06/06/2026
በወራቤ ከተማ የጃክ ፍሩት ተከላ ንቅናቄ በይፋ ተጀመረ!
የምግብ ዋስትናን ለማረጋገጥ እና የአረንጓዴ ልማትን ለማፋጠን ታላቅ ተስፋ የተጣለበት እንዲሁም አዲስ እንሼቲቭ የሆነዉና የፍራፍሬ ንጉስ በመባል የሚታወቀዉ ጃክ ፍሩት(jackfruit) ተከላ ንቅናቄ በወራቤ ከተማ በይፋ ተጀምሯል።
ይህ የልማት እርምጃ በከተማዋ የፍራፍሬ ምርትን ለማሳደግና በየጓሮው አዳዲስ የገቢ ምንጮችን ለመፍጠር ያለመ ነው።
የወራቤ ከተማ አስተዳደር ከንቲባ አቶ ያሲን ከሊል በዚህ ወቅት እንዳሉት ከፍተኛ ምርት በመስጠት ዘርፈ ብዙ እኮኖሚያዊ ጠቀሜታ የሚሰጥ መሆኑን በመጥቀስ በዞናችን እየተስፋፋ የሚገኝ አዲስ የፍራፍሬ አይነት መሆኑን ተናግረዋል።
በመንገድና በሌሎችም መሰረት ልማቶች ምክንያት በማይነሳበት አግባብ መትከል እና በቋሚነት መጠበቅ እንደሚገባም አቶ ያሲን ከሊል አመላክተዋል።
በከተማው ዙሪያ የሚገኙ አርሶአደሮች ይህንን ጠቃሚ የልማት ተግባር በመቀበል በየጓሮአቸው የጃክ ፍሩት ችግኞችን እንዲተክሉና ተገቢዉን እንክብካቤ እንዲያደርጉ ከንቲባው መልዕክት አስተላልፈዋል።
በዕለቱም በአቶ ሪድዋን ኣደም ጥምር ግብርና ማሳ ላይ የሙዝና የመኖ ተከላ ተከናውኗል።
በአረንጓዴ ልማት ላይ አዲስ አሻራ ለማሳረፍ የተጀመረው ይህ ንቅናቄ፤ በከተማዋ በሚገኙ የመንግስት ተቋማት፣ በትምህርት ቤቶች፣በከተማው በሚገኙ ክፍት ቦታዎች እና በአርሶአደሮች ጓሮ ላይ በስፋት ይተገበራል ተብሏል።
አካባቢን ከአየር ንብረት መዛባት ከመጠበቅ ባለፈ በከተማ ግብርና የነዋሪዎችን የምግብ ዋስትና ለማረጋገጥ እምቅ አቅም እንደሚሆን ተመላክቷል።
የወራቤ ከተማ አስተዳደር የመንግሥት ዋና ተጠሪ አቶ ናስር ቡሽራ፣የከተማዉ ብልጽግና ፓርቲ የፖለቲካና አቅም ግንባታ ዘርፍ ሃላፊ አቶ ነስሬ አማን፣የወራቤ ከተማ አስተዳደር ግብርና ጽ/ቤት ሃላፊ አቶ ጃፈር ጃቢር ፣የከተማዉ ግብርና ጽ/ቤት ምክትል ሃላፊ ወ/ሮ ስመኝ ገዛኸኝ፣የግብርና ባለሙያዎች እና ሌሎችም በተከላ መርሃ-ግብሩ ላይ ተገኝተዋል።
~~~~~~~~~~~~~~~~~~~~
ግንቦት 29፣2018[ወራቤ ኮሙኒኬሽን]