04/07/2026
፦
*****************************************************
የመላው ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት (መኢአድ) ላለፉት 35 ዓመታት ሰላማዊ ትግሉን በፅናት ሲያስቀጥል ከሚታገልላቸው ፖሊሲዎች መካከል ፌደራሊዝም አወቃቀሩና የሥርዓተ መንግሥት አወቃቀሩ ከብዙ በጥቂቱ ይጠቀሳሉ።
ለምሳሌ፥ ኢትዮጵያ ሕዳር 1987 ዓ.ም የመንግስት ሰነድ ሆኖ የፀደቀው ባለ ሰማያዊ ቀለም ሕገ-መንግስት ተብዬው ገና ከፅንሰቱ 1968 ምናምን አካባቢ ከደደቢት የአንድ ድርጅት የመታገያ ፕሮግራም ሆኖ በህወሓት የተቀረፀ ፕሮግራምና መተዳደሪያ ደንብ እንደነበርና በታሪክ አጋጣሚ ድንገት ሳያስቡት ኢትዮጵያን የምታክል ግዙፍ ሀገር እጃቸው ላይ በ1983 ዓ.ም ስትወድቅባቸው "ከመጣሽ ማርያም ታምጣሽ" ብለው ተቀበሏትና በዞባና በወረዳ የማስተዳደር እሳቤ ቀጥለው አገዛዛቸውን ሲያፀኑ እንደወግ የማስተዳደሪያ ሰነድ ያስፈልጋልና ያንኑ የጫካ ሰነዳቸውን የተወሰኑ የዓለምአቀፍ ድንጋጌዎችን ጨማመሩበትና የሀገር መምሪያ ሰነድ አድርገውት ሀገርን ያተራምሱበት ያዙ። ሰነዱም ቋንቋ ተኮር ፌዴራሊዝም አድርገውት ላለፉት 40 የተጠጉ ዓመታትን እየተተራመስንበት እንገኛለን። መኢአድ ታዲያ ሀገር በተለይ እንደ ኢትዮጵያ ያሉ በብዙ ቋንቋና ባህል ስብጥሮሽ የበለፀጉ እና በቆዳ ስፋቱና በመልካ ምድራዊ አቀማመጥ የሰፉ ሀገራት ለአስተዳደር አመቺነቱ የፌዴራሊዝም አወቃቀር ተመራጭ ነው ብለን እናምናለን። ስለሆነም ላለፉት 35 ዓመታት የጂኦግራፊ (መልካ ምድራዊ አቀማመጥ) እና የባሕልና ኢኮኖሚ ትሥሥርን መሠረት ያደረገ የፌዴራሊዝም አወቃቀርን መሠረት አድርገን እየታገልን ብዙ ዋጋ ከፍለንበታል። በዚሁ መሠረትም የፓርቲያችን የአመራር መዋቅር እንኳን በ5ቱ የፌዴራሊዝም አወቃቀራችንን ለመምራት በሚያመቸን ሁኔታ፦
1. ሰሜን ኢትዮጵያ ቀጠና
2. ደቡብ ኢትዮጵያ ቀጠና
3. ምሥራቅ ኢትዮጵያ ቀጠና
4. ምዕራብ ኢትዮጵያ ቀጠና እና
5. ማዕከላዊ ኢትዮጵያ ቀጠና በሚል አወቃቀር እያንዳንዱ የቀጠና ኃላፊም በም/ፕሬዚደንት ማዕረግ የማዕከላዊ ሥራ አስፈፃሚ አባል በመሆን አሁን ያለው አወቃቀር እስኪቀየር ድረስ ያለፉት 9 መደበኛ ጉባዔያት ይሄንንኑ መዋቅር አስቀጥለው ነበር። "ነበር" የምልበት ምክንያት አሁን ያለው አመራር የተመረጠው በ10ኛው መደበኛ ጉባዔ የተመረጠ ሲሆን መዋቅሩም በምርጫ ቦርድ አስገዳጅ መመሪያ "የቀጠና መዋቅርን ተቀብዬ ለጉባዔው እውቅና ሰጥቼ ጉባዔውን አላፀድቅም" ስላለን የማዕከላዊ ኮሚቴ/ሥራ አስፈፃሚ/ መዋቅራችንንም ቁጥሩን ከ21 ወደ 13 እንድናወርደው ተገድደናል። ይሄ ሊሆን የቻለበት ብዬ በግሌ የምጠረጥረው እንዲሁ ከሰዎች ጋር ሳወራም ወደ እርገጠኛነት ያደረሰኝ ምርጫ ቦርድ አጀንዳችንን የማስነጠቅ ሴራ እንዳሴረብን እጠረጥራለሁ ጉባኤ ባደረግንበት አካባቢ የሀገራዊ ምክክር ኮሚሽን ተቋቁሞ አጀንዳ ፍለጋ በየመንግስት ተቋማቱ የሚያንጎዳጉድበት ወቅት ስለነበር በሰዓቱ ብልፅግና በመከላከያ ተቋም አማካኝነት የኛን የ5 ቀጠና አወቃቀር አጀንዳ አስይዟል የሚል ወሬ በከፍተኛ ደረጃ የሚናፈስወት ጊዜ ነበር። በዚህ ምክንያት የተቀማን ይመስለኛል።
ፕሮግራም ቀርፀን የምንታገልባቸው አጀንዳዎች መካከል፤
1. የፌዴራሊዝም አወቃቀር ጂዮግራፊካል/መልካምድራዊ/ አቀማመጥን መሠረት ያደረገና
2.መንግስታዊ አወቃቀራችን ደግሞ ፕሬዚዳንታዊ እንደሚሆን በ1995 ዓ.ም የታተመችው ባለ ብርቱካናማ ቀለም ሽፋን ያላት ቋሚ ፕሮግራማችን ላይ በግልፅ ተቀምጧል። ይህ ብቻ አይደለም ሌሎችም ብዙ ብልፅግና የሰረቃቸው አጀንዳዎችን አጭቃ ይዛለች ሌላ ጊዜ እመለስበታለሁ።
ወደ ቀደመ ነገሬ ስመለስ ምንም እንኳን ፕሮግራማችን አሸናፊ መሆኑ ደስ ቢያሰኘኝም ሁሉም ነገር ያለ ጊዜው ፣ ያለቦታውና ያለባለቤቱ ሲሆን ትክክል አይመጣም። ፕሮግራሙን እንዴትና በማን ተግባራዊ ልናደርገው እየታሰበ እንደሆነ ታሳቢ መሆን ይገባዋል። ለምሳሌ ማን ነበር የሆነን ሰው "ክትፎ በፖፖ" በሚል አገላለፅ የገለፀው?(የግለሰቦቹን ስም መጥቀስ ስለሌለብኝ ነው) እንደ ግለሰቡ አገላለፅ ክትፎ ተወዳጅ ምግቡ ነው። ነገር ግን የቀረበለት አቀራረብ ክትፎነቱን አስቀይሮ ቆሻሻ አድርጎታል። እንደ ግለሰቡ አገላለፅ ክትፎ ክትፎ የሚሆነው በጣባ ሲቀርብ ነው። እናም ዛሬ ላይ የተያዘው አጀንዳ ወቅቱ እና አስፈፃሚ አካላቱና ተመካካሪዎቹስ እነማን ናቸው? እውነቱን እንነጋገር ከተባለስ እውን ይሄንን አጀንዳ ብልፅግና ከልብ በራሱ ተነሳሽነት ይሁነኝ ብሎ አቀረበው ወይ? ከሆነስ የዛሬ 7 ዓመት አካባቢ ወደስልጣን በመጣ ማግስት የጫጉላ ሽርሽር ላይ እያለ ገና ያኔ ስሙን ከኢህአዴግ ወደ ብልፅግና የቀየረበት የስም ማውጫ ዳቦ ሳይቆረስ ከብረውት የነበሩ ስለ ሕዝቤ ያገባኛል ሕዝቤ ጠይቆ ሳይመለስ የሚቀር ምንም አይነት ጥያቄ አይኖርም ብለው ለህዝባቸው ቃል ቢገቡ ከብልፅግናው ቁንጮ መሪ ለአንድ ክልል ተብሎ የሚነካካ ህገመንግስት የለም ብለው ጥያቄውን የቁጣ ምላሽ ለምን ሰጡት? ግዴለም ነገርዮውን ከጀርባ በኩል እንመርምረው? እኔ በግሌ ፓርቲዬም ነሚያምንበት አጀንዳዎቹ አንዳንድ ቦታዎች ላይ ጠመም አድርገው ተረድተዋቸው አጣምመው በአጀንዳነው ቢያቀርቡትም አጀንዳችን አሸናፊ ሆኖ መምጣቱ ያን ሁሉ መሰዋዕትነት ለከፈልንለት ለሕዝብ ይጠቅማል ብለን ለማስፈፀም ስለሆነ አሸናፊነቱ ደስታን ይሰጠናል። ነገር ግን አጀንዳው አጀንዳችን ስለሆነ ብቻ ያለጊዜውና ያለቦታው እንዲሁም አስፈላጊነቱን በቅጡ ባልተረዱ አካላት ለመፍታት መውተርተር የመፍትሄ ውሉን አጥፍቶት እንዳያውሰበስበው ከፍተኛ ስጋት አለኝ (አለንም) ስንዴና አረምን መለየት ግዴታ እንደሆነ ቢታወቅም ስንዴና አረሙን የምንለየው ግን ስንዴውን ነቅለን አረሙን በመተው አይደለም ስንዴውን ተንከባክበን አረሙን በመንቀል እንጂ። እናም የተሰረቀ አጀንዳ ልክ እንደ አጀንዳ ፈጣሪው በትክክል ተረድቶት ሰራቂው ለሌላ ወገን በሚገባ ሊገልፀው ስለማይችል አጀንዳውን ለአጀንደ ፈጣሪው በአክብሮት መልሱለትና በተመቻቸ ጠረጴዛ ላይ ቀርቦ አግባብነት ባለው ተወያይና ውይይት ለውጤት እናብቃው እላለሁ።
በቀሪና ከፕሮግራማችን ላይ በተሰረቁ አጀንዳዎች እመለሳለሁ።
ቸር ይግጠመን!!