06/05/2026
የለውጥ ፍሬዎች በሀላባ ዞን አደጋ ስጋት ስራ አመራር ጽ/ቤት ፦ ከተረጂነት ወደ ምርታማነት!
የሀላባ ዞን አደጋ ስጋት ስራ አመራር ጽሕፈት ቤት ባለፉት የለውጥ ዓመታት የአሰራርና የአመለካከት ለውጥ በማምጣት ማህበረሰባችንን ከእጅ ወደ አፍ ህይወትና ከተረጂነት ስነ-ልቦና በማውጣት ወደ ምርታማነት የሚያሸጋግሩ ተስፋ ሰጪ ስራዎችን ሲያከናውን ቆይቷል፡፡ ጽሕፈት ቤታችን ባለፉት የለዉጥ ዓመታት "አደጋን ወደ ጸጋ" በመቀየር ረገድ ያስመዘገባቸው ዋና ዋና ድሎች የሚከተሉት ናቸው፦
የአመለካከት ለውጥና ከተረጂነት መውጣት፦ ባለፈው የለውጥ ዓመት አርሶ አደሩ የነበረበትን "ተረጂነት" አመለካከት በመቀየር ያለውን የተፈጥሮ ጸጋ ተጠቅሞ ወደ "ምርታማነት" እንዲሸጋገር ተደርጓል፡፡ እስከ ዛሬ ተረጂ ሆኖ መቆየቱ "ቁጭት" ውስጥ የከተተው አርሶ አደራችን ፣ ዛሬ በራሱ ጥረት ምርታማ ለመሆን እየሰራ ይገኛል፡፡
አደጋን ወደ ጸጋ መቀየር፦ ከዚህ ቀደም አደጋ ሲደርስ ምላሽ መስጠት ላይ ብቻ ያተኮረውን አሰራር በመቀየር አደጋ ከመድረሱ በፊት በመከላከልና በመቀነስ ስራዎች ላይ ትኩረት ተሰጥቷል፡፡ ለጎርፍ አደጋ ተጋላጭ የነበሩ እንደ ሲንቢጣ ፣ በንዶ ፤ ጮባሬ ሜዕኖ እና ኡዳና ሜዕኖ ያሉ አካባቢዎች የጎርፍ አደጋን ወደ ጸጋ በመቀየር ከ20 ዓመት በላይ የቆየውን ተረጂነት መስበር ችለዋል፡፡
የራስን አቅም መገንባትና የሰብዓዊ ድጋፍ ክምችት፦ ባለፉት የለዉጥ ዓመት የሰብዓዊ ድጋፍን ከፌዴራልና ከክልል ከመጠበቅ ወጥተን በዞኑ መንግስት በውል መሬቶች ላይ በማምረትና የማህበረሰቡን የመረዳዳት ባህል በመጠቀም ባለፉት 2 ዓመታት ብቻ ከ11,000 ኩንታል በላይ እህል በማከማቸት በራስ አቅም ምላሽ የመስጠት አቅም ተፈጥሯል፡፡
የምግብ ዋስትናን ማረጋገጥና ከሴፍትኔት መመረቅ፦
በተደረገላቸው የቤተሰብ ኑሮ ማሻሻያ ድጋፍና በተለያዩ የግብርና ኢንሼቲቮች አማካኝነት 6,376 አባወራዎች (26,051 የቤተሰብ አባላት) ከሴፍትኔት ፕሮግራም መመረቅ ችለዋል፡፡
የሰብዓዊ ድጋፍ ይደረግላቸው ከነበሩ 49,132 ቤተሰቦች መካከል 39,079 የሚሆኑት ከተረጂነት ወደ ምርታማነት ተቀይረዋል፡፡
በቤተሰብ ኑሮ ማሻሻያ ፕሮግራም ለ4,481 አባወራዎች በ149.2 ሚሊዮን ብር በላይ ድጋፍ ተደርጓል፡፡ በዚህም ለድለባ ፣ ለማሞከትና ለወተት እርባታ 7,078 እንስሳት ቀርበው የቤተሰብ ገቢ ማሻሻል ተችሏል፡፡
በቁጠባ ሀብት ማፍራት፦ ባለፉት 2 ዓመት የሴፍቲኔት ተጠቃሚዎች በቋሚነት እንዲቆጥቡ በማድረግና የቁጠባ ባህላቸውን በማሳደግ ለቤተሰብ ኑሮ ማሻሻያ የሚሆን መነሻ 125,000,000 ብር ካፒታል በመቆጠብ በመረጡት የስራ መስክ በመሰማራት "የቤተሰብ ጥሪት" እንዲያፈሩ ተደርጓል፡፡ ይህ ቁጠባ ተጠቃሚዎች ከእርዳታ ጥገኛነት እንዲላቀቁ ትልቅ አቅም ሆኗቸዋል፡፡
የቴክኖሎጂና የውሃ አማራጮች አጠቃቀም፦በዌራ ዲጆ ወረዳ 190 አባወራዎች በ7.6 ሚሊዮን ብር የገንዘብ ድጋፍ የሶላርና የዴዝል ፓምፖችን እንዲያገኙ ተደርጎ በ41.5 ሄክታር መሬት ላይ የጓሮ አትክልትና የበልግ ሰብሎችን በማልማት ኑሮአቸውን ማሻሻል ችለዋል፡፡
ጽሕፈት ቤታችን ይህንኑ ስኬት አጠናክሮ በመቀጠል አደጋዎችን መቋቋም የሚችልና የምግብ ዋስትናው የተረጋገጠ ማህበረሰብ ለመፍጠር በቁርጠኝነት ይሰራል፡፡
"አደጋን በመከላከል ምርታማነትን እናረጋግጣለን!"
#ኢትዮጵያ