንግስትን ወይም የሕዝባዊ ድርጅትን ሥራ በሚያከናውንበት ጊዜ ሕግንና የተዘረጉ የአሠራር ሥርዓትን ጠብቆ ተግባራትን መፈጸም የሚጠበቅ ሲሆን ተከሳሾች ይህንን የተጣለባቸውን ኃላፊነት ወደ ጎን በመተው የወንጀል ድርጊት የፈጸሙ በመሆናቸው እነሱን የሚያርም መሠሎችን የሚያስተምር ቅጣት አግኝተዋል፡፡
🙏ስለሆነም ይህ ቅጣት ሌሎች ከእንደዚህ ዓይነት መሰል የወንጀል ድርጊት ከመፈጸም እንዲቆጠቡ የሚያደርግና ሁሉም ዜጋ ህግን በማክበርና በማስከበር ረገድ የበኩሉን ሚና እንዲጫወት በዚህ አጋጣሚ መልዕክታችንን እናስተላልፋለን፡፡