07/08/2015
አዳዲስ የውጭ ኩባንያዎች በአበባ ልማት ተሰማርተዋል Featured
07 Aug 2015
ኢኮኖሚ
አዲስ አበባ ነሐሴ 1/2007 በኢትዮጵያ በቅርቡ ሶስት አዳዲስ የውጭ ኩባንያዎች በአበባ ልማት ተሰማርተዋል፡፡
የኢትዮጵያ ሆርቲካልቸር ልማት ኤጀንሲ ከአዲሶቹ አበባ አልሚዎች አንዱ የኔዘርላንድ ሁለቱ ደግሞ የህንድ ኩባንያዎች መሆናቸውን ገልጿል።
የኤጀንሲው የህዝብ ግንኙነት ማስተባበሪያ ኃላፊ አቶ መኮንን ኃይሉ ኩባንያዎቹ በአማራ ክልል 190 ሄክታር መሬት ተረክበው ማልማት መጀመራቸውን ተናግረዋል።
የኩባንያዎቹ ስራ መጀመር አገሪቱ ወደ ውጭ የምትልከውን አበባ በብዛትና በጥራት በማቅረብ ከዘርፉ የምታገኘውን የውጭ ምንዛሪ ያሳድገዋል።
በክልሉ የሆርቲካልቸር ልማት ከመስፋቱ ጎን ለጎን የባህርዳር ኤርፖርት የካርጎ አገልግሎት ለመስጠት የማቀዝቀዣ መጋዘኖችና ሌሎች አገልግሎቶችን በማሟላት የኤክስፖርት ሂደቱን ይበልጥ ለማቀላጠፍ የጎላ አስተዋጽኦ ይኖረዋል ብለዋል።
መንግሥት ለዘርፉ በሰጠው ትኩረት፣ ለባለኃብቶች በሚያደርገው ድጋፍና በሃገሪቱ ባለው ምቹ የኢንቨስትመንት ሁኔታ በመሳብ በርካታ የውጭ ኩባንያዎች በዘርፉ ለመስራት ፍላጎት አሳይተዋል ነው ያሉት።
በኤክስፖርት ልማት ዘርፍ የሚሰማሩ የውጭ ኩባንያዎች መበራከት ከሆርቲካልቸር ኤክስፖርት የሚገኘውን የውጭ ምንዛሬ ከማሳደግ ባሻገር በሥራ ዕድል ፈጠራና በቴክኖሎጂ ሽግግር አስተዋፅኦ እያደረገ ነው።
አገሪቱ በተጠናቀቀው በጀት ዓመት በ11 ወራት ከሆርቲካልቸር ኤክስፖርት ኢንዱስትሪ 226 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር ገቢ ያገኘች ሲሆን ከዚሁ ውስጥ 184 ሚሊዮን ዶላር የተገኘው ከአበባ ዘርፍ ነው።
ኢትዮጵያ በሆርቲካልቸር ኤክስፖርት ልማት ከፍተኛ እምቅ ኃብት ካላቸው አገራት መካከል የመጀመሪያ ደረጃ ላይ ትገኛለች።
በአሁኑ ወቅት በአገሪቱ 140 የአገር ውስጥና የውጭ ኩባንያዎች ምርቶቻቸውን ለዓለም ገበያ እንደሚያቀርቡ ከኤጀንሲው የተገኘ መረጃ ያመላክታል።