14/03/2026
የተሰባጠረ የአመጋገብ ስርዓት ጤናማና አምራች ዜጋን ለማፍራት!
(አዲስ አበባ፣ መጋቢት 4 ቀን 2018 ዓ.ም፣ ግብርና ሚኒስቴር)
ግብርና ሚኒስቴር ከአለም ምግብና እርሻ ድርጅት (FAO) ጋር በመተባበር ከሚኒስቴር መስሪያ ቤቱ ከተለያዩ የስራ ክፍሎች ለተውጣጡ ባለሙዎች እና ለግብርና ሚኒስቴርና ተጠሪ ተቋማት የሸማቾች ኃላፊነቱ የተወሰነ የህብረት ስራ ማህበር ባለሙያዎች የኢትዮጵያ ምግብን መሰረት ያደረገ የአመጋገብ መመሪያ ላይ የአቅም ግንባታ ስልጠና ለአራት ተከታታይ ቀናት ሲሰጥ ቆይቷል፡፡
ስልጠናው በንድፈ-ሃሳብና በተግባር የታገዘ ሲሆን የኢትዮጵያ ምግብን መሰረት ያደረገ የአመጋገብ መመሪያ አተገባበር፣ ስርዓተ-ምግብ ተኮር ግብርናን መሰረት ያደረገ የምግብ አዘገጃጀት እንዲሁም የምግብ ደህንነትና ጥራት አጠባበቅ ላይ ያተኮረ ነው፡፡
አንድ ሰው በቀን ውስጥ ስድስቱን የምግብ ምድቦች ማለትም ብዕርና አገዳ/መደበኛ፣ ጥራጥሬ፣ የቅባት እህሎች፣ አትክልትና ፍራፍሬ፣ የእንስሳት ተዋፅዖ እና ቅባት/ዘይት እንዲሁም በአንድ ገበታ ደግሞ አራት የምግብ ምድቦችን አካቶ መመገብ እንዳለበት በስልጠናው ተገልጿል፡፡
የተሰባጠረ የአመጋገብ ስርዓት ጤናማ እና አምራች ዜጋን ለማፍራት ሚናው የጎላ መሆኑንም በመድረኩ ተመላክቷል፡፡