02/06/2026
የ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ያለምንም የፀጥታ ችግር መጠናቀቁን የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ሰላም እና ፀጥታ ቢሮ ገለጸ
ሆሳዕና 25/09/2018 (ሀድያ ቴሌቪዥን)
የ7ኛው ጠቅላላ ምርጫ ያለምንም የፀጥታ ችግር መጠናቀቁን የማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ሰላም እና ፀጥታ ቢሮ ኃላፊ አቶ ተመስገን ካሳ ገለጹ።
ምርጫው መጠናቀቁን ተከትሎም ቢሮው መግለጫ ሰጥቷል።
ግንቦት 24 ቀን 2018 ዓ.ም ዜጎች በሀገረ-መንግስት ግንባታ ላይ ያላቸውን የላቀ ተሳትፎ ያሳዩበት ዕለት መሆኑን የጠቀሱት አቶ ተመስገን ካሳ፤ በማዕከላዊ ኢትዮጵያ ክልል ከማለዳው 12:00 ሰዓት ጀምሮ የተካሄደው ድምፅ የመስጠት ሂደት ያለምንም የፀጥታ ችግር በሰላም መጠናቀቁን አስታውቀዋል።
ከምርጫው አስቀድሞ በክልሉ በሚገኙ ሁሉም አካባቢዎች የምርጫ ሂደቱ የተረጋጋ እና ሰላማዊ እንዲሆን የሚያስችሉ የቅድመ ዝግጅት ሥራዎች ሲከናወኑ መቆየታቸውን ኃላፊው በመግለጫቸው አንስተዋል።
በተመሳሳይ ሁኔታ ከምርጫ በኋላ (በድህረ-ምርጫ) ሊኖሩ ስለሚገባቸው የፀጥታ ሥራዎች ጭምር ዝግጅት ሲደረግ እንደነበር ገልጸዋል።
በምርጫው ወቅት ሊደረጉ ስለሚገቡ ጥንቃቄዎች ኅብረተሰቡን ከማስተማር ጀምሮ፣ በየአካባቢው ሰላምን ለማስከበር የተመደቡ የፀጥታ አካላት በአጠቃላይ ሂደቱ ላይ ምን ዓይነት ሚና ሊኖራቸው እንደሚገባ የሚያስገነዝብ ሥልጠና መሰጠቱንም አቶ ተመስገን ጠቁመዋል።
ግንቦት 24 ቀን በተደረገው የድምፅ አሰጣጥ ሂደት በክልሉ ሥር ባሉ የምርጫ ክልሎችና ጣቢያዎች የነበረው አጠቃላይ እንቅስቃሴ ሰላማዊና የኅብረተሰቡ ጉልህ ተሳትፎ የታየበት እንደነበር ተገልጿል።
በምሽቱ መርሃ ግብር የተከናወነው የድምፅ ቆጠራ ሂደትም ፍፁም ሰላማዊ እንደነበር የገለጹት ኃላፊው፤ በክልሉ በሚገኙ አንዳንድ የምርጫ ጣቢያዎች ግን እስከ ምሽቱ 4:00 ሰዓት ድረስ የድምፅ አሰጣጥ ሂደቱ ቀጥሎ እንደነበር አስረድተዋል።
በድምፅ አሰጣጥ ሂደት ወቅት የታየው የኅብረተሰቡ ከፍተኛ እገዛና ተሳትፎ፣ በቀጣይም የምርጫ ውጤት በሚገለጽበት ወቅት ተጠናክሮ ሊቀጥል ይገባል ብለዋል።
ኃላፊው በመጨረሻም፣ በቅድመ-ምርጫና በምርጫው ዕለት አጠቃላይ ሂደቱ በሰላማዊ መንገድ እንዲጠናቀቅ የበኩላቸውን አስተዋጽኦ ላበረከቱና ከተቋሙ ጋር ለተባበሩ አካላት በሙሉ ምስጋናቸውን አቅርበዋል።