02/06/2026
የደረቅ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ ሕግ በኢትዮጵያ!
#መግቢያ
በአገራችን ሕገ መንግሥት አንቀጽ 44(1) መሠረት ሁሉም ሰዎች ንጹህና ጤናማ በሆነ አካባቢ የመኖር መብት እንዳላቸው እንዲሁም በአንቀጽ 92 መንግሥት ሁሉም ኢትዮጵያዊ ንጹህና ጤናማ በሆነ አካባቢ እንዲኖረው ጥረት የማድረግ ኃላፊነት እንዳለበት በተጨማሪም መንግሥትም ሆነ ዜጎች አካባቢያቸውን የመንከባከብ ግዴታ እንዳለባቸው ተደንግጓል።
ሆኖም በኢትዮጵያ የሕዝብ ቁጥርና የከተሞች እድገትን ተከትሎ ባልተገባ መልኩ የሚጣሉ ደረቅ ቆሻሻዎች ማለትም እንደ ፕላስቲክ/ፌስታል/ ያሉት የውሃ መስመሮችን በመዝጋት፣ ለረጅም ጊዜ ሳይበሰብሱ በመከማቸት የአካባቢን ሥነ ምህዳር እየበከሉ ይገኛሉ፡፡ ስለሆነም ደረቅ ቆሻሻዎች የሚሰበሰቡበት፣ የሚጓጓዙበት፣ የሚከማቹበት፣ መልሰው ጥቅም ላይ የሚውሉበት እና የሚወገዱበትን ሂደት የሚገዛ የሕግ ሥርዓት የሚያስፈልግ በመሆኑ የአካባቢ ጥበቃ ሕጎች ተግባራዊ እየተደረጉ ይገኛሉ።
ከእነዚህም መካከል የደረቅ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ አዋጅ ቁጥር 1383/2017 በሥራ ላይ ውሏል። በዚህ ጽሑፍም በሕጉ የተካተቱ ዋና ዋና ጉዳዮችን አጭር እንመለከታለን።
✅ የደረቅ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ ምንነት፤
ደረቅ ቆሻሻን ማለት ማንኛውም ፈሳሽ ያልሆነ ወይም ነፋሽ /gas/ ያልሆነ ቆሻሻ እንደሆነ በአዋጁ አንቀጽ 2(1) ትርጓሜ የተሰጠው ሲሆን ይህም ፈሳሽ ወይም ጋዝ ነክ ከሆኑት ውጭ ያሉ ቆሻሻዎችን ለምሳሌ ፕላስቲክ፣ ጠርሙስ፣ ወረቀት፣ ካርቶን፣ ወዘተ ያካትታል። የደረቅ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ ማለት ይህንኑ ደረቅ ቆሻሻ ከምንጩ መቀነስ፣ በፈርጅ መለየትና መሰብሰብ፣ ማጓጓዝ፣ ማከም፣ መልሶ መጠቀም፣ መልሶ ዑደት ማድረግ እና አካባቢያዊ ተቀባይነት ባለው መልኩ ማስወገድን እንደሚያጠቃልል በአዋጁ አንቀጽ 2(2) ስር በግልጽ ሰፍሮ እናገኘዋለን።
ስለሆነም ደረቅ ቆሻሻን ከምንጩ እንዳይባዛ መከላከል፣ ከተባዛም በየፈርጁ ለይቶ እንዲሰበሰብ ማድረግና ወደሚፈለግበት ቦታ ማጓጓዝ እንዲሁም አስፈላጊው የማከም ሥራ ታክሎበት መልሶ ጥቅም ወይም ዑደት ላይ የሚውልበት ሂደት መሆኑን መረዳት ይቻላል።
✅ የአዋጁ የተፈጻሚነት ወሰን፤
የደረቅ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ አዋጅን ተፈጻሚነት ስንመለከት በአደገኛ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ አዋጅ ቁጥር 1090/2010 በተሸፈኑ አደገኛ ቆሻሻዎች እና ኤሌክትሪክና ኤሌክትሮኒክ ቆሻሻዎች በስተቀር በመላ አገሪቱ በደረቅ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ ላይ ተፈጻሚ መሆኑን በአዋጁ አንቀጽ 3 ስር ተደንግጎ እናገኘዋለን።
ይህ የሆነበት ምክንያትም ከላይ ለመግለጽ እንደተሞከረው የአደገኛ ቆሻሻዎችን አያያዝና አወገገድን በተመለከተ አዋጅ ቁጥር 1090/2010 ስለሸፈነው ድግግሞሽን ለማስቀረት እንዲሁም አላስፈላጊ የኃላፊነት መቀላቀልን ለማስወገድ ነው። ከዚህም በተጨማሪ የኤሌክትሪክና ኤሌክትሮኒክ ቆሻሻዎች የተለየ አደገኝነት ያላቸውና በኤሌክትሪክና ኤሌክትሮኒክ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ ደንብ ቁጥር 425/2010 ላይ ሽፋን ስላገኙ በዚህ አዋጅ እንዳይሸፈኑ ተደርገዋል።
✅ የደረቅ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ መርሆዎች፤
የደረቅ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ የሚከተሉትን መርሆዎች መከተል እንዳለበት በደረቅ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ አዋጁ አንቀጽ 4 ስር በግልጽ ተደንግጎ እናገኘዋለን። እነዚህም ፡-
➥ ቆሻሻን ከምንጩ መቀነስ /reduction of waste generation from its source/፣
➥ ቆሻሻን መልሶ መጠቀም /waste reuse፣
➥ ቆሻሻን መልሶ ዑደት ማድረግ /waste recycle/፣
➥ ቆሻሻን በአግባቡ ማስወገድ /waste disposal/፣
➥ የኅብረተሰብ ተሳትፎን ማሳደግ /public participation/፣
➥ የበከለን ማስከፈል /polluter pay/ የሚሉት ናቸው።
✅ የደረቅ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ ሂደቶች፤
የቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ የተለያዩ ሂደቶች ያሉት ሲሆን እነዚህም፡-
• ደረቅ ቆሻሻን መሰብሰብ /collection of solid waste/፡- ይህ ሂደት ከተለያዩ ቦታዎችና ምንጮች የመጣን ቆሻሻ በየፈርጁ የመለየትና በጊዜያዊነት ማከማቸትን ያካትታል። በአዋጁ አንቀጽ 6(3) ስር ማንኛውም ሰው ከመኖሪያ ቤቱ፣ ከአገልግሎት መስጫ ወይም ማምረቻ ተቋሙ የሚመነጭን ደረቅ ቆሻሻ በየፈርጁ የመለየት፣ አመቺ በሆነ ቦታ በጊዜያዊነት የማከማቸትና ፈቃድ ለተሰጣቸው ቆሻሻ ሰብሳቢዎች የማስተላለፍ ኃላፊነት ተጥሎበታል። ይህ እንዳለ ሆኖ ደረቅ ቆሻሻ ሰብሳቢዎች በማይኖሩበት አካባቢ የሚኖር ሰው ደረቅ ቆሻሻን ጊዜያዊ ማከማቻ ቦታ ድረስ የማድረስ ኃላፊነት ያለበት መሆኑ ሊዘነጋ አይገባም።
• ደረቅ ቆሻሻን መልሶ መጠቀም፣ መልሶ ዑደት ማድረግ እና ማስወገድ፡- እነዚህ ደረቅ ቆሻሻ ከተሰበሰበ በኋላ በድጋሜ ለአገልግሎት ማዋል፣ በጥሬ እቃነት ተጠቅሞ ለቀድሞ አገልግሎታቸው ወይም ለሌላ አገልግሎት ማዋልና ሙሉ በሙሉ ማስወገድን የሚመለከቱ ሂደቶች ናቸው፡፡ መልሶ መጠቀም /reuse/ ማለት ከደረቅ ቆሻሻ ውስጥ ጠቃሚ እቃዎችን በማውጣት ለተሰሩበት ዓላማ በድጋሚ ጥቅም ላይ የሚውሉበት አሰራር ስለመሆኑ እንዲሁም መልሶ ዑደት ማድረግ /recycle/ ማለት ደግሞ ከደረቅ ቆሻሻ ውስጥ ጠቃሚ ቁሶችን በመለየትና ወደ ጥሬ እቃ በመቀየር ለቀድሞ አገልግሎታቸው ወይም ለሌላ አገልግሎት ማዋል እንደሆነ በአዋጁ አንቀጽ 2(5) እና አንቀጽ 2(6) መረዳት ይቻላል። ደረቅ ቆሻሻን መልሶ መጠቀም፣ መልሶ ዑደት ማድረግ እና ማስወገድ ኢኮኖሚያዊ፣ አካባቢያዊ፣ የጤና እና ማህበራዊ ጠቀሜታ ባለው መንገድ እንዲሁም ለኅብረተሰቡ ፍላጎት ቅድሚያ በመስጠት መከናወን እንዳለበት በአዋጅ አንቀጽ 8 ስር ተደንግጎ እናገኛለን።
ሌላው ነጥብ ቆሻሻን ማስወገድ የሚቻለው ለዚህ ዓላማ ተብሎ ከተዘጋጀ ቦታ ብቻ እንደሆነ እንዲሁም ደረቅ ቆሻሻን በማቃጠል ማስወገድ እንደማይቻል በአዋጁ አንቀጽ 9 ስር ተደንግጎ እናገኛለን፡፡ ሆኖም ግን በሚመለከተው ከተማ አስተዳደር ፈቃድ መሠረት ፈቃድ ባገኘ የማቃጠያ መሳሪያ እና ለዚሁ ዓላማ በተፈቀደ ቦታ እና ሁኔታ ማስወገድ እንደሚቻልም በዚሁ ድንጋጌ ስር በልዩ ሁኔታነት ተቀምጦ እናገኘዋለን።
✅ የልዩ ልዩ ደረቅ ቆሻሻዎች አያያዝ እና አወጋገድን በተመለከተ የተጣሉ ኃላፊነቶች፤
አዋጁ ከአንቀጽ 10 እስከ 15 የልዩ ልዩ ቆሻሻዎች አያያዝ እና አወጋገድ በተመለከተ የተጣሉ ኃላፊነቶችን ደንግጓል፡፡ ይኸውም፡-
✅ የመኖሪያ፣ የአገልግሎት መስጫ ወይም የማምረቻ ተቋማት የደረቅ ቆሻሻ አያያዝ
በአዋጁ አንቀጽ 10 መሠረት ግለሰቦች፣ የአገልግሎት መስጫ ወይም የማምረቻ ተቋማት ያለባቸውን ኃላፊነት ደንግጓል፡፡ ይኸውም፦
➥ ማንኛውም ሰው ከመኖሪያ ቤት ይዞታው ድንበር አንስቶ እስከ 20/ሀያ ሜትር/ ባለው ርቀት ውስጥ ደረቅ ቆሻሻን የማጽዳት፣
➥ ማንኛውም የአገልግሎት መስጫ ወይም የንግድ ተቋም ከይዞታው ድንበር አንስቶ ቢያንስ እስከ 50/ሀምሳ ሜትር/ ባለው ርቀት ውስጥ ደረቅ ቆሻሻን የማጽዳት እንዲሁም በየቆሻሻ ፈርጁ ተለይተው ምልክት የተደረገባቸዉ የጉድፍ ማጠራቀሚያዎችን አመቺ በሆነ ቦታ የማስቀመጥ ኃላፊነት አለበት።
✅ የግንባታና የፍርስራሽ ደረቅ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ፤
ከዚህ ጋር በተያያዘ ተቋራጩ (ግንባታ የሚያካሂድ አካል) የግንባታ ፍርስራሽን ወይም ተቆፍሮ የወጣ አፈርን አካባቢያዊ ተቀባይነት ባለው መንገድ ማስወገድ የሚጠበቅበት ሲሆን የግንባታ ፈቃድ ከመሰጠቱ በፊት ይንን እንደሚያደርግ መረጋገጥ እንዳለበት በአዋጁ አንቀጽ 11 ስር ሰፍሯል።
➥ ጠርሙስ፣ ጣሳ፣ የታሸገ ውኃ መያዣ ፕላስቲክ፤
የከተማ አስተዳደሮች ቆሻሻ ጠርሙስ፣ የቆርቆሮ ጣሳ ወይም ፕላስቲክ መያዣ በጊዜያዊነት የሚከማችበት ቦታ መመደቡንና ክምችቱም በየወቅቱ መነሳቱን የማረጋገጥ ግዴታ የተጣለባቸው ስለመሆኑ የአዋጁ አንቀጽ 12 ያሳያል።
➥ ለአንድ ጊዜ ብቻ ጥቅም ላይ የሚውል ፕላስቲክ፤
አንድ ጊዜ ጥቅም ላይ የሚውል ፕላስቲክ ማለት መልሶ ጥቅም ላይ የማይውል ወይም መልሶ ዑደት የማይደረግ እና አንድ ጊዜ ብቻ ጥቅም ላይ ውሎ ቀጥታ የሚወገድ የፕላስቲክ ምርት ስለመሆኑ የአዋጁ አንቀጽ 2(11) ትርጉም ያሳያል።
ለአንድ ጊዜ ብቻ ጥቅም ላይ የሚውል ፕላስቲክ ማምረት፣ ለገበያ ማቅረብ፣ ወደ አገር ውስጥ ማስገባት፣ መሸጥ፣ ማከማቸት ወይም መጠቀም በአዋጁ አንቀጽ 13 የተከለከለ ሲሆን በአዋጁ አንቀጽ 14 ስር ደግሞ በልዩ ሁኔታ ስለሚፈቀድበት ሁኔታ ያስቀምጣል። የክልከላው የተፈጻሚነት ጊዜ ስንመለከትም ለአንደ ጊዜ ብቻ ጥቅም ላይ የሚውል ፕላስቲክ/ፌስታል/ ክልከላ አዋጁ ከመውጣቱ በፊት የተመረተ፣ ወደ አገር ውስጥ የገባ ወይም ለመግባት ሂደት ላይ ያለን የማይመለከት ሲሆን ይህ ልዩ ሁኔታ የሚቆየውም ግን አዋጁ ሥራ ላይ ከዋለበት ጊዜ ጀምሮ ለስድስት ወር ብቻ ስለመሆኑ በአዋጁ አንቀጽ 13 ሥር ተደንግጎ እናገኘዋለን።
➥ ጉድፍ እና የጉድፍ ማጠራቀሚያ አያያዝና አጠቃቀም፤
ሁለም የከተማ አስተዳደሮች የጉድፍ ማጠራቀሚያ ዕቃዎችን በተገቢ ቦታዎች ላይ የማስቀመጥ እና የጉድፍ ማጠራቀሚያ ወይም በገንዳ የተጠራቀመ ቆሻሻን በተቀመጠለት ጊዜ የማንሳት ኃላፊነት የተጣለባቸው ሲሆን ማንኛውም ሰው የጉድፍ ቆሻሻዎችን በጉድፍ ማጠራቀሚያ ውስጥ የመጣል ግዴታ እንዳለበት በአዋጁ አንቀጽ 15 ሥር ተደንግጓል።
ከዚሁ ጋር በተያያዘ ምንነቱን ስንመለከት ጉድፍ /litter/ ማለት ደረቅ ቆሻሻ ሆኖ በሰዎች የሚመነጩ የሲጋራ ቁርጥራጭ፣ የሶፍት ወረቀት፣ የትራንስፖርት ደረሰኝ፣ የተንቀሳቃሽ ስልክ ካርድ፣ የፈጣን ምግቦች መጠቅለያ ወይም የመሳሰሉትን እንደሚያጠቃልል የአዋጁ አንቀጽ 2(4) ትርጓሜ ያሳያል።
✅ ጥሰቶች የሚያስከትሉት ተጠያቂነት፤
➥ አስተዳደራዊ እርምጃዎች፦
የአዋጁ አንቀጽ 24 አስተዳደራዊ ቅጣቶችን በሚመለከት የደነገገ ሲሆን የእርምጃው ዝርዝር ይዘት የፌዴራል አካባቢ ጥበቃ ባለሥልጣን (ለአዲስ አበባና ድሬዳዋ ከተማ አስተዳደሮች ተፈጻሚ የሚሆን) ወይም የክልል አካባቢ ጥበቃ መስሪያ ቤት (በክልል ደረጃ ተፈጻሚ የሚሆን) በሚያወጣው መመሪያ እንደሚወሰን በድንጋጌው ተመልክቷል፡፡
➥ የወንጀል ተጠያቂነት፦
በአዋጁ አንቀጽ 25 ስር እንደተመላከተው ማንኛውም ሰው የፕላስቲክ ከረጢት /plastic bag/ ወይም በተለምዶ አጠራሩ ፌስታል ከተጠቀመ ወይም ለመጠቀም ይዞ ከተገኘ ከብር 2,000 (ሁለት ሺ) በማያንስና ከብር 5,000 (አምስት ሺ) በማይበልጥ የገንዘብ መቀጮ ይቀጣል።
በሌላ በኩል ማንኛውም ሰው የፕላስቲክ ከረጢት/ፌስታል/ ካመረተ ወይም ወደ አገር ውስጥ ካስገባ፣ ለገበያ ካቀረበ ወይም ከሸጠ፣ ለንግድ ዓላማ ካከማቸ ወይም ይዞ ከተገኘ ከብር 50,000 (ሀምሳ ሺ) በማያንስና ከብር 200,000 (ሁለት መቶ ሺ) በማይበልጥ የገንዘብ መቀጮ እና ከ5 (አምስት) አመት በማይበልጥ ጽኑ እስራት ይቀጣል፡፡
ይኸውም የፕላስቲክ ከረጢት/ፌስታል/ ከግለሰባዊ አገልግሎት ውጪ ለንግድ ዓላማ ጥቅም ላይ ሲውል ከገንዘብ ቅጣት በተደራቢነት በእስራት እንደሚያስቀጣ መረዳት ይቻላል። ከላይ የተጠቀሱት ድርጊቶች የተፈፀሙት የሕግ ሰውነት በተሰጠው አካል ከሆነ ቅጣቱ ከላይ የተቀመጠውን የገንዘብ ቅጣት 3 (ሶስት) እጥፍ እንደሚሆንም በድንጋጌው ስር ተመላክቷል።
#ማጠቃለያ
የደረቅ ቆሻሻ አያያዝና አወጋገድ አዋጅ በኢትዮጵያ ከተሞች ውስጥ ዘላቂና አካባቢን የሚጠብቅ የቆሻሻ አያያዝ ሥርዓት ለመፍጠር ወሳኝ ሕጋዊ ማዕቀፍ ነው። ይህን አዋጁ በተገቢው ሁኔታ ለማስፈጸም በዋናነት የከተማ አስተዳደሮችን የማስፈጸም አቅምን ማሳደግ፣ የሕዝብ ግንዛቤን ማሳደግ እና ሁሉንም ባለድርሻ አካላት ማሳተፍ ይጠይቃል። ኅብረተሰቡም ለአካባቢ ጽዳት ዋና ተዋናይ በመሆን ለጤናማ አካባቢ መፈጠር የበኩሉን አስተዋጽኦ ሊወጣ ይገባል።
👉 በፍትህ ሚኒስቴር በንቃተ ሕግ ትምህርትና ሥልጠና ዳይሬክቶሬት የተዘጋጀ!!!