07/09/2026
የፅናት ቀን የፀጥታና ደህንነት ተቋማት ለሀገር ሰላምና ልማት እያበረከቱ ያሉትን አስተዋጽኦ የሚያሳይ ነው።
ምክትል ኮሚሽነር መላኩ ፋንታ
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት ጳጉሜ 02 ቀን 2018 ዓ.ም
የፅናት ቀን የፀጥታና ደህንነት ተቋማት ለሀገር ሰላም፣ ደህንነትና ልማት እያበረከቱ ያሉትን አስተዋጽኦ ለመላው ሕዝብ ለማስተዋወቅ የሚያስችል አጋጣሚ መሆኑን የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ ምክትል ኮሚሽነር መላኩ ፋንታ ገለጹ።
ምክትል ኮሚሽነሩ የፅናት ቀንን አስመልክቶ በሰጡት ጋዜጣዊ መግለጫ፣ ዝግጅቱ የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት፣ የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ፣ የብሔራዊ መረጃና ደህንነት አስተዳደር፣ የአርቴፊሻል ኢንተለጀንስ አስተዳደር እና የኢንፎርሜሽን መረብ ደህንነት አስተዳደር በጋራ የሚያዘጋጁት መሆኑን ጠቁመዋል።
ሀገራችን በጀመረችው የማንሰራራት ጉዞ የዕድገትና የልማት ግቦችን ለማሳካት ሰላምና ደህንነት መሠረታዊ ጉዳይ በመሆኑ፣ የፀጥታ ተቋማት የሚወጡት ሚና ወሳኝ መሆኑን አስገንዝበዋል።
በዚህ ረገድ የኢትዮጵያ መከላከያ ሠራዊት በጠንካራ ሕዝባዊ መሠረት ላይ ተገንብቶ ከዘመኑ ጋር የዘመነ አቅም በመገንባት የሀገሪቱን ሉዓላዊነት፣ ብሄራዊ ጥቅምና አንድነት ለመጠበቅ የተሰጠውን ሀገራዊ ተልዕኮ እየተወጣ መሆኑን ገልጸዋል።
ሠራዊቱ የአየርና የየብስ ግዛትን በመጠበቅ፣ ሀገረ-መንግሥትንና ሕገ-መንግሥታዊ ሥርዓቱን ከሚያጋጥሙ ስጋቶች በመከላከል እንዲሁም በዓለም አቀፍ የሰላም ማስከበር ተልዕኮዎች በመሳተፍ የሀገሪቱን ስም እያስጠበቀ መሆኑንም አክለዋል።
የኢትዮጵያ ፌዴራል ፖሊስ በበኩሉ የሕግ የበላይነትንና ሰላምን በማስፈን፣ ዓለም አቀፍና ድንበር ተሻጋሪ ወንጀሎችን በመከላከል፣ ወሳኝ ተቋማትንና የቱሪዝም መዳረሻዎችን በመጠበቅ ለሀገራዊ ሰላምና ፀጥታ የበኩሉን አስተዋጽኦ እያበረከተ መሆኑን ምክትል ኮሚሽነሩ ጠቅሰዋል።
በዘመናዊው የፀጥታ ሥራ የመረጃ፣ የሳይበር ደህንነትና የዲጂታል ቴክኖሎጂ ሚና እየጨመረ መምጣቱን ያመለከቱት ምክትል ኮሚሽነሩ፣ የሀገሪቱን ወሳኝ ዲጂታል መሠረተ ልማቶች ከሳይበር ጥቃቶች መጠበቅና የዲጂታል ሉዓላዊነትን ማረጋገጥ የዘመኑ የፀጥታ ሥራ ዋና አካላት መሆናቸውን ገልጸዋል።
በተለይም አርቴፊሻል ኢንተለጀንስንና ሌሎች ዘመናዊ ቴክኖሎጂዎችን ከፀጥታ ሥራ ጋር በማስተሳሰር የሀገሪቱን ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ችግሮች ለመፍታት፣ የፀጥታ ሥራን ለማዘመንና ዲጂታል ኢትዮጵያን ለመገንባት የሚደረገው ሥራ መጠናከር እንዳለበት አስገንዝበዋል።
የፅናት ቀን በዚህ መልኩ የፀጥታ ተቋማት የሚያከናውኗቸውን ሥራዎችና የሚያስመዘግቧቸውን ውጤቶች ለሕዝብ ለማስተዋወቅ፣ የተቋማትን ቅንጅት ለማጠናከርና ለሀገራዊ ሰላምና ልማት የሚያበረክቱትን ድርሻ ለማጉላት ጠቃሚ መድረክ መሆኑን ምክትል ኮሚሽነር መላኩ ፋንታ ገልጸዋል።
ዘጋቢ ብዙአየሁ ተሾመ
ፎቶግራፍ አበረ አየነው
ሳላም ለአለማችን ይሁን!
ሰላማችንን በሰለማዊ መንገድ እናደርግ ፣ እናስተዳድር ፣ እንምረ!
የኢፌዴሪ መከላከያ ሠራዊት
https://dfmc.mod.gov.et/
https://www.facebook.com/EthioPolice.et
https://www.facebook.com/Ethiopeaces